በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

መከር ከመድረሱ በፊት “በእርሻው” ውስጥ መሥራት

መከር ከመድረሱ በፊት “በእርሻው” ውስጥ መሥራት

መከር ከመድረሱ በፊት “በእርሻው” ውስጥ መሥራት

የታላቁ አስተማሪ ደቀ መዛሙርት ግራ ተጋብተው ነበር። ኢየሱስ ስለ ስንዴና ስለ እንክርዳድ የሚገልጽ አጭር ታሪክ ተናግሮ ገና ማብቃቱ ነበር። ይህ ታሪክ በዚያ ዕለት ከተናገራቸው ብዙ ምሳሌዎች መካከል አንዱ ነው። ተናግሮ እንዳበቃ ሲያዳምጡት ከነበሩት መካከል ብዙዎቹ ሄዱ። ተከታዮቹ ግን ኢየሱስ የተናገራቸው ምሳሌዎች የየራሳቸው ትርጉም እንዳላቸው ተገንዝበው ነበር። በተለይ ደግሞ ስለ ስንዴና እንክርዳድ የተናገረውን ምሳሌ ትርጉም ለማወቅ ፈልገዋል። ኢየሱስ እንዲሁ ደስ የሚሉ ተረቶችን የሚያወራ ሰው እንዳልሆነ ያውቁ ነበር።

ማቴዎስ “የእርሻውን እንክርዳድ ምሳሌ ተርጉምልን” ብለው እንደጠየቁት ዘግቧል። ኢየሱስም በደቀ መዛሙርቱ መካከል ታላቅ ክህደት እንደሚነሳ በመተንበይ የምሳሌውን ትርጉም ፈታላቸው። (ማቴዎስ 13:​24-30, 36-38, 43) እንደተባለው ክህደቱ የተነሳ ሲሆን ሐዋርያው ዮሐንስ ከሞተ በኋላ በፍጥነት ተስፋፍቷል። (ሥራ 20:​29, 30፤ 2 ተሰሎንቄ 2:​6-12) ክህደቱ የሚያስከትለው ውጤት ብዙዎችን የሚበክል ስለነበር በሉቃስ 18:​8 ላይ ተመዝግቦ የሚገኘው “የሰው ልጅ በመጣ ጊዜ በምድር እምነትን ያገኝ ይሆንን?” በማለት ኢየሱስ ያነሳው ጥያቄ ተገቢ ነበር።

የኢየሱስ መምጣት በስንዴ የተመሰሉት ክርስቲያኖች “መከር” የደረሰ መሆኑን ያሳያል። ይህ ደግሞ በ1914 የጀመረው ‘የዚህ የነገሮች ሥርዓት መደምደሚያ’ ምልክት ይሆናል። ስለዚህ መከሩ ወደሚጀምርበት ጊዜ እያመሩ ባሉ ዓመታት ለመጽሐፍ ቅዱስ እውነት ከፍተኛ ፍላጎት ያደረባቸው ሰዎች መነሳታቸው ሊያስደንቀን አይገባም።​—⁠ማቴዎስ 13:​39

የታሪክ መዛግብት እንደሚያሳዩት በተለይ ከ15ኛው መቶ ዘመን ወዲህ “በእንክርዳድ” በተመሰሉት ወይም አስመሳይ ክርስቲያኖችን ባቀፈው የሕዝበ ክርስትና አባላት ዘንድ ሳይቀር እውነትን የማወቅ ጉጉት ጨምሮ ነበር። መጽሐፍ ቅዱስን እንደ ልብ ማግኘት በመቻሉና የመጽሐፍ ቅዱስ ማጣቀሻዎች (ኮንኮርዳንስ) በመዘጋጀታቸው ቅን ልብ ያላቸው ግለሰቦች ቅዱሳን ጽሑፎችን በጥንቃቄ መመርመር ጀመሩ።

