በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 21

ምሥራቹ እየተሰበከ ያለው እንዴት ነው?

ምሥራቹ እየተሰበከ ያለው እንዴት ነው?

በቅርቡ ይሖዋ እሱ ባቋቋመው መንግሥት አማካኝነት ችግሮቻችንን ሁሉ ያስወግድልናል። ይህ ሁሉም ሰው ሊያውቀው የሚገባ አስደሳች ዜና ነው። ኢየሱስ ተከታዮቹ ይህን መልእክት ለሌሎች እንዲናገሩ አዟል! (ማቴዎስ 28:19, 20) የይሖዋ ምሥክሮች ኢየሱስ የሰጠውን ይህን ትእዛዝ እየፈጸሙ ያሉት እንዴት ነው?

1. በማቴዎስ 24:14 ላይ ያለው ሐሳብ በዛሬው ጊዜ እየተፈጸመ ያለው እንዴት ነው?

ኢየሱስ “ይህ የመንግሥቱ ምሥራች ለብሔራት ሁሉ ምሥክር እንዲሆን በመላው ምድር ይሰበካል” በማለት አስቀድሞ ተናግሯል። (ማቴዎስ 24:14) እኛ የይሖዋ ምሥክሮች በዚህ አስፈላጊ ሥራ መካፈል ያስደስተናል። በዓለም ዙሪያ ከ1,000 በሚበልጡ ቋንቋዎች ምሥራቹን እየሰበክን ነው! መጠነ ሰፊ የሆነውን ይህን ሥራ ለማከናወን ትጋት የተሞላበት ጥረት ማድረግና በሚገባ የተደራጁ መሆን ያስፈልጋል። ያለይሖዋ እርዳታ ይህን ሥራ ማከናወን አይቻልም።

2. ለሰዎች ለመስበክ የትኞቹን ዘዴዎች እንጠቀማለን?

ሰዎችን በምናገኝባቸው ቦታዎች ሁሉ እንሰብካለን። በመጀመሪያው መቶ ዘመን እንደነበሩት ክርስቲያኖች ሁሉ እኛም “ከቤት ወደ ቤት” እየሄድን ምሥራቹን እንናገራለን። (የሐዋርያት ሥራ 5:42) ይህ የስብከት ዘዴ በየዓመቱ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎችን ለማግኘት ያስችለናል። አንዳንድ ጊዜ ሰዎች ቤታቸው ስለማይገኙ በሌሎች ቦታዎችም እንሰብካለን። ስለ ይሖዋና ስለ ዓላማዎቹ ለሰዎች ለመናገር የሚያስችሉንን አጋጣሚዎች ሁሉ ለመጠቀም ጥረት እናደርጋለን።

3. ምሥራቹን የመስበክ ኃላፊነት ያለበት ማን ነው?

እውነተኛ ክርስቲያኖች በሙሉ ምሥራቹን ለሌሎች የመናገር ኃላፊነት አለባቸው። ይህን ኃላፊነታችንን በቁም ነገር እንመለከተዋለን። አቅማችን እስከፈቀደው ድረስ ምሥራቹን ለመስበክ ጥረት እናደርጋለን፤ ምክንያቱም እንዲህ ማድረጋችን የሰዎችን ሕይወት እንደሚያድን እንገነዘባለን። (1 ጢሞቴዎስ 4:16⁠ን አንብብ።) መጽሐፍ ቅዱስ “በነፃ እንደተቀበላችሁ በነፃ ስጡ” ይላል፤ ስለዚህ ይህን ሥራ ስናከናውን ምንም ዓይነት ክፍያ አንቀበልም። (ማቴዎስ 10:7, 8) አንዳንዶች የምንሰብከውን መልእክት ባይቀበሉም መስበካችንን እንቀጥላለን። ምክንያቱም የስብከቱ ሥራ የአምልኳችን ክፍል ከመሆኑም በላይ ይሖዋን ያስደስተዋል።

ጠለቅ ያለ ጥናት

የይሖዋ ምሥክሮች እያከናወኑ ስላሉት ዓለም አቀፍ የስብከት ሥራና ይሖዋ ይህን ሥራ እየደገፈ ያለው እንዴት እንደሆነ እንመለከታለን።

4. ሁሉም ሰዎች ምሥራቹ እንዲደርሳቸው ከፍተኛ ጥረት እናደርጋለን

የይሖዋ ምሥክሮች በሁሉም ቦታ ለሚኖሩ ሰዎች ምሥራቹን ለመስበክ ልዩ ጥረት ያደርጋሉ። ቪዲዮውን ተመልከቱ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • የይሖዋ ምሥክሮች ምሥራቹን ለመስበክ ከሚያደርጉት ጥረት ጋር በተያያዘ አንተን የሚያስገርምህ ምንድን ነው?

ማቴዎስ 22:39ን እና ሮም 10:13-15ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

  • የስብከቱ ሥራችን ሰዎችን እንደምንወድ የሚያሳየው እንዴት ነው?

