በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ከመንጋው ወጥተው የባዘኑትን እርዱ

ከመንጋው ወጥተው የባዘኑትን እርዱ

ከመንጋው ወጥተው የባዘኑትን እርዱ

“የጠፋውን በጌን አግኝቻለሁና ከእኔ ጋር ደስ ይበላችሁ።”—ሉቃስ 15:6

1. ኢየሱስ አፍቃሪ እረኛ መሆኑን ያሳየው እንዴት ነው?

የይሖዋ አንድያ ልጅ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ “የበጎች ታላቅ እረኛ” ተብሎ ተጠርቷል። (ዕብ. 13:20) ቅዱሳን መጻሕፍት ስለ እሱ መምጣት አስቀድመው የተናገሩ ሲሆን ከእስራኤል ቤት ‘የጠፉትን በጎች’ የሚፈልግ ልዩ እረኛ መሆኑንም አመልክተዋል። (ማቴ. 2:1-6፤ 15:24) ከዚህም በተጨማሪ አንድ እረኛ በጎቹን ከአደጋ ለመጠበቅ ሲል ሕይወቱን እስከ መስጠት ሊደርስ እንደሚችል ሁሉ ኢየሱስም ከእሱ መሥዋዕት ለመጠቀም ራሳቸውን ለሚያቀርቡ በግ መሰል ሰዎች ሲል ቤዛ ሆኖ ሞቷል።—ዮሐ. 10:11, 15፤ 1 ዮሐ. 2:1, 2

2. አንዳንድ ክርስቲያኖች በመንፈሳዊ እንዲቀዘቅዙ ያደረጋቸው ምን ሊሆን ይችላል?

2 የሚያሳዝነው ነገር ለኢየሱስ መሥዋዕት አድናቆት እንዳላቸው ያሳዩና ራሳቸውን ለአምላክ የወሰኑ አንዳንዶች ከክርስቲያን ጉባኤ ርቀዋል። በተስፋ መቁረጥ፣ በጤና እክሎች ወይም በሌሎች ችግሮች የተነሳ ቅንዓታቸው ስለጠፋ በመንፈሳዊ ቀዝቅዘዋል። ይሁን እንጂ ዳዊት በ23ኛው መዝሙር ላይ የተናገረው ዓይነት ሰላምና ደስታ ማግኘት የሚችሉት የአምላክ መንጋ ክፍል ከሆኑ ብቻ ነው። ዳዊት “እግዚአብሔር [“ይሖዋ፣” NW] እረኛዬ ነው፤ አንዳች አይጐድልብኝም” ሲል ዘምሯል። (መዝ. 23:1) በአምላክ መንጋ ውስጥ ያሉ ሰዎች በመንፈሳዊ ሁኔታ አንዳች የሚጎድልባቸው ነገር የለም፤ ከመንጋው ወጥተው የባዘኑት በጎች ሁኔታ ግን ከዚህ የተለየ ነው። ታዲያ እነዚህን ሰዎች ማን ሊረዳቸው ይችላል? እርዳታ ሊደረግላቸው የሚችለው እንዴት ነው? ወደ መንጋው እንዲመለሱ ምን ዓይነት እርዳታ ሊደረግላቸው ይችላል?

ማን ሊረዳቸው ይችላል?

3. ኢየሱስ ከአምላክ ማሰማሪያ ወጥተው የጠፉትን በጎች ለመታደግ ምን እንደሚያስፈልግ የገለጸው እንዴት ነው?

3 ከአምላክ ማሰማሪያ ወጥተው የጠፉትን በጎች መታደግ ልባዊ ጥረት ማድረግ ይጠይቃል። (መዝ. 100:3) ኢየሱስ ይህን ሁኔታ እንዲህ ሲል በምሳሌ ገልጿል፦ “አንድ ሰው መቶ በጎች ቢኖሩትና ከእነርሱም አንዱ ቢጠፋበት ዘጠና ዘጠኙን በተራራ ላይ ትቶ የጠፋውን ለመፈለግ አይሄድምን? እውነት እላችኋለሁ፣ የጠፋውን በግ ሲያገኝ፣ ካልጠፉት ከዘጠና ዘጠኙ ይልቅ በዚያ በተገኘው ደስ ይለዋል። እንደዚሁም ከእነዚህ ከታናናሾቹ መካከል አንዱ እንኳ እንዲጠፋ በሰማያት ያለው አባታችሁ ፈቃድ አይደለም።” (ማቴ. 18:12-14) ታዲያ ከመንጋው ወጥተው የባዘኑትን በግ መሰል ሰዎች ማን ሊረዳቸው ይችላል?

