ምዕራፍ 27

የኢየሱስ ሞት የሚያድነን እንዴት ነው?

የኢየሱስ ሞት የሚያድነን እንዴት ነው?
ጽሑፉን አሳይ ጽሑፉን ደብቅ

የመጀመሪያዎቹ ሰዎች ማለትም አዳምና ሔዋን አምላክን ባለመታዘዛቸው ለኃጢአት፣ ለመከራና ለሞት ተዳርገናል። a ታዲያ ምንም ተስፋ የለንም ማለት ነው? በፍጹም! ይሖዋ በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ አማካኝነት ከኃጢአትና ከሞት ነፃ የምንወጣበት ዝግጅት አድርጎልናል። መጽሐፍ ቅዱስ ኢየሱስ ሕይወቱን አሳልፎ በመስጠት ቤዛ እንደከፈለ ይናገራል። ቤዛ ማለት አንድን ሰው ነፃ ለማውጣት የሚከፈል ዋጋ ነው። ኢየሱስ የከፈለው ፍጹም ሰብዓዊ ሕይወቱን ነው። (ማቴዎስ 20:28⁠ን አንብብ።) ኢየሱስ በምድር ላይ ለዘላለም የመኖር አጋጣሚውን በፈቃደኝነት አሳልፎ በመስጠት አዳምና ሔዋን ያጡትን ነገር በሙሉ መልሰን የምናገኝበት መንገድ ከፍቶልናል። በተጨማሪም ኢየሱስ እሱና ይሖዋ ለእኛ ምን ያህል ጥልቅ ፍቅር እንዳላቸው አሳይቷል። ይህ ምዕራፍ ኢየሱስ ለአንተ ላደረገው ነገር ያለህን አድናቆት ያሳድግልሃል።

1. የኢየሱስ ሞት በዛሬው ጊዜ የሚጠቅመን እንዴት ነው?

ኃጢአተኞች ስለሆንን ይሖዋን የሚያሳዝኑ ብዙ ነገሮችን እናደርጋለን። ሆኖም በሠራነው ኃጢአት ከልብ ካዘንን፣ ይሖዋ ይቅር እንዲለን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ከለመንንና ስህተታችንን ላለመድገም የቻልነውን ሁሉ ካደረግን ከአምላክ ጋር የጠበቀ ወዳጅነት መመሥረት እንችላለን። (1 ዮሐንስ 2:1) መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ “ጻድቅ የሆነው ክርስቶስ እንኳ ለዓመፀኞች ሲል ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ በመሞት ከኃጢአት ነፃ አውጥቷቸዋልና። ይህን ያደረገው እናንተን ወደ አምላክ ለመምራት ነው።”1 ጴጥሮስ 3:18

2. የኢየሱስ ሞት ወደፊት የሚጠቅመን እንዴት ነው?

ይሖዋ ኢየሱስን ፍጹም ሰብዓዊ ሕይወቱን እንዲሰጥ ልኮታል። ይህን ያደረገው በኢየሱስ “የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ ሲል” ነው። (ዮሐንስ 3:16) ኢየሱስ ባደረገው ነገር የተነሳ ይሖዋ የአዳም አለመታዘዝ ያስከተለውን ጉዳት በሙሉ በቅርቡ ያስተካክላል። በመሆኑም በኢየሱስ መሥዋዕት ላይ እምነት እንዳለን ካሳየን ገነት በምትሆነው ምድር ላይ ለዘላለም የመኖር አጋጣሚ እናገኛለን!—ኢሳይያስ 65:21-23

ጠለቅ ያለ ጥናት

ኢየሱስ ሕይወቱን አሳልፎ የሰጠው ለምን እንደሆነ በስፋት እንመለከታለን፤ በተጨማሪም የኢየሱስ መሥዋዕት ለአንተ የሚጠቅምህ እንዴት እንደሆነ እንመረምራለን።

3. የኢየሱስ ሞት ከኃጢአትና ከሞት ነፃ ያወጣናል

ቪዲዮውን ተመልከቱ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • አዳም አምላክን ባለመታዘዙ ምን አጋጣሚ አጥቷል?

ሮም 5:12ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • አዳም ኃጢአት መሥራቱ በአንተ ላይ ምን ውጤት አስከትሏል?

