በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 82

ኢየሱስ ስለ ጸሎት አስተማረ

ኢየሱስ ስለ ጸሎት አስተማረ

ፈሪሳውያን ማንኛውንም ነገር የሚያደርጉት የሰዎችን ትኩረት ለመሳብ ነበር። ለሰዎች ጥሩ ነገር የሚያደርጉት ሌሎች እንዲያዩዋቸው ብለው ነው። ሰው እንዲያያቸው ሲሉ ሕዝብ በብዛት በሚገኝባቸው ቦታዎች ይጸልዩ ነበር። ፈሪሳውያን ረጅም ጸሎቶችን ሸምድደው በምኩራብና በመንገድ ላይ ሰዎች እየሰሟቸው ይጸልዩ ነበር። ስለዚህ ኢየሱስ እንዲህ ብሎ ሲናገር የሚሰሙት ሰዎች ተገርመው ነበር፦ ‘እንደ ፈሪሳውያን አትጸልዩ። እነሱ ረጅም ጸሎት ስላቀረቡ ብቻ አምላክ የሚደሰት ይመስላቸዋል፤ አምላክ ግን በዚህ አይደሰትም። የምትጸልዩት ሌሎች እንዲያዩዋችሁ ብላችሁ ሳይሆን አባታችሁን ይሖዋን በግል ለማነጋገር መሆን አለበት። ጸሎታችሁ እንዲሁ ድግግሞሽ መሆን የለበትም። ይሖዋ በውስጣችሁ የሚሰማችሁን ነገር በግልጽ እንድትነግሩት ይፈልጋል።

‘እንዲህ ብላችሁ ጸልዩ፦ “በሰማያት የምትኖር አባታችን ሆይ፣ ስምህ ይቀደስ። መንግሥትህ ይምጣ። ፈቃድህ በሰማይ እየተፈጸመ እንዳለ ሁሉ በምድርም ላይ ይፈጸም።”’ በተጨማሪም ኢየሱስ፣ ይሖዋ የዕለት ምግባቸውን እንዲሰጣቸው፣ ኃጢአታቸውን ይቅር እንዲላቸው እንዲሁም ስለ ሌሎች የግል ጉዳዮቻቸው እንዲጸልዩ ነግሯቸዋል።

ኢየሱስ እንዲህ ብሏል፦ ‘መጸለያችሁን አታቋርጡ። አባታችሁን ይሖዋን ጥሩ ነገር እንዲያደርግላችሁ ጠይቁት። ሁሉም ወላጅ ለልጁ ጥሩ ነገር መስጠት ይፈልጋል። ልጃችሁ ዳቦ እንድትሰጡት ቢጠይቃችሁ ድንጋይ ትሰጡታላችሁ? ወይስ ዓሣ እንድትሰጡት ቢጠይቃችሁ እባብ ትሰጡታላችሁ?’

ከዚያም ኢየሱስ የምሳሌውን ትርጉም አብራራ፦ ‘እናንተ ለልጆቻችሁ ጥሩ ስጦታ መስጠት የምትችሉ ከሆነ አባታችሁ ይሖዋ እንዴት መንፈስ ቅዱስን አይሰጣችሁም? ከእናንተ የሚጠበቀው መጠየቅ ብቻ ነው።’ አንተስ የኢየሱስን ምክር ትከተላለህ? ስለ ምን ጉዳይ ትጸልያለህ?

“ደጋግማችሁ ለምኑ፣ ይሰጣችኋል፤ ሳታቋርጡ ፈልጉ፣ ታገኛላችሁ፤ ደጋግማችሁ አንኳኩ፣ ይከፈትላችኋል።”—ማቴዎስ 7:7