4, 5. ሽማግሌዎች ለአምላክ መንጋ ምን ዓይነት አመለካከት ሊኖራቸው ይገባል?

4 ክርስቲያን ሽማግሌዎች የባዘኑትን በጎች ለመርዳት ከፈለጉ የአምላክ መንጋ ሲባል ራሳቸውን ለአምላክ የወሰኑ ሰዎችን ጉባኤ፣ አዎ ውድ የሆኑትን ‘የአምላክ የማሰማሪያ በጎች’ የሚያመለክት መሆኑን ማስታወስ ይኖርባቸዋል። (መዝ. 79:13) እነዚህ ውድ የሆኑ በጎች በጥንቃቄ መያዝ ይፈልጋሉ፤ ይህ ደግሞ አፍቃሪ የሆኑ እረኞች ለበጎቹ በግል ትኩረት ማሳየት ይጠይቅባቸዋል። ለእነዚህ በጎች ወዳጃዊ በሆነ መንፈስ የእረኝነት ጉብኝት ማድረግ ጥሩ ውጤት ሊያስገኝ ይችላል። አንድ እረኛ የሚሰጣቸው ፍቅራዊ ማበረታቻ በመንፈሳዊ ሊያንጻቸውና ወደ መንጋው የመመለስ ፍላጎታቸው እንዲጨምር ሊያደርግ ይችላል።—1 ቆሮ. 8:1

5 የአምላክ መንጋ እረኞች የባዘኑትን በጎች የመፈለግና የመርዳት ኃላፊነት አለባቸው። ሐዋርያው ጳውሎስ በጥንቷ ኤፌሶን የነበሩትን ክርስቲያን ሽማግሌዎች፣ የእረኝነት ኃላፊነታቸውን በተመለከተ እንዲህ ሲል አሳስቧቸዋል፦ “ለራሳችሁና መንፈስ ቅዱስ ኤጲስቆጶሳት አድርጎ በላዩ ለሾማችሁ መንጋ ሁሉ ተጠንቀቁ፤ በገዛ ደሙ [“በገዛ ልጁ ደም፣” የታረመው የ1980 ትርጉም] የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ጠብቁ።” (ሥራ 20:28) በተመሳሳይም ሐዋርያው ጴጥሮስ በመንፈስ የተቀቡ ሽማግሌዎችን እንዲህ ሲል መክሯቸዋል፦ “በእናንተ ኀላፊነት ሥር ያለውን የእግዚአብሔርን መንጋ ጠብቁ፤ የምትጠብቁትም ከእግዚአብሔር እንደሚጠበቅባችሁ በግድ ሳይሆን በፈቃደኝነት፣ ለጥቅም በመስገብገብ ሳይሆን ለማገልገል ባላችሁ ጽኑ ፍላጎት ይሁን፤ እንዲሁም በዐደራ ለተሰጣችሁ መንጋ መልካም ምሳሌ በመሆን እንጂ በላያቸው በመሠልጠን አይሁን።”—1 ጴጥ. 5:1-3

6. የአምላክ በጎች በተለይ በዛሬው ጊዜ የእረኞች እንክብካቤ የሚያስፈልጋቸው ለምንድን ነው?

