በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 32

የአምላክ መንግሥት መግዛት ጀምሯል!

የአምላክ መንግሥት መግዛት ጀምሯል!

የአምላክ መንግሥት ከ1914 አንስቶ በሰማይ መግዛት ጀምሯል። የሰዎች አገዛዝ መደምደሚያ የሆኑት የመጨረሻዎቹ ቀናትም የጀመሩት በዚሁ ዓመት ነው። ይህን እንዴት እናውቃለን? ይህን ጥያቄ ለመመለስ የመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢቶችን እንመለከታለን፤ በተጨማሪም ከ1914 አንስቶ በዓለም ላይ እየተከናወኑ ያሉትን ነገሮችና ሰዎች እያሳዩ ያሉትን ባሕርይ እንመረምራለን።

1. የመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢቶች ምን ይጠቁማሉ?

የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል የሆነው የዳንኤል ትንቢት የአምላክ መንግሥት መግዛት የሚጀምረው “ሰባት ዘመናት” ተብሎ የተገለጸው ጊዜ ሲያበቃ እንደሆነ ተናግሯል። (ዳንኤል 4:16, 17) በመቶዎች ከሚቆጠሩ ዓመታት በኋላ ኢየሱስ እነዚህኑ ሰባት ዘመናት “የተወሰኑት የአሕዛብ ዘመናት” ብሎ የጠራቸው ሲሆን በዚያ ወቅት እነዚህ ዘመናት እንዳላበቁ አስተምሯል። (ሉቃስ 21:24) በኋላ ላይ እንደምንመለከተው እነዚህ ዘመናት ያበቁት በ1914 ነው።

2. በዓለም ላይ ከሚከናወኑት ነገሮችና ሰዎች ከሚያሳዩት ባሕርይ ጋር በተያያዘ ከ1914 አንስቶ ምን ለውጥ ታይቷል?

የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ኢየሱስን ‘የመገኘትህና የዚህ ሥርዓት መደምደሚያ ምልክት ምንድን ነው?’ በማለት ጠይቀውት ነበር። (ማቴዎስ 24:3) ኢየሱስ ለጥያቄያቸው መልስ ሲሰጥ፣ እሱ የአምላክ መንግሥት ንጉሥ ሆኖ መግዛት ከጀመረ በኋላ የሚከናወኑ በርካታ ነገሮችን ነግሯቸዋል። ከነገራቸው ነገሮች መካከል ጦርነት፣ የምግብ እጥረትና የምድር ነውጥ ይገኙበታል። (ማቴዎስ 24:7⁠ን አንብብ።) መጽሐፍ ቅዱስ “በመጨረሻዎቹ ቀናት” ሰዎች ከሚያሳዩት ባሕርይ የተነሳ ‘ለመቋቋም የሚያስቸግር ዘመን’ እንደሚመጣም አስቀድሞ ተናግሯል። (2 ጢሞቴዎስ 3:1-5) በትንቢቶቹ ላይ የተጠቀሱት ነገሮች፣ በተለይ ከ1914 ወዲህ ጉልህ በሆነ መንገድ መታየት ጀምረዋል።

3. የአምላክ መንግሥት መግዛት ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ የዓለም ሁኔታ ይህን ያህል የተባባሰው ለምንድን ነው?

ኢየሱስ የአምላክ መንግሥት ንጉሥ ሆኖ ከተሾመ ብዙም ሳይቆይ በሰይጣንና በአጋንንቱ ላይ በሰማይ ጦርነት ከፈተ። ሰይጣን በጦርነቱ ተሸነፈ። መጽሐፍ ቅዱስ ከዚያ በኋላ ስለሆነው ነገር ሲናገር ‘ሰይጣን ወደ ምድር ተጣለ፤ መላእክቱም ከእሱ ጋር ተወረወሩ’ ይላል። (ራእይ 12:9, 10, 12) ሰይጣን መጥፋቱ እንደማይቀር ስለሚያውቅ በጣም ተቆጥቷል። በመላው ምድር ላይ ሥቃይና መከራ እያደረሰ ያለው በዚህ ምክንያት ነው። ከዚህ አንጻር፣ የዓለም ሁኔታ ይህን ያህል የከፋ ደረጃ ላይ መድረሱ ምንም አያስገርምም! የአምላክ መንግሥት እነዚህን ሁሉ ችግሮች ያስወግዳል።

ጠለቅ ያለ ጥናት

የአምላክ መንግሥት በ1914 መግዛት እንደጀመረ የምናውቀው እንዴት እንደሆነና ይህ ለእኛ ምን ትርጉም እንዳለው እንመለከታለን።

4. የመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢቶች ወደ 1914 ይጠቁማሉ

አምላክ የጥንቷ ባቢሎን ንጉሥ የነበረውን ናቡከደነጾርን ትንቢታዊ ትርጉም ያለው ሕልም እንዲያይ አድርጎታል። እሱ ካየው ሕልምና ዳንኤል ከሰጠው ትርጓሜ እንደምንረዳው፣ ሕልሙ የናቡከደነጾርን አገዛዝና የአምላክን መንግሥት የሚመለከት ነው።—ዳንኤል 4:17ን አንብቡ። a