ብርሃኑ እየደመቀ መጣ

ከእነዚህ ሰዎች መካከል አንዱ በ19ኛው መቶ ዘመን መባቻ ላይ በእንግሊዝ በበርሚንግሃም ይኖር የነበረው ሄንሪ ግሪው (1781-1862) ነው። በአሥራ ሦስት ዓመቱ ከቤተሰቦቹ ጋር በመርከብ አትላንቲክ ውቅያኖስን በማቋረጥ ሐምሌ 8, 1795 ዩናይትድ ስቴትስ ደረሰ። እዚያም በሮዴ ደሴት በፕሮቪደንስ መኖር ጀመሩ። ወላጆቹ ለመጽሐፍ ቅዱስ ፍቅር ቀርጸውበታል። በ1807 በ25 ዓመቱ በሃርትፎርድ ኮኔክቲከት በሚገኘው የባፕቲስት ቤተ ክርስቲያን ቄስ ሆኖ እንዲያገለግል ተጋብዞ ነበር።

የማስተማር ኃላፊነቱን በቁም ነገር ይመለከተው የነበረ ሲሆን በሥሩ የሚገኙት ሰዎች ከቅዱሳን ጽሑፎች ጋር ተስማምተው እንዲኖሩ ለመርዳት ጥሯል። ይሁን እንጂ ሆነ ብለው ኃጢአት ከሚሠሩ ሰዎች ጉባኤውን ንጹሕ ማድረግ እንዳለበት ያምን ነበር። አንዳንድ ጊዜ እሱና በቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ ያሉ ኃላፊነት ያላቸው ሰዎች ዝሙት የሚፈጽሙትን ወይም በሌሎች ርኩስ ድርጊቶች የሚጠላለፉ ሰዎችን ያገልሉ (ያስወግዱ) ነበር።

በቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ ሄንሪን የሚረብሹት ሌሎች ችግሮችም ነበሩ። የቤተ ክርስቲያኑ ጉዳይ አስፈጻሚ ሆነው የሚሠሩትና መዝሙር ሲዘመር የሚመሩት የቤተ ክርስቲያን አባላት ያልሆኑ ሰዎች ነበሩ። እነዚህ ሰዎች ጉባኤውን የሚመለከት ድምፀ ውሳኔ በሚደረግበት ጊዜ ድምፅ መስጠት ይችሉ የነበረ ሲሆን እንዲያውም አንዳንድ ጉዳዮችን በቁጥጥራቸው ሥር አድርገው ነበር። ከዓለም መለየት በሚለው መሠረታዊ ሥርዓት መሠረት እነዚህ ኃላፊነቶች መከናወን ያለባቸው ታማኝ በሆኑ ሰዎች ብቻ እንደሆነ አጥብቆ ያምን ነበር። (2 ቆሮንቶስ 6:​14-18፤ ያዕቆብ 1:​27) የማያምኑ ሰዎች አምላክን የሚያወድሱ መዝሙሮች መዘመራቸውን አምላክን እንደ መሳደብ አድርጎ ይቆጥረው ነበር። ሄንሪ ግሪው በዚህ አቋሙ ምክንያት በ1811 በቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ የነበረውን ተቀባይነት አጣ። በዚህ ጊዜ ተመሳሳይ አመለካከት የነበራቸው ሌሎች አባላትም ከቤተ ክርስቲያን ተለዩ።

ከሕዝበ ክርስትና መለየት

ሄንሪ ግሪው እና ይህ ቡድን ሕይወታቸውንና ተግባራቸውን ከምክሩ ጋር ለማስማማት በማሰብ መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናት ጀመሩ። ጥናታቸው የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት ይበልጥ እንዲረዱና የሕዝበ ክርስትናን ስሕተቶች እንዲያጋልጡ አድርጓቸዋል። ለምሳሌ ያህል ግሪው በ1824 የሥላሴ መሠረተ ትምህርት ስሕተት መሆኑን በጥሩ ሁኔታ የሚያስረዳ ጽሑፍ አዘጋጅቶ ነበር። እሱ ካዘጋጀው ጽሑፍ ላይ የተወሰደውን ምክንያታዊ አቀራረብ ተመልከት:- “‘ያንን ቀን ግን ያችንም ሰዓት ማንም ሰው አያውቅም። በሰማይ የሚኖሩ መላእክትም ቢሆኑ ልጅም ቢሆን ከአብ በቀር።’ [ማርቆስ 13:​32] እዚህ ላይ ደረጃው በቅደም ተከተል መቀመጡን ልብ በሉ። ሰው፣ መላእክት፣ ልጅ፣ አብ። . . . ስለዚያች ቀን የሚያውቀው አብ ብቻ መሆኑን ጌታችን አስተምሮናል። ሆኖም አንዳንዶች አብ፣ ቃልና መንፈስ ቅዱስ በአንድ አምላክ ውስጥ ያሉ ሦስት አካላት ናቸው እንደሚሉት ከሆነ ጌታ ያለው እውነት ላይሆን ነው፤ እንደዚህ [እንደ ሥላሴ መሠረተ ትምህርት] ከሆነ . . . ልጅ ከአብ እኩል ስለ መጨረሻው ቀን ያውቃል።”

