በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 90

ኢየሱስ በጎልጎታ ተገደለ

ኢየሱስ በጎልጎታ ተገደለ

የካህናት አለቆቹ ኢየሱስን ወደ አገረ ገዢው ቤተ መንግሥት ወሰዱት። ጲላጦስም ‘በዚህ ሰው ላይ የምታቀርቡት ክስ ምንድን ነው?’ ብሎ ጠየቃቸው። እነሱም ‘ንጉሥ ነኝ ብሏል!’ አሉት። ከዚያም ጲላጦስ ኢየሱስን “አንተ የአይሁዳውያን ንጉሥ ነህ?” በማለት ጠየቀው። ኢየሱስም “መንግሥቴ የዚህ ዓለም ክፍል አይደለም” አለው።

ከዚያም ጲላጦስ፣ በኢየሱስ ላይ ጥፋት ያገኝበት እንደሆነ ለማየት ኢየሱስን የገሊላ ገዢ ወደሆነው ወደ ሄሮድስ ላከው። ሄሮድስ ግን በኢየሱስ ላይ ምንም ጥፋት ስላላገኘበት መልሶ ወደ ጲላጦስ ላከው። ከዚያም ጲላጦስ ሕዝቡን ‘እኔም ሆንኩ ሄሮድስ በዚህ ሰው ላይ ምንም ጥፋት አላገኘንበትም። ስለዚህ እፈታዋለሁ’ አላቸው። ሕዝቡ ግን ‘ግደለው! ግደለው!’ እያሉ ጮኹ። ወታደሮቹ ኢየሱስን ገረፉት፤ ተፉበት እንዲሁም መቱት። ከእሾህ የተሠራ ዘውድ በራሱ ላይ አድርገው ‘የአይሁዳውያን ንጉሥ ሆይ፣ ሰላም ለአንተ ይሁን’ እያሉ አሾፉበት። ጲላጦስ በድጋሚ ሕዝቡን ‘በዚህ ሰው ላይ ምንም ጥፋት አላገኘሁበትም’ አላቸው። እነሱ ግን “ይሰቀል!” እያሉ ጮኹ። ስለዚህ ጲላጦስ ኢየሱስን እንዲሰቀል አሳልፎ ሰጠው።

ወታደሮቹም ኢየሱስን ጎልጎታ ወደሚባል ቦታ ወስደው በእንጨት ላይ በምስማር ቸነከሩት፤ ከዚያም እንጨቱን አቆሙት። ኢየሱስም ‘አባት ሆይ፣ የሚያደርጉትን ስለማያውቁ ይቅር በላቸው’ ብሎ ጸለየ። ሰዎቹም ‘የአምላክ ልጅ ከሆንክ፣ እስቲ ከተሰቀልክበት እንጨት ላይ ውረድ! እስቲ ራስህን አድን!’ እያሉ ያሾፉበት ነበር።

ከጎኑ ከተሰቀሉት ወንጀለኞች መካከል አንዱ ኢየሱስን “ወደ መንግሥትህ ስትመጣ አስበኝ” አለው። ኢየሱስም “ከእኔ ጋር በገነት ትሆናለህ” በማለት ቃል ገባለት። ከሰዓት በኋላ ለሦስት ሰዓት ያህል ጨለማ ሆነ። የኢየሱስን እናት ማርያምን ጨምሮ አንዳንድ ደቀ መዛሙርት ኢየሱስ በተሰቀለበት እንጨት አቅራቢያ ቆመው ነበር። ኢየሱስም ማርያምን ልክ እንደ እናቱ አድርጎ እንዲንከባከባት ለዮሐንስ ነገረው።

በመጨረሻም ኢየሱስ “ተፈጸመ!” አለ። ከዚያም ራሱን ወደ ፊት ዘንበል አድርጎ የመጨረሻ ትንፋሹን ተነፈሰ። ወዲያውኑ ኃይለኛ የመሬት መንቀጥቀጥ ተከሰተ። በቤተ መቅደሱ ውስጥ ቅድስቱን ከቅድስተ ቅዱሳኑ የሚለየው ትልቅ መጋረጃ ለሁለት ተቀደደ። አንድ የጦር መኮንን እነዚህን ነገሮች ሲያይ ‘ይህ በእርግጥ የአምላክ ልጅ ነበር’ አለ።

“አምላክ የሰጣቸው ተስፋዎች የቱንም ያህል ብዙ ቢሆኑም በእሱ አማካኝነት ‘አዎ’ ሆነዋል።”—2 ቆሮንቶስ 1:20