ዳንኤል 4:20-26ን አንብቡ፤ ከዚያም ሰንጠረዡን ተጠቅማችሁ በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

  • (ሀ) ናቡከደነጾር በሕልሙ ምን አይቷል?—ቁጥር 20 እና 21⁠ን ተመልከት።

  • (ለ) ዛፉ ምን ይሆናል?—ቁጥር 23⁠ን ተመልከት።

  • (ሐ) ‘በሰባቱ ዘመናት’ መጨረሻ ላይ ምን ይፈጸማል?—ቁጥር 26⁠ን ተመልከት።

ስለ ዛፉ የሚገልጸው ሕልም ከአምላክ መንግሥት ጋር ምን ግንኙነት አለው?

ትንቢቱ (ዳንኤል 4:20-36)

አገዛዝ

(ሀ) ግዙፍ ዛፍ

አገዛዙ ተቋረጠ

(ለ) ‘ዛፉን ቁረጡ’ እንዲሁም ‘ሰባት ዘመናት ይለፉበት’

አገዛዙ መልሶ ተቋቋመ

(ሐ) “መንግሥትህ ይመለስልሃል”

በዚህ ትንቢት የመጀመሪያ ፍጻሜ መሠረት . . .

  • (መ) ዛፉ የሚያመለክተው ማንን ነው?—ቁጥር 22⁠ን ተመልከት።

  • (ሠ) አገዛዙ የተቋረጠው እንዴት ነው?ዳንኤል 4:29-33ን አንብቡ።

  • (ረ) ‘ሰባቱ ዘመናት’ ሲያበቁ ናቡከደነጾር ምን ሆነ?ዳንኤል 4:34-36ን አንብቡ።

የመጀመሪያው ፍጻሜ

አገዛዝ

(መ) የባቢሎን ንጉሥ የሆነው ናቡከደነጾር

አገዛዙ ተቋረጠ

(ሠ) ከ606 ዓ.ዓ. በኋላ ናቡከደነጾር አእምሮውን የሳተ ሲሆን ቃል በቃል ለሰባት ዓመታት መግዛት አልቻለም

አገዛዙ መልሶ ተቋቋመ

(ረ) ናቡከደነጾር አእምሮው ተመለሰለት፤ ዳግመኛም መግዛት ጀመረ

በዚህ ትንቢት ሁለተኛ ፍጻሜ መሠረት . . .

  • (ሰ) ዛፉ የሚያመለክተው እነማንን ነው?1 ዜና መዋዕል 29:23ን አንብቡ።

  • (ሸ) አገዛዛቸው የተቋረጠው እንዴት ነው? ኢየሱስ ምድር ላይ በነበረበት ጊዜም ጭምር ይህ አገዛዝ ተቋርጦ እንደነበር በምን እናውቃለን?ሉቃስ 21:24ን አንብቡ።

  • (ቀ) ይህ አገዛዝ መልሶ የተቋቋመው መቼና እንዴት ነው?

ሁለተኛው ፍጻሜ

አገዛዝ

(ሰ) የአምላክን አገዛዝ የሚወክሉ እስራኤላውያን ነገሥታት

አገዛዙ ተቋረጠ

(ሸ) ኢየሩሳሌም ጠፋች፤ በዳዊት የዘር ሐረግ የሚመጡት የእስራኤላውያን ነገሥታት መስመር ለ2,520 ዓመታት ተቋረጠ

አገዛዙ መልሶ ተቋቋመ

(ቀ) ኢየሱስ የአምላክ መንግሥት ንጉሥ በመሆን በሰማይ መግዛት ጀመረ

ሰባቱ ዘመናት ምን ያህል ርዝማኔ አላቸው?

አንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ላይ ያለው ሐሳብ በሌላ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ላይ ያለውን ሐሳብ ለመረዳት ያስችለናል። ለምሳሌ ያህል፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል የሆነው የራእይ መጽሐፍ ሦስት ተኩል ዘመናት የ1,260 ቀናት ርዝማኔ እንዳላቸው ይገልጻል። (ራእይ 12:6, 14) ሰባት ዘመናት፣ የሦስት ተኩል ዘመናትን እጥፍ ማለትም 2,520 ቀናትን ያመለክታሉ። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አንድ ቀን አንድ ዓመትን ለማመልከት የሚሠራበት ጊዜ አለ። (ሕዝቅኤል 4:6) በዳንኤል ትንቢት ላይ ከተጠቀሱት ሰባት ዘመናት ጋር በተያያዘም ሁኔታው ተመሳሳይ ነው፤ ሰባቱ ዘመናት 2,520 ዓመታትን ያመለክታሉ።

5. ከ1914 ወዲህ የዓለም ሁኔታ ተቀይሯል

ኢየሱስ እሱ ንጉሥ ከሆነ በኋላ በዓለም ላይ የሚታዩትን ሁኔታዎች አስቀድሞ ተናግሯል። ሉቃስ 21:9-11ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • እዚህ ጥቅስ ላይ ከተጠቀሱት ነገሮች መካከል አንተ ያየኸው ወይም የሰማኸው የትኞቹን ነው?