ግሪው ለክርስቶስ የይስሙላ አገልግሎት የሚያቀርቡትን ቀሳውስትና ወታደራዊ አዛዦች ግብዝነት አጋልጧል። በ1828 እንዲህ ሲል ተናግሮ ነበር:- “አንድ ክርስቲያን ለጠላቶቹ ከሚጸልይበት እልፍኝ ወጥቶ ወታደሮቹ መሣሪያቸውን በእነዚያው ሲጸልይላቸው በነበሩ ጠላቶቹ ልብ ውስጥ በጭካኔ እንዲሰኩ ትእዛዝ የሚሰጥ ከሆነ ልንቀበለው የማንችለው ከዚህ የበለጠ ነገር ይኖራልን? በአንድ በኩል ለሞት ሲያጣጥር የነበረውን ጌታውን ለመምሰል ይሞክራል፤ በሌላ በኩልስ ማንን ይመስላል? ኢየሱስ ለሚገድሉት ሰዎች ጸልዮአል። ክርስቲያኖች ግን ለጠላቶቻቸው ሲጸልዩ ቆይተው እነርሱው ጠላቶቻቸውን ይገድላሉ።”

እንዲያውም ጠበቅ አድርጎ ሲናገር እንዲህ ብሏል:- “ፈጽሞ ‘እንደማይዘበትበት’ የተናገረውን ሁሉን ቻይ አምላክ የምናምነው መቼ ነው? ‘ሙሉ በሙሉ ከክፋት’ እንድንርቅ የሚያዘውን የቅዱሱን ሃይማኖት ባሕርይና ምንነት የምንረዳው መቼ ነው? . . . ሃይማኖቱ በአንድ በኩል የመልአክ በሌላ በኩል ደግሞ የጋኔን ተግባር መፈጸምን እንደሚፈቅድ አድርጎ ማሰብ የብሩኩን አምላክ ልጅ ስም ማጥፋት አይሆንምን?”

ዘላለማዊነት የግድ በተፈጥሮ ያለ ነገር አይደለም

ሬዲዮ እና ቴሌቪዥን ከመፈልሰፋቸው በፊት አመለካከትን ለመግለጽ በሰፊው ጥቅም ላይ የዋለው ዘዴ በራሪ ወረቀቶችን አዘጋጅቶ ማሰራጨት ነበር። በ1835 ገደማ ግሪው የሰው ነፍስ አትሞትም እና ሲኦል መቃጠያ ቦታ ነው የሚሉት ትምህርቶች ቅዱስ ጽሑፋዊ አለመሆናቸውን የሚያጋልጥ በራሪ ወረቀት አዘጋጅቶ ነበር። እነዚህ መሠረተ ትምህርቶች አምላክን የሚሳደቡ እንደሆኑ ተሰምቶት ነበር።

ይህ በራሪ ወረቀት በሰፊው ለመሰራጨት በቅቷል። በ1837 የ40 ዓመቱ ጆርጅ ስቶርዝ ባቡር ላይ ይህን በራሪ ወረቀት አገኘ። ስቶርዝ የሊባኖስ ተወላጅ ሲሆን በወቅቱ በዩቲካ ኒው ዮርክ ይኖር ነበር።

በሜቶዲስት ኤፒስኮፓል ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በጣም የተከበረ አገልጋይ ነበር። በራሪ ወረቀቱ እሱ ሙሉ በሙሉ ያምንባቸው የነበሩት እነዚህ የሕዝበ ክርስትና መሠረታዊ ትምህርቶች ትክክል እንዳልሆኑ የሚገልጽ ጠንካራ ማስረጃ እንዳቀረበ ሲረዳ ተደነቀ። በ1844 ገደማ ሁለቱም በፊላደልፊያ ፔንሲልቫኒያ መኖር እስከጀመሩበትና እስከተገናኙበት ጊዜ ድረስ የዚህ በራሪ ወረቀት ደራሲ ማን እንደሆነ አያውቅም ነበር። ይሁን እንጂ ስቶርዝ ስለተረዳው ነገር ከሌሎች አገልጋዮች ጋር ብቻ እየተነጋገረ ጉዳዩን ለሦስት ዓመታት በግሉ ሲያጠና ቆየ።

