በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ልጆቻችሁን አስተምሩ

ርብቃ ይሖዋን ለማስደሰት ፈቃደኛ ነበረች

ርብቃ ይሖዋን ለማስደሰት ፈቃደኛ ነበረች

በዛሬው ጊዜ በተለያዩ አገሮች ርብቃ የሚለው ስም የተለመደ ነው። አንተስ ርብቃ በሚል ስም የምትጠራ ሴት ታውቃለህ?— * ርብቃ በዓለም ላይ በጣም ታዋቂ በሆነው መጽሐፍ ማለትም በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ትልቅ ቦታ የተሰጣት ሴት ናት። ስለ እሷ ምን የምታውቀው ነገር አለ?— ርብቃ የተወችው ምሳሌ እውነተኛውን አምላክ ይሖዋን እንድናገለግል ስለሚረዳን ስለ እሷ ማወቃችን ጠቃሚ ነው።

ርብቃ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በስም ከተጠቀሱት የይሖዋ አገልጋዮች መካከል ሁለተኛዋ ሴት ናት። የመጀመሪያዋ ሴት ማን እንደሆነች ታውቃለህ?— የአብርሃም ሚስት የነበረችው ሣራ ናት። ሣራ በስተርጅናዋ አንድ ልጇን ይስሐቅን ወለደች። ርብቃ ይሖዋን ለማስደሰት ፈቃደኛ የሆነችው እንዴት እንደሆነና ከይስሐቅ ጋር እንዴት እንደተገናኘች እስቲ እንመልከት።

አብርሃምና ሣራ በአምላክ ትእዛዝ ከካራን ወጥተው ወደ ከነዓን ከሄዱ 60 ዓመታት አልፈዋል። አብርሃምና ሣራ በጣም አርጅተው እያሉ አምላክ ይስሐቅ የሚባል ልጅ እንደሚወልዱ ቃል ገባላቸው። ይስሐቅ በወላጆቹ ምን ያህል እንደሚወደድ መገመት ትችላለህ። ሣራ በ127 ዓመቷ ስትሞት ልጇ ይስሐቅ ትልቅ ሰው የነበረ ሲሆን እናቱን በሞት በማጣቱ በጣም አዝኖ ነበር። አብርሃም ልጁ ይስሐቅ ከከነዓናውያን ሴቶች መካከል እንዲያገባ አልፈለገም፤ ምክንያቱም እነዚህ ሰዎች የይሖዋ አምላኪዎች አልነበሩም። በመሆኑም አብርሃም አገልጋዩን ምናልባትም ኤሊዔዘርን ሳይሆን አይቀርም ከ800 ኪሎ ሜትር ርቀት በላይ ወደምትገኘው ወደ ካራን ላከው፤ አገልጋዩን ወደዚያ የላከው ከዘመዶቹ መካከል ለይስሐቅ ሚስት እንዲያመጣለት ነበር።—ዘፍጥረት 12:4, 5፤ 15:2፤ 17:17, 19፤ 23:1

ከጊዜ በኋላም ኤሊዔዘር ስንቅና ለሙሽሪት የሚሆኑ ስጦታዎችን በአሥር ግመሎች ላይ ጭኖ ከሌሎች የአብርሃም አገልጋዮች ጋር ካራን ደረሰ። ኤሊዔዘር፣ ሰዎች ከሰዓት በኋላ ከብቶቻቸውን ለማጠጣትም ሆነ ለቤተሰቦቻቸው ውኃ ለመቅዳት እንደሚመጡ ያውቅ ስለነበር የውኃ ጉድጓድ አጠገብ ሲደርሱ አረፍ አሉ። ከዚያ በኋላ ኤሊዔዘር፣ ‘ውኃ አጠጪኝ ሲላት “እንካ ጠጣ፤ ግመሎችህንም ላጠጣልህ” ብላ የምትመልስለትን ቆንጆ ለይስሐቅ ሚስት’ አድርጎ እንደሚመርጣት በመግለጽ ወደ ይሖዋ ጸለየ።

