በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 37

መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ሥራና ስለ ገንዘብ ምን ይላል?

መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ሥራና ስለ ገንዘብ ምን ይላል?

የሥራና የገንዘብ ጉዳይ አስጨንቆህ ያውቃል? በአንድ በኩል ለይሖዋ የሚገባውን አምልኮ ማቅረብ፣ በሌላ በኩል ደግሞ ለኑሮ የሚያስፈልጉንን ነገሮች ማሟላት ፈታኝ ሊሆንብን ይችላል። መጽሐፍ ቅዱስ በዚህ ረገድ ሊረዳን የሚችል ጠቃሚ ምክር ይዟል።

1. መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ሥራ ምን ይላል?

አምላክ በሥራችን ደስተኛ እንድንሆን ይፈልጋል። መጽሐፍ ቅዱስ “ሰው . . . ተግቶ በመሥራት እርካታ ከማግኘት የሚሻለው ነገር የለም” ይላል። (መክብብ 2:24) ይሖዋ በትጋት ይሠራል። እኛም በትጋት በመሥራት ምሳሌውን ስንከተል እሱን የምናስደስት ከመሆኑም ሌላ እርካታ እናገኛለን።

ሥራ አስፈላጊ ነው። ሆኖም ሥራችን ለይሖዋ ከምናቀርበው አምልኮ የበለጠ ቦታ መያዝ የለበትም። (ዮሐንስ 6:27) ይሖዋ እሱን የምናስቀድመው ከሆነ ለኑሮ የሚያስፈልጉንን ነገሮች እንደሚያሟላልን ቃል ገብቷል።

2. ለገንዘብ ሊኖረን የሚገባው ሚዛናዊ አመለካከት ምንድን ነው?

መጽሐፍ ቅዱስ “ገንዘብ ጥበቃ እንደሚያስገኝ” ይናገራል፤ በሌላ በኩል ግን ገንዘብ ብቻውን ደስተኛ ሊያደርገን እንደማይችል ያስጠነቅቃል። (መክብብ 7:12) የአምላክ ቃል ገንዘብ እንዳንወድ፣ ከዚህ ይልቅ ‘ባሉን ነገሮች ረክተን እንድንኖር’ የሚያበረታታን ለዚህ ነው። (ዕብራውያን 13:5⁠ን አንብብ።) ባሉን ነገሮች ረክተን የምንኖር ከሆነ ‘ተጨማሪ ነገር ማግኘት አለብኝ’ የሚለው ስሜት ከሚያስከትለው ብስጭት ነፃ እንሆናለን። አላስፈላጊ ዕዳ ውስጥ ከመግባት እንድናለን። (ምሳሌ 22:7) በተጨማሪም ቁማር ከመጫወትና በአጭር ጊዜ ለመክበር ያስችላሉ የሚባሉ የንግድ አማራጮችን ከማሳደድ እንቆጠባለን።

3. ገንዘባችንን ከራስ ወዳድነት ነፃ በሆነ መንገድ ልንጠቀምበት የምንችለው እንዴት ነው?

ይሖዋ ለጋስ አምላክ ነው፤ እኛም “ለጋሶችና ለሌሎች ለማካፈል ዝግጁ” በመሆን የእሱን ምሳሌ እንከተላለን። (1 ጢሞቴዎስ 6:18) ጉባኤውን በመደገፍ እንዲሁም የተቸገሩ ሰዎችን በተለይ መንፈሳዊ ወንድሞቻችንንና እህቶቻችንን በመርዳት ገንዘባችንን ከራስ ወዳድነት ነፃ በሆነ መንገድ ልንጠቀምበት እንችላለን። ይሖዋ ትኩረት የሚያደርገው በምንሰጠው የገንዘብ መጠን ላይ ሳይሆን ለመስጠት በተነሳሳንበት ምክንያት ላይ ነው። ከልባችን በልግስና ስንሰጥ ደስተኞች እንሆናለን፤ ይሖዋንም እናስደስታለን።—የሐዋርያት ሥራ 20:35⁠ን አንብብ።

ጠለቅ ያለ ጥናት

ለሥራ ተገቢውን አመለካከት መያዝና ባሉን ነገሮች ረክቶ መኖር ያለውን ጥቅም እንመለከታለን።

4. ይሖዋን በሚያስከብር መንገድ ሥራህን አከናውን

ከይሖዋ ጋር የመሠረትነው ወዳጅነት ለሥራ ባለን አመለካከት ላይ ለውጥ ሊያመጣ ይገባል። ቪዲዮውን ተመልከቱ ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

  • በቪዲዮው ላይ ጄሰን ለሥራው ካለው አመለካከትና ከምግባሩ ጋር በተያያዘ አንተን ያስገረመህ ምንድን ነው?

  • ለሥራው ተገቢውን ቦታ እንዲሰጥ የረዳው ምንድን ነው?

ቆላስይስ 3:23, 24ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • ለሥራ ያለን አመለካከት ሊያሳስበን የሚገባው ለምንድን ነው?

