በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 58

ምንጊዜም ለይሖዋ ታማኝ ሁን

ምንጊዜም ለይሖዋ ታማኝ ሁን

እውነተኛ ክርስቲያኖች የትኛውም ነገር ወይም ማንኛውም አካል ለይሖዋ በሚያቀርቡት አምልኮ ላይ እንቅፋት እንዲፈጥርባቸው አይፈቅዱም። አንተም እንዲህ እንደሚሰማህ እርግጠኞች ነን። ይሖዋ ለእሱ የምታሳየውን ታማኝነት ከፍ አድርጎ ይመለከታል። (1 ዜና መዋዕል 28:9⁠ን አንብብ።) ለይሖዋ ያለህን ታማኝነት ሊፈትኑ የሚችሉ አንዳንድ ሁኔታዎች የትኞቹ ናቸው? እነዚህን ሁኔታዎች መወጣት የምትችለውስ እንዴት ነው?

1. ሌሎች ሰዎች ለይሖዋ ያለንን ታማኝነት ሊፈትኑት የሚችሉት እንዴት ነው?

አንዳንድ ሰዎች ይሖዋን ማገልገላችንን እንድናቆም ለማድረግ ይሞክራሉ። እንዲህ ለማድረግ የሚሞክሩት እነማን ናቸው? ከእውነት ቤት የወጡ አንዳንድ ሰዎች እምነታችንን ለማዳከም ሲሉ ስለ አምላክ ድርጅት ውሸት ይናገራሉ። እንዲህ ያሉት ሰዎች ከሃዲዎች ተብለው ይጠራሉ። በተጨማሪም አንዳንድ የሃይማኖት መሪዎች ስለ እኛ የሐሰት መረጃዎችን በማናፈስ አስተዋይ ያልሆኑ ሰዎች ከእውነት ቤት እንዲወጡ ለማድረግ ይሞክራሉ። እንዲህ ካሉ ተቃዋሚዎች ጋር መከራከር እንዲሁም ጽሑፋቸውን ማንበብ፣ ድረ ገጻቸውን መጎብኘት ወይም ቪዲዮዎቻቸውን መመልከት አደገኛ ነው። ኢየሱስ ሌሎች ይሖዋን በታማኝነት እንዳያገለግሉ እንቅፋት የሚፈጥሩ ሰዎችን አስመልክቶ እንዲህ ብሏል፦ “ተዉአቸው፤ እነሱ ዕውር መሪዎች ናቸው። ስለዚህ ዕውር ዕውርን ቢመራ ሁለቱም ጉድጓድ ውስጥ ይወድቃሉ።”ማቴዎስ 15:14

አንድ የምናውቀው ሰው ይሖዋን ማገልገሉን ለማቆም ቢወስንስ? የምንቀርበው ሰው እንዲህ ያለ ውሳኔ ማድረጉ በጣም ሊያሳዝነን ይችላል። ይህ ሰው ከእሱና ከይሖዋ አንዱን እንድንመርጥ ሊያስገድደን ይሞክር ይሆናል። እንዲህ ያለ ሁኔታ ሲያጋጥመን ከማንም በላይ ለይሖዋ ታማኝ ለመሆን ቁርጥ ውሳኔ ማድረግ አለብን። (ማቴዎስ 10:37) ይሖዋ እንዲህ ካሉ ሰዎች ጋር እንዳንቀራረብ የሰጠንን ትእዛዝ እንፈጽማለን።—1 ቆሮንቶስ 5:11⁠ን አንብብ።

2. የምናደርጋቸው ውሳኔዎች ለይሖዋ ያለንን ታማኝነት ሊያሳዩ የሚችሉት እንዴት ነው?