6 ክርስቲያን እረኞች ‘መልካሙን እረኛ’ ኢየሱስን መኮረጅ ይኖርባቸዋል። (ዮሐ. 10:11) ኢየሱስ ለአምላክ በጎች በጥልቅ ያስብ የነበረ ከመሆኑም ሌላ ስምዖን ጴጥሮስን “በጎቼን ጠብቅ” ባለው ጊዜ በጎቹን የመንከባከቡን አስፈላጊነት በአጽንዖት ገልጿል። (ዮሐንስ 21:15-17ን አንብብ።) ዲያብሎስ ራሳቸውን ለአምላክ የወሰኑ ሰዎች ንጹሕ አቋማቸውን እንዲያጎድፉ ለማድረግ ጥረቱን ባፋፋመበት በተለይ በዛሬው ጊዜ በጎቹ እንዲህ ዓይነት እንክብካቤ ያስፈልጋቸዋል። ሰይጣን የሥጋ ድካማችንንና ይህን ዓለም በመጠቀም የይሖዋ በጎች ኃጢአት እንዲፈጽሙ ለማድረግ ይጥራል። (1 ዮሐ. 2:15-17፤ 5:19) የቀዘቀዙ ክርስቲያኖች ይበልጥ ለዚህ ጥቃት የተጋለጡ ስለሆኑ “በመንፈስ ኑሩ” የሚለውን ምክር ተግባራዊ እንዲያደርጉ እርዳታ ያስፈልጋቸዋል። (ገላ. 5:16-21, 25) እንዲህ ዓይነቶቹን በጎች መታደግ እንድንችል አምላክ እንዲረዳን መጸለይ፣ የመንፈሱን አመራር መለመንና ቃሉን በጥሩ ሁኔታ መጠቀም ይኖርብናል።—ምሳሌ 3:5, 6፤ ሉቃስ 11:13፤ ዕብ. 4:12

7. ሽማግሌዎች በእነሱ ጥበቃ ሥራ የሚገኙትን በግ መሰል ሰዎች መንከባከባቸው ምን ያህል አስፈላጊ ነው?

7 በጥንቷ እስራኤል የሚኖር አንድ እረኛ መንጋውን ለመምራት ረጅም ቆልማማ በትር ወይም ከዘራ ይጠቀም ነበር። በጎቹ ወደ ጉረኗቸው ሲገቡ ወይም ከዚያ ሲወጡ እረኛው ‘ከበትሩ በታች’ እንዲያልፉ በማድረግ ይቆጥራቸዋል። (ዘሌ. 27:32፤ ሚክ. 2:12፤ 7:14) አንድ ክርስቲያን እረኛም በተመሳሳይ በእሱ ጥበቃ ሥር ባለው የአምላክ መንጋ ውስጥ የሚገኘውን እያንዳንዱን በግ በሚገባ ሊያውቅና ያለበትን ሁኔታ ሊከታተል ይገባል። (ከምሳሌ 27:23 ጋር አወዳድር።) በመሆኑም እረኝነት የሽማግሌዎች አካል ከሚወያይባቸው አስፈላጊ ጉዳዮች መካከል አንዱ ነው። ይህም የባዘኑትን በጎች ለመርዳት ዝግጅት ማድረግን ይጨምራል። ይሖዋ ራሱ በጎቹን እንደሚፈልግና የሚያስፈልጋቸውን እንክብካቤ እንደሚያደርግላቸው ተናግሯል። (ሕዝ. 34:11) ስለዚህ ሽማግሌዎች የባዘኑት በጎች ወደ መንጋው እንዲመለሱ ለመርዳት ተመሳሳይ ጥረት ሲያደርጉ ሲያይ ይደሰታል።

8. ሽማግሌዎች ለበጎች በግል ትኩረት ሊሰጡ የሚችሉት በምን መንገዶች ነው?

8 አንድ የእምነት ባልንጀራችን አካላዊ ጤንነቱ ቢቃወስና የአምላክን መንጋ የሚጠብቅ አንድ እረኛ ሄዶ ቢጠይቀው ሊደሰትና ሊበረታታ ይችላል። በመንፈሳዊ የታመመ አንድ በግም በግል ትኩረት ሲሰጠው ተመሳሳይ ስሜት ይሰማዋል። ሽማግሌዎች ለቀዘቀዘው ክርስቲያን ጥቅሶች ሊያነቡለት፣ በጽሑፍ ላይ የወጣ አንድ ርዕስ ሊያወያዩት፣ በስብሰባ ላይ ከቀረቡት ትምህርቶች ዋና ዋናዎቹን ሊከልሱለት፣ አብረውት ሊጸልዩና የመሳሰሉትን ነገሮች ሊያደርጉ ይችላሉ። ሽማግሌዎቹ እሱ ወደ ጉባኤ ስብሰባ ቢመጣ የጉባኤው አባላት ደስ እንደሚላቸው ሊጠቅሱለት ይችላሉ። (2 ቆሮ. 1:3-7፤ ያዕ. 5:13-15) የቀዘቀዘውን ሰው ሄዶ በመጠየቅ፣ ስልክ በመደወል ወይም ደብዳቤ በመጻፍ ማበረታታት ትልቅ ለውጥ ሊያመጣ ይችላል! ከመንጋው ለጠፋ በግ በግል እርዳታ መስጠት ርኅሩኅ ለሆነው ክርስቲያን እረኛም ከፍተኛ ደስታ ሊያስገኝ ይችላል።