የሆነውም ልክ እንደዚሁ ነበር! “እጅግ ውብ” የሆነችው ርብቃ ወደ ጉድጓዱ መጣች። ኤሊዔዘር ውኃ እንድታጠጣው ሲጠይቃት ይህች ወጣት ‘ለግመሎችህም ውሃ እቀዳላቸዋለሁ’ አለችው። ርብቃ ‘እየሮጠች ከጕድጓዱ ውሃ ስታመላልስ’ ኤሊዔዘር “በአንክሮ” ይከታተላት ነበር። እስቲ አስበው፣ የተጠሙትን አሥር ግመሎች እስኪጠግቡ ድረስ ለማጠጣት ርብቃ 1,000 ሊትር ውኃ ማመላለስ ነበረባት!

ኤሊዔዘር፣ ርብቃ ውኃ አጠጥታ ስትጨርስ የሚያማምሩ ስጦታዎችን ሰጣት። ርብቃ የማን ልጅ እንደሆነች ሲጠይቅ የአብርሃም ዘመድ የሆነው የባቱኤል ልጅ እንደሆነች አወቀ። ርብቃም ኤሊዔዘርንና ጓደኞቹን በቤተሰቦቿ ቤት ‘እንዲያድሩ’ ጋበዘቻቸው። ከዚያም ሮጣ በመሄድ ለቤተሰቦቿ አብርሃም እነሱን ለመጠየቅ ከከነዓን ሰዎችን እንደላከ ነገረቻቸው።

የርብቃ ወንድም ላባ፣ ለእህቱ የተሰጣትን ውድ የሆኑ ስጦታዎችን ሲመለከትና ኤሊዔዘር ማን እንደሆነ ሲያውቅ ወደ ቤት እንዲገባ ጋበዘው። ይሁንና ኤሊዔዘር “የመጣሁበትን ጕዳይ ሳልናገር እህል አልቀምስም” አለ። ከዚያም አብርሃም ለምን ጉዳይ እንደላከው ተናገረ። ባቱኤል፣ ባለቤቱና ላባ በሁኔታው የተደሰቱ ሲሆን በጋብቻውም ተስማሙ።

ኤሊዔዘርና ጓደኞቹ እህል ከበሉ በኋላ እዚያው አደሩ። በማግስቱ ጠዋት ኤሊዔዘር “እንግዲህ ወደ ጌታዬ እንድመለስ አሰናብቱኝ” አለ። ይሁንና የርብቃ እናትና ወንድም “ቢያንስ ዐሥር ቀን ያህል” እንድትቆይ ፈለጉ። ይሁን እንጂ ርብቃ ወዲያውኑ መሄድ ትፈልግ እንደሆነ ስትጠየቅ “አዎን፤ እሄዳለሁ” ብላ መለሰች። በዚህም ምክንያት የዚያኑ ዕለት ከኤሊዔዘር ጋር ሄደች። ከነዓንም ሲደርሱ ርብቃ የይስሐቅ ሚስት ሆነች።—ዘፍጥረት 24:1-58, 67

ርብቃ ምናልባትም እንደገና እንደማታገኛቸው እያወቀች ቤተሰቦቿንና ጓደኞቿን ትታ በጣም ሩቅ ወደሆነ ቦታ መሄዷ ቀላል ይመስልሃል?— ቀላል አይደለም። ይሁንና ርብቃ ይሖዋን ደስ የሚያሰኘውን ለማድረግ ፈቃደኛ በመሆኗ ተባርካለች። አዳኛችን የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ የተወለደው በእሷ ዘር በኩል ነው። እኛም ይሖዋን የሚያስደስተውን ነገር ለማድረግ እንደ እሷ ፈቃደኛ ከሆንን እንባረካለን።—ሮም 9:7-10

^ አን.3 ይህን ርዕስ የምታነበው ከልጆች ጋር ከሆነ፣ ይህ ሰረዝ የተደረገው ቆም ብለህ ጥያቄውን ለልጆቹ እንድታቀርብላቸው ለማስታወስ ተብሎ ነው።