ሥራ አስፈላጊ ነው። ሆኖም ሥራችን ለይሖዋ ከምናቀርበው አምልኮ የበለጠ ቦታ መያዝ የለበትም

5. ባሉን ነገሮች ረክተን መኖራችን ይጠቅመናል

በርካታ ሰዎች የቻሉትን ያህል ብዙ ገንዘብ ለማጠራቀም ይሞክራሉ። መጽሐፍ ቅዱስ ግን ከዚህ የተለየ ነገር እንድናደርግ ይመክረናል። አንደኛ ጢሞቴዎስ 6:6-8ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • መጽሐፍ ቅዱስ ምን እንድናደርግ ይመክረናል?

ያለን ገንዘብ በጣም አነስተኛ ቢሆንም እንኳ ደስተኛ መሆን እንችላለን። ቪዲዮውን ተመልከቱ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • በቪዲዮው ላይ የታዩት ቤተሰቦች ያላቸው ገንዘብ ጥቂት ቢሆንም ደስተኛ እንዲሆኑ የረዳቸው ምንድን ነው?

ብዙ ገንዘብ እያለንም ተጨማሪ ገንዘብ ለማግኘት የምንፈልግ ቢሆንስ? ኢየሱስ ይህ ያለውን አደጋ የሚያሳይ ምሳሌ ተናግሯል። ሉቃስ 12:15-21ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • ኢየሱስ ከሰጠው ምሳሌ ምን ትምህርት አግኝተሃል?—ቁጥር 15⁠ን ተመልከት።

ምሳሌ 10:22ን እና 1 ጢሞቴዎስ 6:10ን አንብቡና አወዳድሩ። ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

  • ይበልጥ አስፈላጊ የሆነው ምን ይመስልሃል? የይሖዋ ወዳጅ መሆን ወይስ ብዙ ገንዘብ ማግኘት? እንዲህ ብለህ የመለስከው ለምንድን ነው?

  • ገንዘብ ማሳደድ ምን ችግሮች ሊያስከትል ይችላል?

6. ይሖዋ የሚያስፈልጉንን ነገሮች ያሟላልናል

ከሥራና ከገንዘብ ጋር በተያያዘ ችግር ሲያጋጥመን በይሖዋ ላይ ያለን እምነት ሊፈተን ይችላል። እንዲህ ያሉ የእምነት ፈተናዎችን መወጣት የምንችለው እንዴት እንደሆነ ለማወቅ ቪዲዮውን ተመልከቱ ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

  • በቪዲዮው ላይ ወንድም ምን ችግሮች አጋጥመውታል?

  • እነዚህን ችግሮች በተሳካ ሁኔታ መወጣት የቻለው እንዴት ነው?

ማቴዎስ 6:25-34ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • ይሖዋ እሱን ለሚያስቀድሙ ሰዎች ምን እንደሚያደርግ ቃል ገብቷል?

አንዳንዶች እንዲህ ይላሉ፦ “ቤተሰቤን ለማስተዳደር ጠንክሬ መሥራት አለብኝ። በየሳምንቱ የጉባኤ ስብሰባዎች ላይ መገኘት አልችልም።”

  • ለይሖዋ የምታቀርበውን አምልኮ ማስቀደም ከሁሉ የተሻለ ውሳኔ እንደሆነ እርግጠኛ እንድትሆን የሚያደርግህ የትኛው ጥቅስ ነው?

ማጠቃለያ

ሥራና ገንዘብ አስፈላጊ ነገሮች ናቸው፤ ሆኖም ይሖዋን እንዳናገለግል እንቅፋት ሊሆኑብን አይገባም።

ክለሳ

  • ለሥራ ሚዛናዊ አመለካከት ለመያዝ የሚረዳህ ምንድን ነው?

  • ባሉህ ነገሮች ረክተህ መኖርህ ምን ጥቅም ያስገኝልሃል?

  • ይሖዋ ሕዝቡን እንደሚንከባከብ በገባው ቃል ላይ እምነት እንዳለህ ማሳየት የምትችለው እንዴት ነው?

ግብ

ምርምር አድርግ

መጽሐፍ ቅዱስ ገንዘብ በራሱ መጥፎ እንደሆነ ያስተምራል?

“ገንዘብ የክፋት ሁሉ ሥር ነው?” (ድረ ገጻችን ላይ የወጣ ርዕስ)

ገንዘባችንን አምላክን በሚያስደስት መልኩ መጠቀም የምንችለው እንዴት ነው?

“መስጠትን በተመለከተ መጽሐፍ ቅዱስ ምን ይላል?” (ድረ ገጻችን ላይ የወጣ ርዕስ)

ቁማር ምንም ጉዳት የሌለው መዝናኛ ነው?

“መጽሐፍ ቅዱስ ምን ይላል?—ቁማር” (ንቁ! መጋቢት 2015)

ቁማርተኛና ዘራፊ የነበረ አንድ ሰው ማስተካከያ ለማድረግ የተነሳሳው ለምንድን ነው?

“የፈረስ ግልቢያ ውድድር በጣም እወድ ነበር” (መጠበቂያ ግንብ ኅዳር 1, 2011)