በጋራ የሚደረግ ጥረት

9, 10. ለባዘኑ በጎች እርዳታ መስጠት ለሽማግሌዎች ብቻ የተተወ አይደለም የምንለው ለምንድን ነው?

9 የምንኖረው ውጥረት በበዛበትና አስጨናቂ በሆነ ዘመን ውስጥ ስለሆነ አንድ የእምነት ባልንጀራችን ቀስ በቀስ ከጉባኤ እየራቀ መሆኑን ላናስተውል እንችላለን። (ዕብ. 2:1) ይሁንና የይሖዋ በጎች በእሱ ፊት ውድ ናቸው። እያንዳንዱ የሰውነታችን ክፍል አስፈላጊ እንደሆነ ሁሉ እያንዳንዱ በግም ዋጋ አለው። በመሆኑም ሁላችንም ለወንድሞቻችን ትኩረት መስጠትና እርስ በርስ ከልብ መተሳሰብ ይኖርብናል። (1 ቆሮ. 12:25) አንተስ እንዲህ ዓይነት አመለካከት አለህ?

10 ምንም እንኳ ሽማግሌዎች የባዘኑትን በጎች በመፈለግና በመርዳት ረገድ ግንባር ቀደም ቢሆኑም ከመካከላችን ለጠፉ የእምነት ባልንጀሮቻችን ትኩረት መስጠት ለክርስቲያን የበላይ ተመልካቾች ብቻ የተተወ አይደለም። ሌሎችም ከእነዚህ እረኞች ጋር መተባበር ይችላሉ። እኛም ወደ መንጋው ለመመለስ እርዳታ ለሚያስፈልጋቸው ወንድሞቻችንና እህቶቻችን ማበረታቻና መንፈሳዊ እርዳታ መስጠት እንችላለን፤ ደግሞም እንዲህ ማድረግ ይኖርብናል። ታዲያ እንዲህ ዓይነት እርዳታ መስጠት የሚቻለው እንዴት ነው?

11, 12. መንፈሳዊ እርዳታ የሚያስፈልገውን ሰው መርዳት የምትችልበት ምን መብት ልታገኝ ትችላለህ?

11 አንዳንድ ጊዜ ሽማግሌዎች እርዳታ እንዲደረግላቸው የሚፈልጉ የቀዘቀዙ ክርስቲያኖችን ተሞክሮ ያላቸው የመንግሥቱ አስፋፊዎች በግል መጽሐፍ ቅዱስን እንዲያስጠኗቸው ዝግጅት ሊያደርጉ ይችላሉ። ይህ ዝግጅት የሚደረግበት ዓላማ እነዚህ የቀዘቀዙ ክርስቲያኖች ‘የቀድሞ ፍቅራቸውን’ መልሰው እንዲያቀጣጥሉ ለመርዳት ነው። (ራእይ 2:1, 4) እነዚህ የእምነት ባልንጀሮቻችን ከጉባኤ ርቀው በቆዩባቸው ጊዜያት ያመለጧቸውን ትምህርቶች አብሮ በመከለስ እንዲታነጹና በመንፈሳዊ እንዲጠናከሩ ማድረግ ይቻላል።