በመጨረሻ ጆርጅ ስቶርዝ እየተማረ የነበረውን ነገር ማንም ውድቅ ማድረግ ስላልቻለ ሜቶዲስት ቤተ ክርስቲያንን ለቅቆ ካልወጣ ለአምላክ ታማኝ መሆን እንደማይችል አሰበ። በ1840 ቤተ ክርስቲያኑን በገዛ ፈቃዱ ከለቀቀ በኋላ በአልባኒ ኒው ዮርክ መኖር ጀመረ።

በ1842 የጸደይ ወቅት መግቢያ ላይ ስቶርዝ “ምርምር የሚያሻው ጥያቄ​—⁠ክፉዎች የማትሞት ነፍስ አለቻቸው?” በሚል ርዕስ በስድስት ሳምንታት ጊዜ ውስጥ ስድስት ተከታታይ ንግግሮች አቀረበ። ሕዝቡ ለማወቅ የነበረው ጉጉት ከፍተኛ ስለነበረ አንዳንድ ማሻሻያዎችን አድርጎበት ያሳተመው ሲሆን በቀጣዮቹ ከ40 በሚበልጡ ዓመታት ጊዜ ውስጥ በዩናይትድ ስቴትስና በታላቋ ብሪታኒያ በ200, 000 ቅጂዎች ተሰራጨ። ስቶርዝ እና ግሪው ነፍስ አትሞትም የሚለውን መሠረተ ትምህርት ውድቅ የሚያደርግ የመከራከሪያ ሐሳብ በማቅረብ ግንባር ፈጥረው ነበር። ግሪው ነሐሴ 8, 1862 በፊላደልፊያ እስከ ሞተበት ዕለት ድረስ በቅንዓት ሲሰብክ ቆይቷል።

ስቶርዝ ቀደም ሲል የተጠቀሱትን ስድስት ንግግሮች ካቀረበ በኋላ ክርስቶስ በ1843 በሚታይ ሁኔታ ይመለሳል ብሎ በሚጠብቀው በዊልያም ሚለር ስብከት ተማረከ። ስቶርዝ ለሁለት ዓመታት ያህል ይህን መልእክት በሰሜን ምሥራቅ ዩናይትድ ስቴትስ ከዳር እስከ ዳር ይሰብክ ነበር። ከ1844 በኋላ የክርስቶስ መመለስ በዚህ ጊዜ ይሆናል ብሎ ቀን ቆርጦ መጠበቁን አቆመ፤ ሆኖም ሌሎች ስለ ዘመናት ስሌት ምርምር ቢያደርጉ አይቃወምም ነበር። ስቶርዝ የክርስቶስ መመለስ እንደቀረበ ያምን ስለነበር ክርስቲያኖች ምርመራ ለሚካሄድበት ቀን ዝግጁ እንዲሆኑ መንቃትና በመንፈሳዊ መትጋት እንደሚያስፈልጋቸው ይናገር ነበር። ሆኖም ስቶርዝ ከሚለር ቡድን ጋር የነበረውን ግንኙነት አቋረጠ፤ ምክንያቱም ቡድኑ ነፍስ አትሞትም፣ ዓለም ትቃጠላለች፣ ሳያውቁ የሞቱ ሰዎች ምንም ዓይነት የዘላለም ሕይወት ተስፋ የላቸውም እንደሚሉት ባሉ ቅዱስ ጽሑፋዊ ባልሆኑ መሠረተ ትምህርቶች ያምናሉ።

የአምላክ ፍቅር ወደ ምን ይመራል?