  • ይሖዋ ምሥራቹን ለሚሰብኩ ሰዎች ምን አመለካከት አለው?—ሮም 10:15⁠ን ተመልከት።

5. የምንሠራው ከአምላክ ጋር ነው

ብዙ ተሞክሮዎች እንደሚያሳዩት ሥራችንን የሚመራው ይሖዋ ነው። ለምሳሌ ያህል፣ ፖል የተባለ በኒው ዚላንድ የሚኖር ወንድም አንድ ቀን ከሰዓት ከቤት ወደ ቤት ሲያገለግል አንዲት ሴት አገኘ። ሴትየዋ በዚያኑ ዕለት ይሖዋ የሚለውን ስም ተጠቅማ ወደ አምላክ የጸለየች ሲሆን አንድ ሰው መጥቶ እንዲያነጋግራት አምላክን ለምናው ነበር። ፖል “ይህ ከሆነ ከሦስት ሰዓት በኋላ ወደ ቤቷ ሄድኩ” ሲል ተናግሯል።

አንደኛ ቆሮንቶስ 3:9ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • ፖል እንዳጋጠመው ዓይነት ተሞክሮዎች ይሖዋ የስብከቱን ሥራ እየመራው እንዳለ የሚያሳዩት እንዴት ነው?

የሐዋርያት ሥራ 1:8ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • የስብከቱን ሥራ ለመሥራት የይሖዋ እርዳታ የሚያስፈልገን ለምንድን ነው?

ይህን ታውቅ ነበር?

በሳምንቱ መሃል በምናደርገው ስብሰባ ላይ እንዴት መስበክ እንዳለብን የሚያሳይ ሥልጠና ይሰጠናል። በዚህ ስብሰባ ላይ ተገኝተህ የምታውቅ ከሆነ ስለሚሰጠው ሥልጠና ምን ተሰማህ?

6. አምላክ እንድንሰብክ የሰጠንን ትእዛዝ እንፈጽማለን

በመጀመሪያው መቶ ዘመን ተቃዋሚዎች የኢየሱስ ተከታዮች የሚያከናውኑትን የስብከት ሥራ ለማስቆም ጥረት አድርገው ነበር። በዚያን ጊዜ የነበሩት ክርስቲያኖች ‘ምሥራቹ በሕግ የጸና እንዲሆን በማድረግ’ የመስበክ መብታቸውን ለማስጠበቅ ሞክረዋል። (ፊልጵስዩስ 1:7) በዛሬው ጊዜ ያሉ የይሖዋ ምሥክሮችም እንዲህ ያደርጋሉ። a

የሐዋርያት ሥራ 5:27-42ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

አንድ ሰው እንዲህ ብሎ ቢጠይቅህስ? “የይሖዋ ምሥክሮች ወደ ሰዎች ቤት እየሄዱ የሚሰብኩት ለምንድን ነው?”

  • ምን ብለህ ትመልሳለህ?

ማጠቃለያ

ኢየሱስ ተከታዮቹን ለሁሉም ብሔራት ምሥራቹን እንዲሰብኩ አዟቸዋል። ይሖዋ ሕዝቦቹ ይህን ሥራ እንዲያከናውኑ እየረዳቸው ነው።

ክለሳ

  • ምሥራቹ በዓለም ዙሪያ እየተሰበከ ያለው እንዴት ነው?

  • ምሥራቹን መስበካችን ሰዎችን እንደምንወድ የሚያሳየው እንዴት ነው?

  • የስብከቱ ሥራ አስደሳች እንደሆነ ይሰማሃል? እንዲህ ብለህ የመለስከው ለምንድን ነው?

ግብ

ምርምር አድርግ

የይሖዋ ምሥክሮች በትላልቅ ከተሞች ለሚኖሩ ሰዎች የሚሰብኩት እንዴት ነው?

በፓሪስ የተደረገ ልዩ የአደባባይ ምሥክርነት (5:11)

የይሖዋ ምሥክሮች ለስደተኞች ለመስበክ ምን ጥረት አድርገዋል?

የስደተኞችን መንፈሳዊ ጥማት ማርካት (5:59)

ሕይወቷን ሙሉ በስብከቱ ሥራ ያሳለፈች አንዲት ሴት ይህ ሥራ የሚያስደስታት ለምን እንደሆነ ስትናገር ተመልከት።

በመረጥኩት ሥራ ደስተኛ ነኝ (6:29)

በፍርድ ቤት ያገኘናቸው አንዳንድ ድሎች የስብከቱን ሥራ ለማስፋፋት የረዱን እንዴት ነው?

“የመንግሥቱ ሰባኪዎች ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እንዲታይላቸው አደረጉ” (የአምላክ መንግሥት እየገዛ ነው! ምዕራፍ 13)

a ለሰዎች እንድንሰብክ ያዘዘን አምላክ ነው። በመሆኑም የይሖዋ ምሥክሮች ምሥራቹን ለመስበክ የባለሥልጣናት ፈቃድ አያስፈልጋቸውም።