12 ሽማግሌዎች መንፈሳዊ እርዳታ የሚያስፈልገውን አንድ የእምነት ባልንጀራህን እንድታስጠና ከጠየቁህ ይሖዋ እንዲመራህና የምታደርገውን ጥረት እንዲባርክልህ ጸልይ። አዎ፣ “የምታደርገውን ሁሉ ለእግዚአብሔር ዐደራ ስጥ፤ ዕቅድህም ሁሉ ይሳካልሃል።” (ምሳሌ 16:3) መንፈሳዊ እርዳታ ከሚያስፈልጋቸው ጋር በምትወያይበት ጊዜ ልጠቀምባቸው እችላለሁ ብለህ በምታስባቸው የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶችና እምነት የሚያጠናክሩ ነጥቦች ላይ አሰላስል። ሐዋርያው ጳውሎስ የተወውን ግሩም ምሳሌ ቆም ብለህ አስብ። (ሮሜ 1:11, 12ን አንብብ።) ጳውሎስ ጸንተው እንዲቆሙ የሚያስችላቸውን መንፈሳዊ ስጦታ ሊያካፍላቸው ስለፈለገ በሮም ያሉ ክርስቲያኖችን ለማየት ይጓጓ ነበር። በተጨማሪም እርስ በርስ መበረታታት የሚችሉበትን አጋጣሚ በጉጉት ይጠባበቅ ነበር። እኛስ ከአምላክ መንጋ ወጥተው የባዘኑትን በጎች ለመርዳት በምናስብበት ጊዜ ተመሳሳይ የሆነ መንፈስ ማሳየት አይኖርብንም?

13. ከአንድ የቀዘቀዘ ክርስቲያን ጋር ስለ ምን ጉዳዮች መወያየት ትችላላችሁ?

13 በጥናቱ ወቅት “እውነትን የሰማኸው እንዴት ነው?” ብለህ መጠየቅ ትችላለህ። የቀዘቀዘው ሰው በጉባኤና በትልልቅ ስብሰባዎች ላይ ይገኝ እንዲሁም በስብከቱ ሥራ ይካፈል በነበረበት ጊዜ ያገኛቸውን ደስ የሚሉ ተሞክሮዎች እንዲናገር በማበረታታት ድሮ ያሳለፈውን አስደሳች ጊዜ እንዲያስታውስ አድርገው። በይሖዋ አገልግሎት አብራችሁ ያሳለፋችሁት አስደሳች ጊዜ ካለ ያንን ጥቀስለት። ወደ ይሖዋ በመቅረብህ ስላገኘኸው ደስታ ንገረው። (ያዕ. 4:8) አምላክ ለእኛ ለሕዝቦቹ እንክብካቤ ስለሚያደርግበት መንገድ በተለይ ደግሞ መከራ ሲደርስብን ስለሚሰጠን ማጽናኛና ተስፋ ያለህን አድናቆት ግለጽለት።—ሮሜ 15:4፤ 2 ቆሮ. 1:3, 4

14, 15. የቀዘቀዙ ክርስቲያኖች የትኞቹን በረከቶች እንዲያስታውሱ መርዳት ጠቃሚ ሊሆን ይችላል?

14 የቀዘቀዘው ክርስቲያን በጉባኤ ውስጥ ጥሩ እንቅስቃሴ ያደርግ በነበረበት ጊዜ ያገኛቸውን አንዳንድ በረከቶች መለስ ብሎ እንዲያስታውስ ማድረግ ጠቃሚ ሊሆን ይችላል። ለምሳሌ ያህል፣ ስለ አምላክ ቃልና ዓላማ በየጊዜው ተጨማሪ እውቀት ያገኝ ነበር። (ምሳሌ 4:18) ‘በመንፈስ ይኖር’ በነበረበት ጊዜ ኃጢአት እንዲፈጽም የሚገፋፉ ፈተናዎችን መቋቋም ይቀለው እንደነበር ግልጽ ነው። (ገላ. 5:22-26) በዚህ ምክንያት ያገኘው ንጹሕ ሕሊና ደግሞ ወደ ይሖዋ በጸሎት እንዲቀርብና ‘ከማስተዋል በላይ የሆነውን፣ ልባችንንና አሳባችንን የሚጠብቀውን የአምላክ ሰላም’ እንዲያገኝ አስችሎታል። (ፊልጵ. 4:6, 7) እነዚህን ነጥቦች በአእምሮህ ያዝ፣ ልባዊ አሳቢነት አሳይ እንዲሁም የእምነት ባልንጀራህ ወደ መንጋው እንዲመለስ ፍቅራዊ ማበረታቻ ለመስጠት የሚቻልህን ሁሉ አድርግ።—ፊልጵስዩስ 2:4ን አንብብ።

