በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የአንባቢያን ጥያቄዎች

የአንባቢያን ጥያቄዎች

የአንባቢያን ጥያቄዎች

ኢየሱስ፣ ታማኝ ባሪያውን “ብልኅ” ብሎ ሲጠራው ምን ማለቱ ነበር?

ኢየሱስ እንዲህ በማለት ጠይቆ ነበር:- “በተገቢው ጊዜ ምግባቸውን እንዲሰጣቸው ባለቤቱ በቤተ ሰዎቹ ላይ የሾመው ታማኝና ብልኀ አገልጋይ እንግዲህ ማነው?” (ማቴዎስ 24:45) መንፈሳዊ ‘ምግብ’ የሚያቀርበው “አገልጋይ” ወይም ባሪያ በመንፈስ የተቀቡ ክርስቲያኖችን ጉባኤ ያመለክታል። ታዲያ ኢየሱስ እነዚህን ክርስቲያኖች ብልኅ ብሎ የጠራቸው ለምን ነበር? a

ኢየሱስ “ብልኅ” ሲል ምን ማለቱ እንደሆነ እሱ ከሰጠው ትምህርት መረዳት እንችላለን። ለአብነት ያህል፣ ክርስቶስ ስለ “ታማኝና ብልኀ አገልጋይ” በጠቀሰበት ወቅት የሙሽራውን መምጣት ይጠባበቁ ስለነበሩ አሥር ልጃገረዶች የሚገልጽ ምሳሌ ተናግሮ ነበር። እነዚህ ልጃገረዶች የታላቁን ሙሽራ የኢየሱስ ክርስቶስን መምጣት በከፍተኛ ጉጉት ይጠባበቁ የነበሩትን ከ1914 በፊት የነበሩ ቅቡዓን ክርስቲያኖችን ያስታውሱናል። ከእነዚህ ከአሥሩ ልጃገረዶች መካከል አምስቱ ሙሽራውን ለመቀበል የሚያስችላቸው በቂ ዘይት ስላልነበራቸው በሠርጉ ግብዣ ላይ ሊገኙ አልቻሉም። አምስቱ ግን ብልኅ መሆናቸውን አሳይተዋል። ሙሽራው ሲመጣ መብራታቸውን እያበሩ መቀጠል እንዲችሉ በቂ ዘይት ይዘው ስለነበር ወደ ሠርጉ ግብዣ አብረውት እንዲገቡ ተፈቅዶላቸዋል።—ማቴዎስ 25:10-12

ኢየሱስ በ1914 በመንግሥቱ ሥልጣን ሲገኝ ከቅቡዓን ክርስቲያኖች መካከል አብዛኞቹ ወዲያውኑ ወደ ሰማይ ሄደው ከእሱ ጋር እንደሚሆኑ ተስፋ አድርገው ነበር። ይሁን እንጂ በምድር ላይ የሚሠሩት ብዙ ሥራ የነበረ ሲሆን አንዳንዶች ለዚህ ዝግጁ አልነበሩም። እነዚህ ክርስቲያኖች ብልኅ እንዳልነበሩት ልጃገረዶች አስቀድመው ራሳቸውን በመንፈሳዊ ባለማጠናከራቸው ብርሃን አብሪዎች ሆነው ለመቀጠል አልተዘጋጁም ነበር። አብዛኞቹ ክርስቲያኖች ግን ጥበበኞችና አርቆ አስተዋዮች በመሆን ራሳቸውን በመንፈሳዊ በማጠናከር ብልኅ መሆናቸውን አሳይተዋል። ብዙ ሥራ እንደሚጠብቃቸው ሲያውቁ በደስታ ይህን ሥራ ለማከናወን ተነሳስተዋል። በመሆኑም “ታማኝና ብልኀ አገልጋይ” ወይም ባሪያ መሆናቸውን አሳይተዋል።

ኢየሱስ በማቴዎስ 7:24 ላይ “ብልኅ” የሚለውን ቃል እንዴት እንደተጠቀመበት እንመልከት። “ቃሌን ሰምቶ በተግባር የሚያውል፣ ቤቱን በዐለት ላይ የሠራን ብልኅ ሰው ይመስላል” ብሏል። ይህ ብልኅ ሰው፣ ቤቱ ኃይለኛ ዝናብንና ንፋስን መቋቋም እንዲችል ቤቱን በጠንካራ መሠረት ላይ ገንብቶታል። ከዚህ በተቃራኒ ግን ሞኙ ሰው ቤቱን የሠራው በአሸዋ ላይ በመሆኑ ፈርሶበታል። በመሆኑም ብልኅ የሆነ የኢየሱስ ተከታይ ሰብዓዊ ጥበብን መከተል የሚያመጣውን መዘዝ አስቀድሞ ያስተውላል። እንዲህ ያለው ሰው አስተዋይና ጥሩ የማመዛዘን ችሎታ ያለው በመሆኑ እምነቱ፣ ተግባሩና ትምህርቱ በኢየሱስ ትምህርቶች ላይ የተመሠረተ ነው። በተመሳሳይም ‘ታማኝና ብልኀ የሆነው አገልጋይ’ ወይም ባሪያ እንዲሁ ያደርጋል።

“ብልኀ” ተብሎ የተተረጎመው ቃል በተለያዩ የዕብራይስጥ ቅዱሳን መጻሕፍት ትርጉሞች ውስጥ እንዴት እንደተሠራበትም እንመልከት። ለምሳሌ ፈርዖን፣ የግብጽን የምግብ አቅርቦት እንዲቆጣጠር ዮሴፍን የሾመው ሲሆን ይህም ይሖዋ ለሕዝቡ ምግብ ለማቅረብ ያደረገው ዝግጅት ክፍል ነበር። ዮሴፍ የተመረጠው ለምንድን ነው? ፈርዖን ዮሴፍን “እንዳንተ ያለ አስተዋይና ብልኀ ሰው የለም” ብሎታል። (ዘፍጥረት 41:33-39፤ 45:5) በተመሳሳይም መጽሐፍ ቅዱስ አቢግያን “አስተዋይ” ወይም ብልኅ በማለት ጠርቷታል። አቢግያ፣ ይሖዋ ለቀባው ለዳዊትና አብረውት ለነበሩት ሰዎች ምግብ አቅርባለች። (1 ሳሙኤል 25:3, 11, 18) ዮሴፍና አቢግያ የአምላክን ፈቃድ አስተውለው አርቆ አሳቢነትና ጥሩ የማመዛዝን ችሎታ የተንጸባረቀበት እርምጃ በመውሰዳቸው ብልኅ ተብለው ሊጠሩ ችለዋል።

ስለዚህ ኢየሱስ ታማኙን ባሪያ፣ ብልኅ ብሎ ሲጠራው በባሪያው የተወከሉት ክርስቲያኖች የማስተዋል፣ አርቆ የመመልከትና ጥሩ የማመዛዘን ችሎታ እንደሚኖራቸው መጠቆሙ ነው። ይህ የሆነው ደግሞ እምነታቸው፣ ተግባራቸው እንዲሁም ትምህርታቸው እውነት በሆነው የአምላክ ቃል ላይ የተመሠረተ በመሆኑ ነው።

[የግርጌ ማስታወሻ]

a “ብልኅ” ተብሎ የተተረጎመው የግሪክኛ ቃል ፍሮኒሞስ የሚል ነው። በማርቪን ቪንሰንት በተዘጋጀው ወርድ ስተዲስ ኢን ዘ ኒው ቴስታመንት በተባለው መጽሐፍ መሠረት ይህ ቃል ብዙውን ጊዜ ጥበብንና ማስተዋልን ያመለክታል።