በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 51

በንግግርህ ይሖዋን ማስደሰት የምትችለው እንዴት ነው?

በንግግርህ ይሖዋን ማስደሰት የምትችለው እንዴት ነው?

ይሖዋ ሲፈጥረን ልዩ ስጦታ ሰጥቶናል፤ ይህ ስጦታ የመናገር ችሎታ ነው። ይህን ስጦታ የምንጠቀምበት መንገድ አምላክን ያሳስበዋል? አዎ፣ ያሳስበዋል! (ያዕቆብ 1:26⁠ን አንብብ።) ታዲያ የመናገር ችሎታችንን ይሖዋን በሚያስደስት መንገድ ልንጠቀምበት የምንችለው እንዴት ነው?

1. ይሖዋ የሰጠንን የመናገር ችሎታ እንዴት ልንጠቀምበት ይገባል?

መጽሐፍ ቅዱስ “እርስ በርስ ተበረታቱ እንዲሁም እርስ በርስ ተናነጹ” የሚል ምክር ይሰጠናል። (1 ተሰሎንቄ 5:11) ማበረታቻ የሚያስፈልገው ሰው ታውቃለህ? ግለሰቡን ለማበረታታት ምን ማለት ትችላለህ? ከልብ እንደምታስብለት ንገረው። ምናልባትም የምታደንቅለትን ነገር ልትነግረው ትችል ይሆናል። ግለሰቡን ለማበረታታት የትኛውን የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ ልትጠቀም ትችላለህ? በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ብዙ የሚያበረታቱ ጥቅሶች አሉ። በተጨማሪም የምትናገርበት መንገድ ከምትናገረው ነገር ያልተናነሰ ኃይል እንዳለው አስታውስ። እንግዲያው ሁሌም በለዘበና ደግነት በሚንጸባረቅበት መንገድ ለመናገር ጥረት አድርግ።—ምሳሌ 15:1

2. ምን ዓይነት አነጋገሮችን ልናስወግድ ይገባል?

መጽሐፍ ቅዱስ “የበሰበሰ ቃል ከቶ ከአፋችሁ አይውጣ” ይላል። (ኤፌሶን 4:29⁠ን አንብብ።) ይህም ሲባል ጸያፍ የሆነ፣ አሳቢነት የጎደለው ወይም ሌሎችን ቅር የሚያሰኝ ነገር መናገር አይኖርብንም ማለት ነው። በተጨማሪም ከሐሜትና ስም ከማጥፋት ልንቆጠብ ይገባል።—ምሳሌ 16:28⁠ን አንብብ።

3. ሌሎችን በሚያበረታታ መንገድ ለመናገር ምን ይረዳናል?

አብዛኛውን ጊዜ የምንናገረው ነገር በልባችን ውስጥ ያለውን ወይም የምናስበውን ነገር ያንጸባርቃል። (ሉቃስ 6:45) በመሆኑም ጥሩ በሆኑ ነገሮች ላይ ማለትም ጽድቅ፣ ንጹሕና ተወዳጅ በሆኑ እንዲሁም በመልካም በሚነሱ ነገሮች ላይ ለማተኮር ራሳችንን ማሠልጠን ያስፈልገናል። (ፊልጵስዩስ 4:8) በእነዚህ ነገሮች ላይ ለማተኮር በመዝናኛና በጓደኛ ምርጫችን ረገድ ጠንቃቆች መሆን አለብን። (ምሳሌ 13:20) በተጨማሪም ከመናገራችን በፊት ማሰባችን ይረዳናል። የምትናገረው ነገር በሌሎች ላይ ምን ስሜት እንደሚያሳድር አስብ። መጽሐፍ ቅዱስ “ሳይታሰብበት የሚነገር ቃል እንደ ሰይፍ ይወጋል፤ የጥበበኞች ምላስ ግን ፈውስ ነው” ይላል።—ምሳሌ 12:18

ጠለቅ ያለ ጥናት

አነጋገርህ ይሖዋን የሚያስደስትና ሌሎችን የሚያበረታታ እንዲሆን ማድረግ የምትችለው እንዴት እንደሆነ እንመለከታለን።

4. አንደበትህን ተቆጣጠር

ሁላችንም በኋላ ላይ የምንቆጭበትን ነገር የምንናገርበት ጊዜ አለ። (ያዕቆብ 3:2) ገላትያ 5:22, 23ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

  • አንደበትህን መቆጣጠር እንድትችል እዚህ ጥቅስ ላይ ከተጠቀሱት ባሕርያት መካከል የትኞቹን ለማዳበር ልትጸልይ ትችላለህ? እነዚህን ባሕርያት ማዳበርህ የሚጠቅምህ እንዴት ነው?

