በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምን ያህል ገንዘብ ማዋጣት ይኖርብኛል?

ምን ያህል ገንዘብ ማዋጣት ይኖርብኛል?

አንባቢያን የሚያነሱት ጥያቄ

ምን ያህል ገንዘብ ማዋጣት ይኖርብኛል?

‘አምላክ በደስታ የሚሰጠውን ሰው ይወዳል።’ (2 ቆሮንቶስ 9:7) በዓለም ዙሪያ የሚኖሩ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች ይህን አባባል ያውቁታል። ይሁንና ወደ አብያተ ክርስቲያናት የሚሄዱ በርካታ ሰዎች ከአቅማቸው በላይ እንዲያዋጡ እንደሚጠበቅባቸው ይሰማቸዋል። እንዲያውም አንዳንድ ሃይማኖታዊ ድርጅቶች አባሎቻቸው የተወሰነ መጠን ያለው ገንዘብ እንዲያዋጡ ይጠብቁባቸዋል። እንዲህ ያለው መዋጮ የማድረግ ሥርዓት አሥራት ተብሎ ይጠራል፤ አንድ ሰው አሥራት ከፈለ ሲባል የገቢውን 10 በመቶ ለቤተ ክርስቲያን ሰጠ ማለት ነው።

መጽሐፍ ቅዱስ የተወሰነ መጠን ያለው ገንዘብ እንድናዋጣ ያዛል? ከሆነ ‘ምን ያህል ገንዘብ ማዋጣት ይኖርብኛል?’ ብለህ ራስህን ትጠይቅ ይሆናል።

በጥንት ዘመን በግዴታና በፈቃደኝነት ይደረጉ የነበሩ መዋጮዎች

መጽሐፍ ቅዱስ አምላክ፣ እስራኤላውያን ምን ያህል እንዲያዋጡ ይጠብቅባቸው እንደነበር የሚያሳይ ግልጽ መመሪያ ይዟል። (ዘሌዋውያን 27:30-32፤ ዘኍልቍ 18:21, 24፤ ዘዳግም 12:4-7, 11, 17, 18፤ 14:22-27) እስራኤላውያን እንዲያዋጡ ይጠበቁባቸው የነበሩት መዋጮዎች ከአቅማችው በላይ አልነበሩም። ይሖዋ፣ ሕዝቦቹ ሕጉን ሲታዘዙ “የተትረፈረፈ ብልጽግና” በመስጠት እንደሚባርካቸው ቃል ገብቶላቸው ነበር።—ዘዳግም 28:1, 2, 11, 12

በሌሎች ጊዜያት ደግሞ እስራኤላውያን በፈቃደኝነት ተነሳስተው የቻሉትን ወይም የፈለጉትን ያህል መስጠት ይችሉ ነበር። ለምሳሌ ያህል፣ ንጉሥ ዳዊት ለይሖዋ ቤተ መቅደስ ለመገንባት ዝግጅት ባደረገበት ወቅት በእሱ ግዛት ሥር የነበሩት ሰዎች “አምስት ሺህ መክሊት ወርቅ” ሰጥተው ነበር። * (1 ዜና መዋዕል 29:7) ይህን ስጦታ ኢየሱስ በምድር ላይ በነበረበት ወቅት ከተመለከተው ነገር ጋር እስቲ አወዳድር። ኢየሱስ “አንዲት ድሃ መበለት በጣም አነስተኛ ዋጋ ያላቸው ሁለት ትናንሽ ሳንቲሞች” በመዋጮ ዕቃዎቹ ስትከት ተመለከተ። ይህች ሴት የሰጠችው ገንዘብ ምን ያህል ዋጋ ነበረው? የአንድ ቀን ደሞዝ 1/64ኛ ብቻ ያህል ነበር። ይሁንና ኢየሱስ በጣም አነስተኛ ዋጋ ያለው ይህ ገንዘብ በአምላክ ዘንድ ተቀባይነት እንዳለው ተናግሯል።—ሉቃስ 21:1-4

ክርስቲያኖች የተወሰነ መጠን ያለው ገንዘብ እንዲያዋጡ ይጠበቅባቸዋል?

ክርስቲያኖች ለእስራኤላውያን በተሰጠው የሕግ ቃል ኪዳን ሥር አይደሉም። በመሆኑም የተወሰነ መጠን ያለው ገንዘብ እንዲያዋጡ አይገደዱም። ይሁን እንጂ በእውነተኛው የክርስቲያን ጉባኤ ውስጥ ያሉ ሰዎች መስጠት ታላቅ ደስታ እንደሚያስገኝ ያውቃሉ። ኢየሱስ ራሱ “ከመቀበል ይልቅ መስጠት የበለጠ ደስታ ያስገኛል” በማለት ተናግሯል።—የሐዋርያት ሥራ 20:35

የይሖዋ ምሥክሮች በዓለም ዙሪያ የሚያካሂዱት የስብከት ሥራ የሚደገፈው በፈቃደኝነት በሚደረጉ የገንዘብ መዋጮዎች ነው። እነዚህ መዋጮዎች፣ አንተ አሁን እያነበብከው ያለኸውን መጽሔት ጨምሮ ሌሎች ጽሑፎችን ለማተም እንዲሁም የመንግሥት አዳራሾች በመባል የሚጠሩትን የአምልኮ ቦታዎች ለመገንባትና ለማደስ ይውላሉ። የሚሰበሰበው መዋጮ ለሠራተኞች ደሞዝ ለመክፈል አይውልም። ደቀ መዛሙርት በማድረጉ ሥራ ሙሉ ጊዜያቸውን የሚያሳልፉ አንዳንድ ፈቃደኛ ሠራተኞች የትራንስፖርትና ሌሎች የግል ውጪዎቻቸውን መሸፈን እንዲችሉ የገንዘብ ድጋፍ ይደረግላቸዋል። ይሁንና አንዳቸውም ቢሆኑ ይህን ገንዘብ ማግኘት መብታቸው እንደሆነ አይሰማቸውም። እንዲያውም አብዛኞቹ የይሖዋ ምሥክሮች ለሚያከናውኑት የስብከት ሥራ የገንዘብ ድጋፍ አይደረግላቸውም። ከዚህ ይልቅ ጳውሎስ ድንኳን በመስፋት የግል ወጪውን ይሸፍን እንደነበረ ሁሉ እነሱም ራሳቸውን ለመደገፍ ሰብዓዊ ሥራ ይሠራሉ።—2 ቆሮንቶስ 11:9፤ 1 ተሰሎንቄ 2:9

አንድ ሰው የይሖዋ ምሥክሮች የሚሠሩትን ሥራ በገንዘብ ለመደገፍ ቢፈልግ ምን ያህል ገንዘብ ማዋጣት ይኖርበታል? ሐዋርያው ጳውሎስ እንዲህ ሲል ጽፏል፦ “አምላክ በደስታ የሚሰጠውን ሰው ስለሚወድ እያንዳንዱ ሰው ቅር እያለው ወይም ተገዶ ሳይሆን በልቡ ያሰበውን ይስጥ።”—2 ቆሮንቶስ 8:12፤ 9:7

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.7 በ2008 የአንድ ወቄት (28 ግራም) ወርቅ አማካይ ዋጋ 871 የአሜሪካ ዶላር ነበር። እስራኤላውያኑ ያመጡት ወርቅ በዚህ ሒሳብ ሲሰላ ወደ 4,794,855,000 የሚጠጋ የአሜሪካ ዶላር ያወጣል።