ለይሖዋ ያለን ፍቅር ከሐሰት ሃይማኖት ጋር ምንም ዓይነት ንክኪ እንዳይኖረን እንድንጠነቀቅ ያነሳሳናል። ሥራችን፣ የምንካፈልበት እንቅስቃሴ አሊያም አባል የሆንበት ድርጅት ከሐሰት ሃይማኖት ጋር ምንም ንክኪ ሊኖረው አይገባም። ይሖዋ ‘ሕዝቤ ሆይ፣ ከታላቂቱ ባቢሎን ውጡ’ በማለት አስጠንቅቆናል።—ራእይ 18:2, 4

ጠለቅ ያለ ጥናት

ማንም ሰው ለይሖዋ ያለህን ታማኝነት እንዳያዳክመው መጠንቀቅ የምትችለው እንዴት እንደሆነ እንመለከታለን። በተጨማሪም ከታላቂቱ ባቢሎን በመውጣት ታማኝነትህን ማሳየት የምትችለው እንዴት እንደሆነ እንመረምራለን።

3. ሐሰተኛ አስተማሪዎች እንዳያታልሉህ ተጠንቀቅ

ስለ ይሖዋ ድርጅት መጥፎ ነገር ብንሰማ ምን ማድረግ ይኖርብናል? ምሳሌ 14:15ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • የምንሰማውን ነገር ሁሉ ማመን የሌለብን ለምንድን ነው?

ሁለተኛ ዮሐንስ 10ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

  • ከሃዲዎችን በተመለከተ ምን አቋም ሊኖረን ይገባል?

  • ከከሃዲዎች ጋር በአካል ባንገናኝ እንኳ እነሱ ለሚያስተምሩት ትምህርት ልንጋለጥ የምንችልባቸው አንዳንድ መንገዶች የትኞቹ ናቸው?

  • ይሖዋ ስለ እሱ ወይም ስለ ድርጅቱ ለሚነገር መጥፎ ወሬ ጆሮ ብንሰጥ ምን የሚሰማው ይመስልሃል?

4. አንድ ወንድም ኃጢአት በሚሠራበት ጊዜ ለአምላክ ታማኝ እንደሆንክ አሳይ

በጉባኤ ውስጥ ያለ አንድ ሰው ከባድ ኃጢአት እንደፈጸመ ካወቅን ምን የማድረግ ግዴታ አለብን? አምላክ ለጥንቶቹ እስራኤላውያን የሰጠው ሕግ ምን ማድረግ እንዳለብን ይጠቁመናል። ዘሌዋውያን 5:1ን አንብቡ።

እዚህ ጥቅስ ላይ እንደተገለጸው አንድ ሰው ከባድ ኃጢአት እንደፈጸመ ከተገነዘብን የምናውቀውን ነገር ለሽማግሌዎች መናገር ይኖርብናል። ሆኖም እንዲህ ከማድረጋችን በፊት ግለሰቡ ራሱ ወደ ሽማግሌዎች ሄዶ ኃጢአቱን እንዲናዘዝ በማበረታታት ደግነት ማሳየታችን ተገቢ ነው። እንዲህ ካላደረገ ግን ለይሖዋ ያለን ታማኝነት የምናውቀውን ነገር ለሽማግሌዎች እንድንናገር ሊያነሳሳን ይገባል። ይህን እርምጃ መውሰዳችን . . .

  • ለይሖዋ አምላክ ያለንን ፍቅር የሚያሳየው እንዴት ነው?

  • ኃጢአት ለሠራው ግለሰብ ያለንን ፍቅር የሚያሳየው እንዴት ነው?

  • በጉባኤው ውስጥ ላሉ ሌሎች ሰዎች ያለንን ፍቅር የሚያሳየው እንዴት ነው?

አንድ ክርስቲያን ችግር ካጋጠመው እርዳው!

5. ከታላቂቱ ባቢሎን ጋር ምንም ንክኪ እንዳይኖርህ ተጠንቀቅ

ሉቃስ 4:8ን እና ራእይ 18:4, 5ን አንብቡ፤ ከዚያም የሚከተሉትን ጥያቄዎች ለመመለስ ሞክር፦

  • ስሜ አሁንም በሐሰት ሃይማኖት አባላት ስም ዝርዝር ውስጥ ይገኛል?

  • ከሌላ ሃይማኖት ጋር ንክኪ ያለው ድርጅት አባል ነኝ?