አምላክ ክፉ ሰዎችን ከሞት የሚያስነሳው መልሶ ሊገድላቸው ብቻ ነው የሚለው የአድቬንቲስቶች አመለካከት አይዋጥለትም ነበር። አምላክ ይህን ትርጉም የለሽ የበቀል እርምጃ ስለሚወስድበት ምክንያት የሚገልጽ ማስረጃ ከቅዱሳን ጽሑፎች ፈጽሞ ማግኘት አልቻለም። ስቶርዝና ጓደኞቹ ወደ ሌላኛው ጽንፍ በመሄድ ክፉዎች ከናካቴው አይነሱም ብለው ደምድመው ነበር። ምንም እንኳ ኃጢአተኞች ትንሣኤ ስለ ማግኘታቸው የሚናገሩትን አንዳንድ ጥቅሶች ማብራራት ቢቸግራቸውም የደረሱበት መደምደሚያ ከአምላክ ፍቅር ጋር ይበልጥ ተስማሚ እንደሆነ ተሰምቷቸው ነበር። ስለ አምላክ ዓላማ ተጨማሪ ግንዛቤ የሚገኝበት ጊዜ ሩቅ አልነበረም።

በ1870 ስቶርዝ በጠና ስለታመመ ለጥቂት ወራት ሥራ አቁሞ ነበር። በዚያን ጊዜ ውስጥ ባሳለፋቸው 74 ዓመታት የተማራቸውን ነገሮች አንድ በአንድ የመከለስ አጋጣሚ አገኘ። በአብርሃም ቃል ኪዳን ውስጥ የተገለጸውን ‘አብርሃም የአምላክን ቃል ስለሰማ የምድር ሕዝቦች በሙሉ እንደሚባረኩ’ አምላክ ለሰው ልጆች ያለውን ዓላማ ዓብይ ክፍል እንደዘነጋ ተገነዘበ።​—⁠ዘፍጥረት 22:​18፤ ሥራ 3:​25

ይህም አንድ አዲስ ሐሳብ ብልጭ እንዲልለት አደረገ። “የምድር አሕዛብ ሁሉም” የሚባረኩ ከሆነ ምሥራቹ ለሁሉም ሊሰበክ አይገባውም? ታዲያ እንዴት ይሰማሉ? በሚልዮንና በቢልዮን የሚቆጠሩ ሰዎች ሞተው የለም እንዴ? ቅዱሳን ጽሑፎችን ይበልጥ ሲመረምር የሞቱት “ክፉ” ሰዎች በሁለት እንደሚከፈሉ ተገነዘበ። እነርሱም የአምላክን ፍቅር በፈቃዳቸው አንቀበልም ያሉና ስለ አምላክ ፍቅር ምንም ሳያውቁ የሞቱ ናቸው።

ስቶርዝ እንደሚለው ስለ አምላክ ፍቅር ሳያውቁ የሞቱ ሰዎች የኢየሱስ ክርስቶስ ቤዛዊ መሥዋዕት ጥቅም የማግኘት አጋጣሚ እንዲከፈትላቸው ሲባል ከሞት ይነሳሉ። ቤዛዊ መሥዋዕቱን የሚቀበሉ በምድር ላይ ለዘላለም ይኖራሉ። የማይቀበሉ ለዘላለም ይጠፋሉ። አዎን፣ የመኖር ተስፋ ሳይኖረው አምላክ ከሞት የሚያስነሳው ሰው እንደማይኖር ስቶርዝ ያምን ነበር። ውሎ አድሮ ከአዳም ከራሱ በስተቀር በአዳም ኃጢአት ምክንያት የሚሞት ሰው አይኖርም! ሆኖም ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ተመልሶ በሚመጣበት ጊዜ በሕይወት የሚኖሩ ሰዎችስ ምን ይሆናሉ? ስቶርዝ እነዚህን ሰዎች ለማዳረስ ዓለም አቀፋዊ የስብከት ዘመቻ መካሄድ እንዳለበት የኋላ ኋላ ተገንዝቦ ነበር። እንዲህ ያለው ሥራ እንዴት ሊሠራ እንደሚችል ምንም ፍንጭ የለውም፤ ሆኖም በእምነት እንዲህ ሲል ጽፎ ነበር:- “ለእነርሱ ካልተቻለ ለአምላክ የማይቻል ይመስል ብዙዎች አንድን ነገር እንዴት እንደሚሠራ ካልታያቸው አይነኩትም።”

ጆርጅ ስቶርዝ ታኅሣሥ 1879 ብሩክሊን ኒው ዮርክ በሚገኘው ቤቱ ሞተ። ቤቱ በጉጉት ሲጠብቀው የነበረው ዓለም አቀፍ የስብከት ዘመቻ ማዕከል ከሆነው ሕንፃ ጥቂት አለፍ ብሎ ይገኝ ነበር።