15 የእረኝነት ጉብኝት እያደረግህ ያለህ ሽማግሌ ነህ ብለን እናስብ። በመንፈሳዊ የቀዘቀዙ አንድ ባልና ሚስት በአምላክ ቃል ውስጥ የሚገኘውን እውነት መጀመሪያ የተማሩበትን ጊዜ መለስ ብለው እንዲያስታውሱ ልታበረታታቸው ትችላለህ። እውነት በጣም የሚያስደስት፣ አሳማኝ፣ አርኪና መንፈሳዊ ነፃነት የሚያስገኝ ሆኖላቸው ነበር! (ዮሐ. 8:32) ስለ ይሖዋ፣ ስለ ፍቅሩና ግሩም ስለሆኑት ዓላማዎቹ ሲማሩ ልባቸው በአመስጋኝነት ስሜት ተሞልቶ ነበር! (ከሉቃስ 24:32 ጋር አወዳድር።) ከይሖዋ ጋር ስለነበራቸው የጠበቀ ዝምድና እንዲሁም ራሳቸውን ለአምላክ የወሰኑ ክርስቲያኖች ስላላቸው ግሩም የሆነ የጸሎት መብት አስታውሳቸው። የቀዘቀዙ ክርስቲያኖች ‘ደስተኛ ለሆነው አምላክ ክብራማ ምሥራች’ ዳግም ምላሽ እንዲሰጡ ከልብ አበረታታቸው።—1 ጢሞ. 1:11 NW

ፍቅር ማሳየታችሁን ቀጥሉ

16. መንፈሳዊ እርዳታ ለመስጠት የሚደረጉ ጥረቶች በእርግጥ ውጤት እንደሚያስገኙ የሚያሳይ አንድ ምሳሌ ጥቀስ።

16 ከላይ የተጠቀሱት ሐሳቦች በእርግጥ ውጤት ያስገኛሉ? አዎ፣ ያስገኛሉ። በ12 ዓመቱ የመንግሥቱ ምሥራች አስፋፊ የነበረና በ15 ዓመቱ የቀዘቀዘ የአንድን ወጣት ሁኔታ እንደ ምሳሌ እንውሰድ። ይህ ወንድም ከጊዜ በኋላ እንደገና የተነቃቃ ሲሆን ከ30 ለሚበልጡ ዓመታት በሙሉ ጊዜ አገልግሎት ውስጥ ሲካፈል ቆይቷል። በመንፈሳዊ እንዲያንሰራራ ያስቻለው ዋነኛው ምክንያት አንድ ክርስቲያን ሽማግሌ የሰጠው እርዳታ ነው። ይህ ወንድም ላገኘው መንፈሳዊ እርዳታ እጅግ አመስጋኝ ነው!

17, 18. ከአምላክ መንጋ ወጥቶ የባዘነን ሰው ለመርዳት የትኞቹን ባሕርያት ማንጸባረቅ ሊያስፈልግህ ይችላል?

17 ክርስቲያኖች በመንፈሳዊ የቀዘቀዙትን ወደ ጉባኤ እንዲመለሱ ለመርዳት የሚያነሳሳቸው ፍቅር ነው። ኢየሱስ ተከታዮቹን በተመለከተ እንዲህ ብሏል፦ “አዲስ ትእዛዝ እሰጣችኋለሁ፤ ይኸውም እርስ በርሳችሁ እንድትዋደዱ ነው፤ እንግዲህ እኔ እንደ ወደድኋችሁ እናንተም እርስ በርሳችሁ ተዋደዱ። እርስ በርሳችሁ ብትዋደዱ፣ ሰዎች ሁሉ የእኔ ደቀ መዛሙርት እንደ ሆናችሁ በዚህ ያውቃሉ።” (ዮሐ. 13:34, 35) አዎ፣ ፍቅር የእውነተኛ ክርስቲያኖች መለያ ነው። በመንፈሳዊ ለቀዘቀዙ የተጠመቁ ክርስቲያኖች እንዲህ ዓይነት ፍቅር ልናሳያቸው አይገባም? ምንም ጥያቄ የለውም! ሆኖም እነሱን በምንረዳበት ጊዜ የተለያዩ ክርስቲያናዊ ባሕርያትን ማሳየት ያስፈልገናል።

