በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 18

እውነተኛ ክርስቲያኖችን ለይቶ ማወቅ የሚቻለው እንዴት ነው?

እውነተኛ ክርስቲያኖችን ለይቶ ማወቅ የሚቻለው እንዴት ነው?

በቢሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎች ክርስቲያኖች እንደሆኑ ይናገራሉ። ሆኖም የሚያምኑበት ነገርም ሆነ የሚመሩበት መሥፈርት የተለያየ ነው። ታዲያ እውነተኛ ክርስቲያኖችን ለይተን ማወቅ የምንችለው እንዴት ነው?

1. ክርስቲያን ማለት ምን ማለት ነው?

ክርስቲያን ማለት የኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዝሙር ወይም ተከታይ ማለት ነው። (የሐዋርያት ሥራ 11:26⁠ን አንብብ።) ክርስቲያኖች የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት መሆናቸውን የሚያሳዩት እንዴት ነው? ኢየሱስ “ቃሌን ጠብቃችሁ ብትኖሩ በእርግጥ ደቀ መዛሙርቴ ናችሁ” ብሏል። (ዮሐንስ 8:31) ስለዚህ እውነተኛ ክርስቲያኖች ኢየሱስ ያስተማረውን ትምህርት መታዘዝ አለባቸው። በተጨማሪም ኢየሱስ የሚያስተምረው ነገር በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሠረተ እንደነበር ሁሉ እውነተኛ ክርስቲያኖችም የሚያምኑበት ነገር በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሠረተ መሆን አለበት።—ሉቃስ 24:27⁠ን አንብብ።

2. እውነተኛ ክርስቲያኖች አንዳቸው ለሌላው ፍቅር እንዳላቸው የሚያሳዩት እንዴት ነው?

ኢየሱስ ተከታዮቹን “እኔ እንደወደድኳችሁ እናንተም እርስ በርሳችሁ ተዋደዱ” ብሏቸዋል። (ዮሐንስ 15:12) ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱን እንደሚወዳቸው ያሳየው እንዴት ነው? ከእነሱ ጋር ጊዜ ያሳልፍ፣ ያበረታታቸው እንዲሁም ይረዳቸው ነበር። አልፎ ተርፎም ለእነሱ ሲል ሕይወቱን አሳልፎ ሰጥቷል። (1 ዮሐንስ 3:16) በተመሳሳይም እውነተኛ ክርስቲያኖች ስለ ፍቅር ከማውራት ያለፈ ነገር ያደርጋሉ። እርስ በርስ እንደሚዋደዱ በቃል ብቻ ሳይሆን በተግባርም ያሳያሉ።

3. እውነተኛ ክርስቲያኖች በየትኛው ሥራ ይካፈላሉ?

ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ ሥራ ሰጥቷቸዋል። “የአምላክን መንግሥት እንዲሰብኩ” ልኳቸዋል። (ሉቃስ 9:2) በጥንት ዘመን የነበሩ ክርስቲያኖች በአምልኮ ቦታቸው ብቻ ሳይሆን ወደ መኖሪያ ቤቶችና ሰዎች ወደሚገኙባቸው ቦታዎች እየሄዱ ይሰብኩ ነበር። (የሐዋርያት ሥራ 5:42⁠ን እና 17:17⁠ን አንብብ።) በዘመናችን ያሉ እውነተኛ ክርስቲያኖችም ሰዎች በሚገኙበት ቦታ ሁሉ የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት ያስተምራሉ። ለሰዎች ፍቅር ስላላቸው ጊዜያቸውንና ጉልበታቸውን መሥዋዕት በማድረግ ተስፋና መጽናኛ የሚሰጠውን የመጽሐፍ ቅዱስ መልእክት በደስታ ይሰብካሉ።—ማርቆስ 12:31

ጠለቅ ያለ ጥናት

እውነተኛ ክርስቲያኖችን የኢየሱስን ትምህርትና ምሳሌ ከማይከተሉ ሰዎች መለየት የምትችለው እንዴት እንደሆነ እንመለከታለን።

4. ለመጽሐፍ ቅዱስ እውነት ትልቅ ቦታ ይሰጣሉ

የጥንቶቹ ክርስቲያኖች የአምላክን ቃል ከፍ አድርገው ይመለከቱ ነበር

አንዳንድ ሰዎች ክርስቲያን እንደሆኑ ቢናገሩም ለመጽሐፍ ቅዱስ እውነት አክብሮት የላቸውም። ቪዲዮውን ተመልከቱ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • ክርስቲያን ነን የሚሉ አንዳንድ አብያተ ክርስቲያናት ኢየሱስ ካስተማረው ትምህርት ያፈነገጡት እንዴት ነው?

ኢየሱስ በአምላክ ቃል ውስጥ የሚገኘውን እውነት አስተምሯል። ዮሐንስ 18:37ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • ኢየሱስ በተናገረው መሠረት ‘ከእውነት ጎን የቆሙትን’ ክርስቲያኖች ለይተን ማወቅ የምንችለው እንዴት ነው?

5. የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት ይሰብካሉ

የጥንቶቹ ክርስቲያኖች ለሌሎች ይሰብኩ ነበር

ኢየሱስ ወደ ሰማይ ከማረጉ በፊት ለተከታዮቹ እስከ ዛሬ ድረስ የዘለቀ አንድ ተልእኮ ሰጥቷቸዋል። ማቴዎስ 28:19, 20ን እንዲሁም የሐዋርያት ሥራ 1:8ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • የስብከቱ ሥራ ምን ያህል ስፋት ይኖረዋል?

6. የሚሰብኩትን ይሠሩበታል

ቶም የተባለ ሰው እውነተኛ ክርስትናን እንዳገኘ እርግጠኛ እንዲሆን ያደረገው ምንድን ነው? ቪዲዮውን ተመልከቱ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • በቪዲዮው ላይ እንደታየው ቶምን በሃይማኖት ተስፋ እንዲቆርጥ ያደረገው ምን ነበር?

  • እውነትን እንዳገኘ እርግጠኛ እንዲሆን ያደረገው ምንድን ነው?

የምናደርገው ነገር ከምንናገረው ነገር የበለጠ ኃይል አለው። ማቴዎስ 7:21ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • ኢየሱስ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው እንደምናምንበት ለምንናገረው ነገር ነው ወይስ በድርጊታችን ለምናሳየው ነገር?

7. እርስ በርስ ይዋደዳሉ

የጥንቶቹ ክርስቲያኖች እርስ በርስ ይዋደዱ ነበር

በእርግጥ ክርስቲያኖች ለሌሎች ክርስቲያኖች ሲሉ ሕይወታቸውን አደጋ ላይ ለመጣል ፈቃደኛ ናቸው? ቪዲዮውን ተመልከቱ ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

  • በቪዲዮው ላይ ሎይድ፣ ወንድም ዮሐንሰንን ለማዳን ሲል ሕይወቱን አደጋ ላይ እንዲጥል ያነሳሳው ምንድን ነው?

  • ከእውነተኛ ክርስቲያኖች የሚጠበቀውን ነገር አድርጓል ትላለህ?

ዮሐንስ 13:34, 35ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

  • የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት (እውነተኛ ክርስቲያኖች) ሌላ ብሔር ወይም ዘር ላለው ሰው ምን አመለካከት አላቸው?

  • በጦርነት ወቅት ይህን የሚያሳዩት እንዴት ነው?

አንዳንዶች እንዲህ ይላሉ፦ “የየትኛውም ሃይማኖት አባል ብትሆን ለውጥ አያመጣም። ዋናው ነገር በኢየሱስ ክርስቶስ ማመንህ ነው።”

  • እውነተኛዎቹ የኢየሱስ ክርስቶስ ተከታዮች ከሌሎች የተለዩ እንደሆኑ ለማሳየት የትኛውን ጥቅስ ትጠቀማለህ?

ማጠቃለያ

እውነተኛ ክርስቲያኖች መጽሐፍ ቅዱስን በጥብቅ ይከተላሉ፤ ከራስ ወዳድነት ነፃ የሆነ ፍቅር ያሳያሉ፤ እንዲሁም የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት ይሰብካሉ።

ክለሳ

  • እውነተኛ ክርስቲያኖች የሚያምኑበት ነገር በምን ላይ የተመሠረተ ነው?

  • እውነተኛ ክርስቲያኖች ተለይተው የሚታወቁት በየትኛው ባሕርይ ነው?

  • እውነተኛ ክርስቲያኖች የትኛውን ሥራ ያከናውናሉ?

ግብ

ምርምር አድርግ

ኢየሱስ ክርስቶስ የተወውን ምሳሌና ያስተማረውን ትምህርት ለመከተል ጥረት የሚያደርግ አንድ ቡድን አለ። ይህ ቡድን ማን ነው?

ስለ ይሖዋ ምሥክሮች ማወቅ ትፈልጋለህ? (1:13)

መነኩሲት የነበረች አንዲት ሴት “እውነተኛ መንፈሳዊ ቤተሰብ” ያገኘችው እንዴት ነው?

“ጥያቄዎቼን በሙሉ የመለሱልኝ ከመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ነው!” (መጠበቂያ ግንብ ሚያዝያ 1, 2014)

እውነተኛ ክርስቲያኖች እርዳታ ለሚያስፈልጋቸው ወንድሞቻቸውና እህቶቻቸው ፍቅር የሚያሳዩት እንዴት ነው?

በአደጋ ወቅት ወንድሞቻችንን መርዳት—ተቀንጭቦ የተወሰደ (3:57)

በጥንት ዘመን የነበሩት ክርስቲያኖችም ሆኑ በዘመናችን ያሉት እውነተኛ ክርስቲያኖች፣ ኢየሱስ የእሱ ተከታዮች ተለይተው እንደሚታወቁበት የተናገረውን መሥፈርት የሚያሟሉት እንዴት ነው?

“የእውነተኛው ክርስትና መለያ ምልክቶች ምንድን ናቸው?” (መጠበቂያ ግንብ መጋቢት 1, 2012)