ዮሐንስ 3:16ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • ይሖዋ ልጁን ወደ ምድር የላከው ለምንድን ነው?

  1. ሀ. ፍጹም ሰው የነበረው አዳም አምላክን ባለመታዘዙ የሰው ልጆችን ለኃጢአትና ለሞት ዳርጓቸዋል

  2. ለ. ፍጹም ሰው የነበረው ኢየሱስ አምላክን ስለታዘዘ የሰው ልጆች ፍጽምና ላይ መድረስና የዘላለም ሕይወት ማግኘት የሚችሉበት መንገድ ከፍቷል

4. የኢየሱስ ሞት ለሁሉም ሰው ጥቅም ያስገኛል

ቪዲዮውን ተመልከቱ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • የአንድ ሰው ሞት ሁሉንም ሰዎች ሊጠቅም የሚችለው እንዴት ነው?

አንደኛ ጢሞቴዎስ 2:5, 6ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • ፍጹም ሰው የነበረው አዳም የሰው ልጆችን ለኃጢአትና ለሞት ዳርጓቸዋል። ኢየሱስም ፍጹም ሰው ነበር። ከዚህ አንጻር “ተመጣጣኝ ቤዛ” ሊከፍል የቻለው እንዴት ነው?

5. ቤዛው ይሖዋ ለአንተ የሰጠው ስጦታ ነው

የይሖዋ ወዳጆች ቤዛው ለእነሱ በግል የተሰጠ ስጦታ እንደሆነ ይሰማቸዋል። ይህን የሚያሳይ ምሳሌ ለመመልከት ገላትያ 2:20ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • ሐዋርያው ጳውሎስ ቤዛውን ለእሱ በግሉ እንደተሰጠው ስጦታ አድርጎ ይቆጥር እንደነበር በምን እናውቃለን?

አዳም በሠራው ኃጢአት የተነሳ እሱም ሆነ ዘሮቹ ሞት ተፈርዶባቸዋል። ይሖዋ ግን ልጁን ለእኛ ሲል እንዲሞት በመላክ የዘላለም ሕይወት የምታገኝበት መንገድ ከፍቶልሃል።

ቀጣዮቹ ጥቅሶች ሲነበቡ ይሖዋ ልጁ ሲሠቃይ ምን እንደተሰማው በዓይነ ሕሊናህ ለመሣል ሞክር። ዮሐንስ 19:1-7⁠ን እና 16-18ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • ይሖዋና ኢየሱስ ስላደረጉልህ ነገር ስታስብ ምን ይሰማሃል?

አንድ ሰው እንዲህ ብሎ ቢጠይቅህስ? “የአንድ ሰው ሞት ሁሉንም ሰዎች ሊያድን የሚችለው እንዴት ነው?”

  • ምን ብለህ ትመልሳለህ?

ማጠቃለያ

የኢየሱስ ሞት ይሖዋ ኃጢአታችንን ይቅር የሚልበት መሠረት እንዲኖረው አድርጓል፤ እንዲሁም ለዘላለም በደስታ የምንኖርበት መንገድ ከፍቶልናል።

ክለሳ

  • ኢየሱስ የሞተው ለምንድን ነው?

  • የኢየሱስ ፍጹም ሰብዓዊ ሕይወት ተመጣጣኝ ቤዛ ሊሆን የቻለው እንዴት ነው?

  • የኢየሱስ ሞት ለአንተ ምን ጥቅም ያስገኝልሃል?

ግብ

ምርምር አድርግ

የኢየሱስ ፍጹም ሰብዓዊ ሕይወት ‘ቤዛ’ ተብሎ የሚጠራው ለምንድን ነው?

“የኢየሱስ መሥዋዕት ‘ለብዙዎች ቤዛ’ የሆነው እንዴት ነው?” (ድረ ገጻችን ላይ የወጣ ርዕስ

a ኃጢአት የሚለው ቃል ትክክል ያልሆነ ነገር ማድረግን ብቻ የሚያመለክት አይደለም። ከዚህ ይልቅ ከአዳምና ከሔዋን የወረስነውን ወደተሳሳተ አቅጣጫ የሚመራ ዝንባሌም ያመለክታል።