ተጨማሪ ብርሃን አስፈለገ

ሄንሪ ግሪውንና ጆርጅ ስቶርዝን የመሳሰሉ ሰዎች እውነትን እንደ እኛ በግልጽ ተረድተው ነበርን? በፍጹም። ስቶርዝ በ1847 “ከቤተ ክርስቲያን የጨለማ ዘመን ገና መውጣታችን እንደሆነ መዘንጋት የለብንም፤ እውነት እንደሆኑ በማሰብ አሁንም ድረስ አንዳንድ ‘ባቢሎናዊ ልብሶችን’ እንደለበስን ብንገኝ ሊያስገርም አይገባም” ሲል እንደተናገረው ጥረታቸው ምን እንደነበረ ተረድተውታል። ለምሳሌ ያህል ግሪው ኢየሱስ ቤዛ እንደሆነ ተገንዝቧል። ሆኖም የኢየሱስ ፍጹም ሰብዓዊ ሕይወት የአዳምን ፍጹም ሰብዓዊ ሕይወት ለመተካት የተከፈለ “ተመጣጣኝ ቤዛ” እንደሆነ አልተረዳም ነበር። (1 ጢሞቴዎስ 2:​6 NW ) እንዲሁም ሄንሪ ግሪው ኢየሱስ በሚታይ መንገድ መጥቶ እዚህ ምድር ላይ ይገዛል የሚል የተሳሳተ አስተሳሰብ ነበረው። ይሁን እንጂ ግሪው ከሁለተኛው መቶ ዘመን አንስቶ ጥቂት ሰዎች ብቻ ትኩረት ሰጥተውት የነበረው ጉዳይ ይኸውም የይሖዋ ስም መቀደስ ሲያሳስበው ቆይቷል።

በተመሳሳይም ጆርጅ ስቶርዝ አንዳንድ አስፈላጊ ነጥቦችን በትክክል አልተረዳም ነበር። ቀሳውስቱ የሚያስተምሩት ሐሰት መሆኑን ተረድቶ ነበር፤ ሆኖም አንዳንድ ጊዜ እሱ ራሱ ወደ ተቃራኒው ጽንፍ ያደላ ነበር። ለምሳሌ ያህል የኦርቶዶክስ ቀሳውስት ስለ ሰይጣን ያላቸውን አመለካከት ለመቃወም ሳይሆን አይቀርም ዲያብሎስ ራሱን የቻለ አንድ አካል ነው የሚለውን ትምህርት አይቀበልም ነበር። በሥላሴ አያምንም ነበር። ሆኖም ሊሞት እስከተቃረበበት ጊዜ ድረስ መንፈስ ቅዱስ አካል ይሁን አይሁን እርግጠኛ አልነበረም። ጆርጅ ስቶርዝ ክርስቶስ የሚመለሰው በማይታይ ሁኔታ ቢሆንም መጨረሻ ላይ በሚታይ ሁኔታ ይገለጣል ብሎ ያስብ ነበር። የሆነ ሆኖ ሁለቱም ሰዎች ልበ ቅኖች ነበሩ ለማለት ይቻላል። ከሌሎች በተሻለ ወደ እውነት ተጠግተዋል።

ኢየሱስ ስለ ስንዴውና ስለ እንክርዳዱ በተናገረው ምሳሌ ላይ የጠቀሰው “እርሻው” ገና ለአጨዳ አልደረሰም ነበር። (ማቴዎስ 13:​38) ግሪው፣ ስቶርዝና ሌሎች ሰዎች ለመከሩ ሥራ አንዳንድ ሁኔታዎችን በማመቻቸት በ“እርሻው” ላይ ሲሠሩ ቆይተዋል።

ይህን መጽሔት በ1879 ማሳተም የጀመረው ቻርልስ ቴዝ ራስል ቀደም ሲል ስላሳለፋቸው ዓመታት የሚከተለውን ጽፎ ነበር:- “ጌታ ቃሉን ስናጠና በእጅጉ ረድቶናል፤ እጅግ ተወዳጅ የሆነው አረጋዊው ወንድማችን ጆርጅ ስቶርዝ በግንባር ቀደምትነት ከሚጠቀሱት አንዱ ሲሆን በቃልም ሆነ በጽሑፍ ብዙ ረድቶናል። ሆኖም ‘እንደተወደዱ ልጆች የአምላክ ተከታዮች’ ለመሆን እንጂ የሰው ደቀ መዛሙርት ለመሆን አስበን አናውቅም።” አዎን፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች ግሪውንና ስቶርዝን የመሰሉ ሰዎች ካደረጉት ጥረት ጥቅም ሊያገኙ ይችላሉ። አሁንም ቢሆን እውነት የሚፈልቅበት ትክክለኛው ምንጭ መጽሐፍ ቅዱስ በመሆኑ የአምላክን ቃል መመርመሩ እጅግ አስፈላጊ ነው።​—⁠ዮሐንስ 17:​17