አንደኛ ቆሮንቶስ 15:33ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • የጓደኛና የመዝናኛ ምርጫህ በአነጋገርህ ላይ ምን ተጽዕኖ ሊያሳድር ይችላል?

መክብብ 3:1, 7ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • ዝም ማለታችን ወይም አመቺ ጊዜ ጠብቀን መናገራችን የተሻለ የሚሆንባቸው አንዳንድ ሁኔታዎች የትኞቹ ናቸው?

5. ስለ ሌሎች ጥሩ ነገር ተናገር

ሌሎችን የሚጎዳና ደግነት የጎደለው ነገር እንዳንናገር ምን ይረዳናል? ቪዲዮውን ተመልከቱ ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

  • በቪዲዮው ላይ የታየው ወንድም ስለ ሌሎች በሚናገርበት መንገድ ላይ ማስተካከያ ማድረግ የፈለገው ለምንድን ነው?

  • ለውጥ ለማድረግ ምን እርምጃዎች ወሰደ?

መክብብ 7:16ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • ስለ አንድ ሰው መጥፎ ነገር ለማውራት ስንፈተን ምን ማስታወስ ይኖርብናል?

መክብብ 7:21, 22ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • ይህ ጥቅስ አንድ ሰው ስለ አንተ መጥፎ ነገር ሲያወራ እንዳትበሳጭ የሚረዳህ እንዴት ነው?

6. ቤተሰብህን ደግነት በሚንጸባረቅበት መንገድ አነጋግር

ይሖዋ ቤተሰቦቻችንን ፍቅርና ደግነት በሚንጸባረቅበት መንገድ እንድናነጋግር ይፈልጋል። ቪዲዮውን ተመልከቱ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • ቤተሰብህን ደግነት በሚንጸባረቅበት መንገድ ለማነጋገር ምን ይረዳሃል?

ኤፌሶን 4:31, 32ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • በቤተሰብ መካከል ጥሩ መንፈስ እንዲሰፍን የሚያደርገው ምን ዓይነት አነጋገር ነው?

ይሖዋ ለልጁ ለኢየሱስ ያለውን ፍቅር ገልጿል። ማቴዎስ 17:5ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • ቤተሰብህን ከምታነጋግርበት መንገድ ጋር በተያያዘ ይሖዋን መምሰል የምትችለው እንዴት ነው?

ለሌሎች አድናቆትህን ለመግለጽ የሚያስችሉህን አጋጣሚዎች ፈልግ

አንዳንዶች እንዲህ ይላሉ፦ “የምናገረው የሚሰማኝን ነው። ሌሎች ቅር ቢሰኙም ምንም ማድረግ አልችልም።”

  • አንተ በዚህ ሐሳብ ትስማማለህ? እንዲህ ብለህ የመለስከው ለምንድን ነው?

ማጠቃለያ

የምንናገረው ነገር ትልቅ ኃይል አለው። ስለዚህ ምን እንደምንናገር፣ መቼ እንደምንናገር እና እንዴት እንደምንናገር በጥንቃቄ ልናስብ ይገባል።

ክለሳ

  • በንግግርህ ሌሎችን ማበረታታት የምትችልባቸው አንዳንድ መንገዶች የትኞቹ ናቸው?

  • ምን ዓይነት አነጋገሮችን ልታስወግድ ይገባል?

  • ንግግራችን ምንጊዜም ደግነት የሚንጸባረቅበትና ሌሎችን የሚያበረታታ እንዲሆን ምን ይረዳናል?

ግብ

ምርምር አድርግ

ሌሎችን በሚያበረታታ መንገድ ለመናገር ምን ይረዳናል?

የጥበበኞች ምላስ ይኑራችሁ (8:04)

መጥፎ አነጋገርን ለማስወገድ ምን ሊረዳህ ይችላል?

“መሳደብ ያን ያህል መጥፎ ነገር ነው?” (ድረ ገጻችን ላይ የወጣ ርዕስ)

ሐሜትን ለማስወገድ የሚረዳህ ምንድን ነው?

ሐሜትን ማስወገድ የምችለው እንዴት ነው? (2:36)

ተሳዳቢ የነበረ አንድ ሰው በይሖዋ እርዳታ ለውጥ ማድረግ የቻለው እንዴት እንደሆነ ተመልከት።

“ሕይወቴ ወዴት አቅጣጫ እያመራ እንደሆነ በቁም ነገር ማሰብ ጀመርኩ” (መጠበቂያ ግንብ ነሐሴ 1, 2013)