ሐዋርያው ጳውሎስ የሰው ልጆች አገዛዝ ከመደምደሙ በፊት ባሉት ‘የመጨረሻዎቹ ቀናት’ ሰዎች ምን ዓይነት ባሕርይ እንደሚኖራቸው ገልጿል። ሁለተኛ ጢሞቴዎስ 3:1-5ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • በዛሬው ጊዜ ሰዎች የትኞቹን ባሕርያት ሲያንጸባርቁ ተመልክተሃል?

6. የአምላክ መንግሥት እየገዛ መሆኑን ማወቃችን ለተግባር ያነሳሳናል

ማቴዎስ 24:3, 14ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

  • የአምላክ መንግሥት በመግዛት ላይ መሆኑን የሚያሳየው የትኛው አስፈላጊ ሥራ መከናወኑ ነው?

  • በዚህ ሥራ መሳተፍ የምትችለው እንዴት ነው?

የአምላክ መንግሥት አሁን በመግዛት ላይ ይገኛል፤ በቅርቡ ደግሞ መላዋን ምድር በቁጥጥሩ ሥር ያደርጋል። ዕብራውያን 10:24, 25ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • “ቀኑ እየቀረበ መምጣቱን ስናይ” እያንዳንዳችን ምን ማድረግ አለብን?

አንድ ነገር ሌሎችን ሊጠቅምና ሕይወታቸውን ሊያድን እንደሚችል ስታውቅ ምን ለማድረግ ትነሳሳለህ?

አንድ ሰው እንዲህ ብሎ ቢጠይቅህስ? “የይሖዋ ምሥክሮች ለ1914 ይህን ያህል ትኩረት የሚሰጡት ለምንድን ነው?”

  • ምን ብለህ ትመልሳለህ?

ማጠቃለያ

የመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢት እንዲሁም በዓለም ላይ የሚታዩት ሁኔታዎች የአምላክ መንግሥት አሁን በመግዛት ላይ መሆኑን ያረጋግጣሉ። ስለዚህ ጉዳይ በመስበክና በጉባኤ ስብሰባዎች ላይ በመገኘት የአምላክ መንግሥት እየገዛ መሆኑን እንደምናምን እናሳያለን።

ክለሳ

  • የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል በሆነው በዳንኤል መጽሐፍ ላይ በተገለጹት ሰባት ዘመናት ማብቂያ ላይ ምን ተከናውኗል?

  • የአምላክ መንግሥት በ1914 መግዛት ጀምሯል ብለህ እንድታምን የሚያደርግህ ምንድን ነው?

  • የአምላክ መንግሥት በመግዛት ላይ መሆኑን እንደምታምን ማሳየት የምትችለው እንዴት ነው?

ግብ

ምርምር አድርግ

የታሪክ ምሁራንና ሌሎች ሰዎች ከ1914 ወዲህ በዓለም ላይ ስለታየው ለውጥ ምን ይላሉ?

“ሥነ ምግባር በድንገት ማሽቆልቆል የጀመረበት ጊዜ” (ንቁ! ሚያዝያ 2007)

በማቴዎስ 24:14 ላይ የሚገኘው ትንቢት በአንድ ሰው ሕይወት ላይ ለውጥ ያመጣው እንዴት ነው?

“ከምንም ነገር በላይ የሚያስደስተኝ ቤዝቦል መጫወት ነበር!” (መጠበቂያ ግንብ ቁጥር 3 2017)

 ዳንኤል ምዕራፍ 4 ላይ የሚገኘው ትንቢት ስለ አምላክ መንግሥት እንደሚናገር ማወቅ የምንችለው እንዴት ነው?

“የአምላክ መንግሥት መግዛት የጀመረው መቼ ነው? (ክፍል 1)” (መጠበቂያ ግንብ ጥቅምት 1, 2014)

ዳንኤል ምዕራፍ 4 ላይ የተጠቀሱት ሰባት ዘመናት በ1914 እንዳበቁ የሚጠቁም ምን ማስረጃ አለ?

“የአምላክ መንግሥት መግዛት የጀመረው መቼ ነው? (ክፍል 2)” (መጠበቂያ ግንብ ኅዳር 1, 2014)

a በዚህ ምዕራፍ “ምርምር አድርግ” በሚለው ክፍል ሥር የተጠቀሱትን  የመጨረሻዎቹን ሁለት የማመሣከሪያ ጽሑፎች ተመልከት።