[በገጽ 26 ላይ የሚገኝ ሣጥን/ሥዕል]

ሄንሪ ግሪው ያምንባቸው የነበሩ ነገሮች

የይሖዋ ስም ነቀፋ ደርሶበታል፤ ስለዚህ መቀደስ ያስፈልገዋል።

ሥላሴ፣ ነፍስ አትሞትም እንዲሁም ሲኦል መቃጠያ ቦታ ነው የሚሉት መሠረተ ትምህርቶች ሐሰት ናቸው።

የክርስቲያን ጉባኤ ከዓለም መለየት ይገባዋል።

ክርስቲያኖች ብሔራት በሚያደርጉት ጦርነት መሳተፍ አይገባቸውም።

ክርስቲያኖች በቅዳሜ ወይም በእሑድ የሰንበት ሕግ ሥር አይደሉም።

ክርስቲያኖች እንደ ፍሪማሶን ያሉ ምስጢራዊ ቡድኖች አባላት መሆን አይገባቸውም።

በክርስቲያኖች መካከል የቀሳውስት ክፍልና የምዕመናን ክፍል የሚል ነገር መኖር የለበትም።

ሃይማኖታዊ ማዕረግ የጸረ ክርስቶሶች ነው።

ጉባኤዎች በሙሉ የሽማግሌዎች አካል ይኖራቸዋል።

ሽማግሌዎች በአኗኗራቸው ሁሉ ቅዱስና የማይነቀፉ ሊሆኑ ይገባል።

እያንዳንዱ ክርስቲያን ምሥራቹን መስበክ ይገባዋል።

በምድር ላይ በገነት ለዘላለም የሚኖሩ ሰዎች ይኖራሉ።

ክርስቲያናዊ መዝሙር ይሖዋንና ክርስቶስን የሚያወድስ ሊሆን ይገባዋል።

[ምንጭ]

ፎቶ:- Collection of The New-York Historical Society/69288

[በገጽ 28 ላይ የሚገኝ ሣጥን/ሥዕል]

ጆርጅ ስቶርዝ ያምንባቸው የነበሩ ነገሮች

ኢየሱስ ለሰው ዘር ሕይወቱን ቤዛ አድርጎ ከፍሏል።

ምሥራቹ ገና አልተሰበከም (በ1871)።

በዚህ ምክንያት መጨረሻው በዚያ ጊዜ አልቀረበም (በ1871)። ምሥራቹ የሚሰበክበት ጊዜ ወደፊት መምጣት አለበት።

በምድር ላይ የዘላለም ሕይወት የሚወርሱ ሰዎች ይኖራሉ።

ስለ አምላክ እውነት ሳያውቁ የሞቱ ሰዎች በሙሉ ትንሣኤ ያገኛሉ። የክርስቶስን ቤዛዊ መሥዋዕት የሚቀበሉ ሰዎች በምድር ላይ የዘላለም ሕይወት ያገኛሉ። የማይቀበሉ ለዘላለም ይጠፋሉ።

የሰው ነፍስ አትሞትም እና ሲኦል መቃጠያ ስፍራ ነው የሚሉት መሠረተ ትምህርቶች ለአምላክ ክብር የማይሰጡ ትምህርቶች ናቸው።

የጌታ እራት ኒሳን 14 የሚከበር ዓመታዊ በዓል ነው።

[ምንጭ]

ፎቶ:- የጆርጅ ስቶርዝ ስድስት ተከታታይ ስብከቶች (1855)

[በገጽ 29 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

“የጽዮን መጠበቂያ ግንብ” አዘጋጅ ሲ ቲ ራስል በ1909 ወደ ብሩክሊን፣ ኒው ዮርክ፣ ዩ ኤስ ኤ ተዛወረ