በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ይሖዋ ከእኛ የሚፈልገው ምንድን ነው?

ይሖዋ ከእኛ የሚፈልገው ምንድን ነው?

ወደ አምላክ ቅረብ

ይሖዋ ከእኛ የሚፈልገው ምንድን ነው?

ዘዳግም 10:12, 13

መታዘዝ ወይስ አለመታዘዝ? በዚህ ረገድ ውሳኔ ማድረግ ሁልጊዜ ቀላል ነው ማለት አይቻልም። አንድ አለቃ ቁጡና በቀላሉ የማይረካ ቢሆን ከሥሩ ያሉት ሠራተኞች እያጉረመረሙም ቢሆን ለይስሙላ ይታዘዙት ይሆናል። ይሁንና ይሖዋ አምላክን የሚያመልኩ ሰዎች እሱን የሚታዘዙት በፈቃደኝነት ነው። እንዲህ የምንለው ለምንድን ነው? ለዚህ መልስ ለማግኘት ሙሴ በዘዳግም 10:12, 13 ላይ የተናገረውን ሐሳብ እንመርምር። *

ሙሴ፣ አምላክ ሕዝቡ እንዲያሟሉ የሚጠብቅባቸውን ብቃቶች ጠቅለል አድርጎ ሲገልጽ “አምላክህ እግዚአብሔር ከአንተ የሚፈልገው ምንድን ነው?” የሚል ጥያቄ አቅርቦ ነበር። (ቁጥር 12) አምላክ ከእኛ የሚፈልገውን ማንኛውንም ነገር የመጠየቅ መብት አለው። እንዲህ የምንለው ሉዓላዊ ጌታና የሕይወት ምንጭ እንዲሁም በሕይወት እንድንቀጥል የሚያስፈልጉንን ነገሮች የሚሰጠን እሱ በመሆኑ ነው። (መዝሙር 36:9፤ ኢሳይያስ 33:22) ይሖዋ እንድንታዘዘው የመጠየቅ መብት አለው። ይሁን እንጂ በግድ እንድንታዘዘው አይፈልግም። ታዲያ ከእኛ ምን ይፈልጋል? ‘ከልብ እንድንታዘዘው’ ይፈልጋል።—ሮም 6:17

አምላክን በፈቃደኝነት ለመታዘዝ የሚያነሳሳን ምክንያት ምንድን ነው? ሙሴ አንደኛውን ምክንያት ሲገልጽ ‘አምላክህን ይሖዋን ፍራ’ ብሏል። * (ቁጥር 12) ይህ ሲባል ቅጣት ይደርስብናል ብሎ በፍርሃት መራድ ማለት ሳይሆን ለአምላክና ለትእዛዛቱ አክብሮታዊ ፍርሃት ማሳየት ማለት ነው። ለአምላክ ጥልቅ አክብሮት ካለን እሱን የሚያሳዝን ነገር ላለማድረግ ጥረት እናደርጋለን።

ይሁን እንጂ አምላክን ለመታዘዝ በዋነኝነት የሚያነሳሳን ምክንያት ምን ሊሆን ይገባል? ሙሴ ‘አምላክህን ይሖዋን ውደደው፤ በፍጹም ልብህና በፍጹም ነፍስህ አገልግለው’ በማለት ተናግሯል። (ቁጥር 12) አምላክን መውደድ ከስሜት የበለጠ ነገር ይጠይቃል። አንድ የማመሳከሪያ ጽሑፍ “ስሜትን የሚገልጹ የዕብራይስጥ ግሶች አንዳንድ ጊዜ ስሜቱን ተከትሎ የሚመጣውን ድርጊት ጭምር ያመለክታሉ” ብሏል። ይኸው ጽሑፍ አምላክን መውደድ ሲባል እሱን “እንደምንወደው በሚያሳይ መንገድ መኖር” ማለት እንደሆነ ተናግሯል። በሌላ አባባል አምላክን ከልብ የምንወደው ከሆነ እሱን የሚያስደስተውን ነገር እናደርጋለን።—ምሳሌ 27:11