  • የምሠራው ሥራ በሆነ መንገድ ለሐሰት ሃይማኖት ድጋፍ የሚሰጥ ነው?

  • በሕይወቴ ውስጥ ከሐሰት ሃይማኖት ጋር ሊያነካኩኝ የሚችሉ ሌሎች አቅጣጫዎች ይኖሩ ይሆን?

  • ከእነዚህ ጥያቄዎች መካከል ለአንዱም እንኳ ‘አዎ’ የሚል መልስ ከሰጠሁ ምን ለውጥ ማድረግ ይኖርብኛል?

በማንኛውም ሁኔታ ሥር ሕሊናህን የማይረብሽና ለይሖዋ ያለህን ታማኝነት የሚያሳይ ውሳኔ አድርግ።

አንድ ሃይማኖት ለሚያከናውነው የበጎ አድራጎት ሥራ ገንዘብ እንድታዋጣ ብትጠየቅ ምን ታደርጋለህ?

አንዳንዶች እንዲህ ይላሉ፦ “ለእውነት ጥብቅና መቆም እንድችል ከሃዲዎች ስለ ይሖዋ ምሥክሮች ምን እንደሚሉ ማወቅ አለብኝ።”

  • እንዲህ ማድረግ ጥሩ ነው ትላለህ? እንዲህ ብለህ የመለስከው ለምንድን ነው?

ማጠቃለያ

ለይሖዋ ምንጊዜም ታማኝ ለመሆን ለእሱ ታማኝ ካልሆኑ ሰዎች መራቅ ይኖርብናል። በተጨማሪም ከሐሰት ሃይማኖት ጋር ምንም ዓይነት ንክኪ እንዳይኖረን መጠንቀቅ ያስፈልገናል።

ክለሳ

  • ከሃዲዎች የሚያወጡትን ቪዲዮ መመልከት፣ ጽሑፎቻቸውን ማንበብ እንዲሁም ለሚያናፍሱት ወሬ ጆሮ መስጠት የሌለብን ለምንድን ነው?

  • የይሖዋ ምሥክሮች ከነበሩ ሆኖም ይሖዋን ማገልገላቸውን ለማቆም ከወሰኑ ሰዎች ጋር ምን ዓይነት ግንኙነት ሊኖረን ይገባል?

  • ከሐሰት ሃይማኖት እንድንወጣ የተሰጠንን ማስጠንቀቂያ እንደምንታዘዝ ማሳየት የምንችለው በየትኞቹ መንገዶች ነው?

ግብ

ምርምር አድርግ

ስለ ይሖዋ ምሥክሮች የሐሰት ወሬ የሚያናፍሱ ሰዎች ሲያጋጥሙህ ምን እርምጃ መውሰድ ይኖርብሃል?

“የተሟላ መረጃ አለህ?” (መጠበቂያ ግንብ ነሐሴ 2018)

ታላቂቱ ባቢሎንን የሚደግፉ ድርጅቶችን ወይም እንቅስቃሴዎችን ለይተህ ማወቅ የምትችለው እንዴት ነው?

“‘በመጨረሻዎቹ ቀናት’ መጨረሻ ሥራ የበዛላችሁ ሁኑ” (መጠበቂያ ግንብ ጥቅምት 2019 አንቀጽ 16-18)

አንዳንድ ተቃዋሚዎች እምነታችንን ለማዳከም ምን ዘዴ ይጠቀማሉ?

እንዳትታለሉ ተጠንቀቁ (9:32)

“ከልጅነቴ ጀምሮ አምላክን ስፈልግ ኖሬያለሁ” የሚል ርዕስ ባለው የሕይወት ታሪክ ላይ የሺንቶ ሃይማኖት ካህን የነበረ አንድ ሰው ከሐሰት ሃይማኖት ጋር የነበረውን ግንኙነት ያቋረጠው እንዴት እንደሆነ ተመልከት።

“መጽሐፍ ቅዱስ የሰዎችን ሕይወት ይለውጣል” (መጠበቂያ ግንብ ሐምሌ 1, 2011)