በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

አምላክ ባደረገው ነገር ይጸጸታል?

አምላክ ባደረገው ነገር ይጸጸታል?

ወደ አምላክ ቅረብ

አምላክ ባደረገው ነገር ይጸጸታል?

መሳፍንት 2:11-18

ፍጹማን ባለመሆናችን ምክንያት ሁላችንም ባደረግነው ነገር የምንጸጸትበት ጊዜ አለ። ለምሳሌ ያህል፣ ስህተት እንደሠራን ስናውቅ ልናዝን እንችላለን። የሚገርመው ነገር መጽሐፍ ቅዱስ ይሖዋም ጸጸት እንደሚሰማው ይናገራል። እንዲህ ሲባል ግን ‘አምላክ ፍጹም ነው፤ ስህተት አይሰራም!’ ብለህ ትናገር ይሆናል። ታዲያ አምላክ የሚጸጸተው እንዴት ነው? ለዚህ ጥያቄ የምናገኘው መልስ አንድ የሚያስገርም ነገር እንድንገነዘብ ይረዳናል፤ ይኸውም ይሖዋ ስሜት እንዳለውና የምናደርገው ነገር ሊያስደስተው ወይም ሊያሳዝነው የሚችል መሆኑ ነው። እስቲ በመሳፍንት 2:11-18 ላይ ተመዝግቦ የሚገኘውን ታሪክ እንመልከት።

በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኘው የመሳፍንት መጽሐፍ በእስራኤል ታሪክ ውስጥ ሁከት ስለነገሠበት ዘመን ዘግቧል። በዚህ ወቅት የእስራኤል ብሔር አምላክ ለአብርሃም ቃል በገባለት በከነዓን ምድር ሰፍሮ ነበር። ከዚያ በኋላ በነበሩት መቶ ዓመታት እስራኤላውያን በተደጋጋሚ ይከተሉት የነበረውን አካሄድ በአራት ነገሮች ጠቅለል አድርጎ መግለጽ ይቻላል። እነሱም ዓመፅ፣ ጭቆና፣ ልመና እና ነፃ መውጣት ናቸው። *

ዓመፅ። እስራኤላውያን በከነዓናውያን ተጽዕኖ ተሸንፈው ‘ይሖዋን በመተው’ ሌሎች አማልክትን በተለይም “በኣልንና አስታሮትን” ማምለክ ጀመሩ። * በዚህ መንገድ በይሖዋ አምልኮ ላይ ማመፅ ክህደት ነበር። ከግብፅ ነፃ ያወጣቸው አምላክ በእስራኤላውያን ላይ ‘መቆጣቱ’ ምንም አያስገርምም።—ቁጥር 11-13መሳፍንት 2:1

ጭቆና። ይሖዋ የጽድቅ ቁጣ በመቆጣት ጀርባቸውን ለሰጡት ለእስራኤላውያን ጥበቃ ማድረጉን ይተዋል። በዚህ ጊዜ እስራኤላውያን ምድሪቱን በሚዘርፉ ‘ጠላቶቻቸው’ እጅ ይወድቃሉ።—ቁጥር 14

ልመና። እስራኤላውያን እጅግ ሲጨነቁ የተከተሉት ጎዳና ስህተት እንደሆነ ተገንዝበው አምላክ እንዲረዳቸው ወደ እሱ መጮኽ ይጀምራሉ። ‘ከጠላቶቻቸው ሥቃይና መከራ ሲደርስባቸው መጮኻቸው’ ይሖዋ እንዲረዳቸው መለመናቸውን የሚያሳይ ሊሆን ይችላል። (ቁጥር 18) ወደ አምላክ ልመና ማቅረባቸው በተደጋጋሚ የሚከሰት ነገር ነበር። (መሳፍንት 3:9, 15፤ 4:3፤ 6:6, 7፤ 10:10) ታዲያ አምላክ ምን ምላሽ ይሰጣቸው ነበር?

ነፃ መውጣት። ይሖዋ የእስራኤላውያንን ጩኸት ሰምቶ ‘ይጸጸት’ ነበር። ‘ጸጸት’ ተብሎ የተተረጎመው የዕብራይስጥ ቃል “ሐሳብን ወይም አመለካከትን መለወጥ” የሚል ትርጉም ሊኖረው ይችላል። አንድ የማመሳከሪያ ጽሑፍ እንዲህ በማለት አስቀምጦታል፦ “ይሖዋ በሚያሰሙት ጩኸት የተነሳ እነሱን ለመቅጣት የነበረውን ሐሳብ በመተው ነፃ ያወጣቸው ነበር።” ይሖዋ በምሕረቱ ተነሳስቶ ሕዝቡን ከጠላቶቻቸው ነፃ የሚያወጣ ‘መሳፍንት ያስነሳላቸው’ ነበር።—ቁጥር 18 NW

አምላክ እንዲጸጸት ወይም ሐሳቡን እንዲለውጥ ያነሳሳው ምን እንደሆነ አስተዋልክ? ሕዝቡ አመለካከቱን መለወጡ ነበር። እስቲ ነገሩን በዚህ መንገድ አስበው፦ አንድ አፍቃሪ አባት ልጁ ጥፋት ሲያጠፋ አንዳንድ ነገሮችን በመከልከል ይቀጣው ይሆናል። ሆኖም አባትየው ልጁ ባደረገው ነገር ከልቡ እንዳዘነ ሲመለከት ቅጣቱን ሊያነሳለት ይችላል።

ታዲያ ከዚህ ዘገባ ስለ ይሖዋ ምን እንማራለን? አንድ ሰው ሆን ብሎ የሚፈጽመው ኃጢአት እንደሚያስቆጣው ሁሉ ከልቡ ንስሐ ሲገባ ደግሞ ምሕረት ለማሳየት ይገፋፋል። የምናደርገው ነገር በአምላክ ስሜት ላይ ለውጥ እንደሚያመጣ ማወቃችን ቆም ብለን እንድናስብ ያደርገናል። እንግዲያው የይሖዋን ‘ልብ ደስ ለማሰኘት’ ምን ማድረግ እንደምትችል ለምን አትማርም? (ምሳሌ 27:11) እንዲህ በማድረግህ ፈጽሞ አትጸጸትም።

[የግርጌ ማስታወሻዎች]

^ አን.2 በመሳፍንት 2:11-18 ላይ የሚገኘው ዘገባ እስራኤላውያን በተደጋጋሚ ይከተሉት የነበረውን አካሄድ ለመጀመሪያ ጊዜ ይጠቅሳል፤ ይህ አካሄድ በቀጣዮቹ ምዕራፎች ውስጥ በዝርዝር ተገልጿል።

^ አን.3 በኣል ትልቅ ስፍራ የሚሰጠው የከነዓናውያን አምላክ ሲሆን አስታሮት ደግሞ የበኣል ሚስት እንደሆነች ተደርጋ የምትታሰብ እንስት አምላክ ነች።