አምላክን የምንታዘዘው እስከ ምን ድረስ ነው? ሙሴ ‘በመንገዶቹ ሁሉ ሂድ’ በማለት ተናግሯል። (ቁጥር 12) ይሖዋ፣ እሱ የሚጠብቅብንን ማንኛውንም ነገር እንድናደርግ ይፈልጋል። እንዲህ ያለው ፍጹም ታዛዥነት ፍላጎታችንን የሚጋፋ ነው? በፍጹም አይደለም።

ለይሖዋ በፈቃደኝነት መታዘዛችን በረከት ያስገኝልናል። ሙሴ ‘መልካም እንዲሆንልህ ዛሬ እኔ የምሰጥህን ትእዛዞች ጠብቅ’ በማለት ጽፏል። (ቁጥር 13) አዎን፣ ይሖዋ ማንኛውንም ትእዛዝ የሚሰጠን ማለትም ከእኛ የሚፈልገውን ማንኛውንም ነገር እንድንፈጽም የሚጠብቅብን ለእኛ መልካም እንዲሆንልን በማሰብ ነው። እንዲህ ብለን ማመናችን ተገቢ ነው፤ ምክንያቱም መጽሐፍ ቅዱስ “አምላክ ፍቅር ነው” ይላል። (1 ዮሐንስ 4:8) ይሖዋ እነዚህን ትእዛዛት የሰጠው ዘላቂ ጥቅም እንድናገኝ በማሰብ ብቻ ነው። (ኢሳይያስ 48:17) ይሖዋ እንድናደርግ ያዘዘውን ነገር ሁሉ መፈጸማችን በአሁኑ ወቅት ተስፋ ከሚያስቆርጡ ብዙ ችግሮች የሚጠብቀን ሲሆን ወደፊት ደግሞ መንግሥቱ ምድርን በሚያስተዳድርበት ጊዜ ማለቂያ የሌለው በረከት ያስገኝልናል። *

ይሖዋ ከእኛ ከሚፈልገው ነገር ጋር በተያያዘ ‘የመታዘዝ ወይስ ያለመታዘዝ’ ጉዳይ ከተነሳ ጥበብ የተሞላበት ምርጫ የሚሆነው አንድ ብቻ ነው። ይህም ምንጊዜም ቢሆን ይሖዋን በፈቃደኝነት ተነሳስተን በሙሉ ልብ መታዘዝ ነው። እንዲህ ያለውን የታማኝነት ጎዳና መከተላችን ምንጊዜም ለእኛ መልካም የሆነውን ነገር ወደሚያስብልን ወደ ይሖዋ ይበልጥ እንድንቀርብ ይረዳናል።

[የግርጌ ማስታወሻዎች]

^ አን.1 ሙሴ ይህን ሐሳብ የተናገረው ለጥንቶቹ እስራኤላውያን ቢሆንም መሠረታዊ ሥርዓቱ በዛሬው ጊዜ አምላክን ማስደሰት ለሚፈልጉ ሁሉ ይሠራል።—ሮም 15:4

^ አን.3 ሙሴ ‘አምላክን መፍራት’ የአምላክ አገልጋዮች ሊመሩበት የሚገባ መሠረታዊ ሥርዓት እንደሆነ በዘዳግም መጽሐፍ ውስጥ አበክሮ ገልጿል።—ዘዳግም 4:10፤ 6:13, 24፤ 8:6፤ 13:4፤ 31:12, 13

^ አን.6 ተጨማሪ ማብራሪያ ለማግኘት ትክክለኛው የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ምንድን ነው? በተባለው መጽሐፍ ምዕራፍ 3 ላይ የሚገኘውን “አምላክ ለምድር ያለው ዓላማ ምንድን ነው?” የሚለውን ርዕስ ተመልከት። ይህ መጽሐፍ የተዘጋጀው በይሖዋ ምሥክሮች ነው።