18 ከአምላክ መንጋ ወጥቶ የባዘነን ሰው መርዳት ብትፈልግ የትኞቹን ባሕርያት ማሳየት ሊኖርብህ ይችላል? ከፍቅር በተጨማሪ ርኅራኄን፣ ደግነትን፣ ገርነትንና ትዕግሥትን ማሳየት ሊያስፈልግህ ይችላል። ይቅር ባይ እንድትሆን የሚያስገድዱ ሁኔታዎችም ሊያጋጥሙህ ይችላሉ። ጳውሎስ እንዲህ ሲል ጽፏል፦ “ርኅራኄን፣ ቸርነትን፣ ትሕትናን፣ ጨዋነትንና ትዕግሥትን ልበሱ፤ እርስ በርሳችሁ ተቻቻሉ፤ ከእናንተ አንዱ በሌላው ላይ ቅር የተሰኘበት ነገር ቢኖር ይቅር ተባባሉ፤ ጌታ ይቅር እንዳላችሁ እናንተም ሌላውን ይቅር በሉ። በእነዚህ ሁሉ ላይ ሁሉን በፍጹም አንድነት የሚያስተሳስረውን ፍቅርን ልበሱት።”—ቈላ. 3:12-14

19. በግ መሰል ሰዎች ወደ ክርስቲያን ጉባኤ እንዲመለሱ ለመርዳት የምናደርገው ጥረት አያስቆጭም የምንለው ለምንድን ነው?

19 በዚህ መጽሔት ላይ የሚገኘው ቀጣዩ የጥናት ርዕስ አንዳንዶች ከአምላክ መንጋ ወጥተው የሚባዝኑበትን ምክንያት ይገልጻል። በተጨማሪም ወደ መንጋው በሚመለሱበት ጊዜ ምን ዓይነት አቀባበል ይደረግልናል ብለው መጠበቅ እንደሚችሉ ይጠቁማል። ይህን የጥናት ርዕስ በአእምሮህ ይዘህ ቀጣዩን ርዕስ በምታጠናበት ጊዜ በግ መሰል ሰዎች ወደ ክርስቲያን ጉባኤ ይመለሳሉ በሚል ተስፋ እነሱን ለመርዳት የምታደርገው ጥረት ሁሉ ፈጽሞ እንደማያስቆጭ እርግጠኛ ሁን። በዚህ ሥርዓት ውስጥ ብዙ ሰዎች በሕይወት ዘመናቸው በሙሉ ሀብት ለማካበት ይደክማሉ፤ ይሁንና የአንድ ሰው ሕይወት ብቻ እንኳ በዓለም ላይ ካለው ገንዘብ ሁሉ እጅግ የላቀ ዋጋ አለው። ኢየሱስ ስለጠፋው በግ በተናገረው ምሳሌ ላይ ለዚህ ጉዳይ አጽንዖት ሰጥቷል። (ማቴ. 18:12-14) ከጉባኤ ርቀው የባዘኑትን የይሖዋን ውድ በጎች ወደ መንጋው ለመመለስ በጥድፊያ ስሜት ልባዊ ጥረት በምታደርግበት ጊዜ ሕይወታቸው ትልቅ ዋጋ እንዳለው ምንጊዜም አትርሳ።

ምን ብለህ ትመልሳለህ?

• ክርስቲያን እረኞች ከመንጋው ወጥተው የባዘኑትን በጎች በተመለከት ምን ኃላፊነት አለባቸው?

• በአሁኑ ጊዜ ከጉባኤ የራቁትን መርዳት የምትችለው እንዴት ነው?

• ከመንጋው ወጥተው የባዘኑትን ለመርዳት የትኞቹን ባሕርያት ማንጸባረቅ ሊረዳህ ይችላል?

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 10 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ክርስቲያን እረኞች ከአምላክ መንጋ ወጥተው የባዘኑትን ሰዎች ለመርዳት በፍቅር ተነሳስተው ጥረት ያደርጋሉ