በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ይህን ያውቁ ኖሯል?

ይህን ያውቁ ኖሯል?

ይህን ያውቁ ኖሯል?

ጳውሎስ በአንደኛ ቆሮንቶስ ላይ ለጣዖት ስለተሠዋ ሥጋ ያነሳው ለምን ነበር?

ሐዋርያው ጳውሎስ “ከሕሊናችሁ የተነሳ ምንም ጥያቄ ሳታነሱ በሥጋ ገበያ የሚሸጠውን ሁሉ ብሉ” በማለት ጽፎ ነበር። (1 ቆሮንቶስ 10:25) ይህ ሥጋ የሚመጣው ከየት ነበር?

በግሪካውያንና በሮማውያን ቤተ መቅደስ ውስጥ እንስሳትን መሥዋዕት ማድረግ የአምልኮቱ ሥነ ሥርዓት ዋነኛ ክፍል ነበር፤ ሆኖም መሥዋዕት የሚደረገው እንስሳ የተወሰነ ክፍል በሥነ ሥርዓቱ ላይ አይበላም ነበር። በመሆኑም በጣም ብዙ ሥጋ ከአረማውያን ቤተ መቅደስ ወጥቶ በሥጋ ገበያ ይሸጥ ነበር። አይድል ሚት ኢን ኮሪንዝ የተባለው መጽሐፍ እንዲህ ብሏል፦ “የአምልኮ ሥነ ሥርዓቱን የሚያከናውኑ ሰዎች . . . ምግብ አብሳይ ወይም ሉካንዳ ነጋዴ ተብለው የሚጠሩበት ጊዜም ነበር። እነዚህ ሰዎች እንስሳውን በማረዳቸው ምክንያት በክፍያ መልክ ከሚሰጣቸው ሥጋ ላይ የተወሰነውን ይሸጡት ነበር።”

በዚህም ምክንያት በሥጋ ገበያ ላይ የሚሸጠው ሥጋ በሙሉ ከሃይማኖታዊ ሥነ ሥርዓቱ የተረፈ ሥጋ ነው ማለት አይቻልም። በፓምፔ የሥጋ ገበያ (በላቲን፣ ማኬለም) ላይ በተደረገ የመሬት ቁፋሮ የበጎች ሙሉ አፅም ተገኝቷል። ሄንሪ ካድበሪ የተባሉ ምሑር እንደገለጹት ይህ ሁኔታ፣ “በቤተ መቅደሱ የታረዱ ወይም የተሠዉ እንስሳት ሥጋ ብቻ ሳይሆን እንስሳቱ ከነሕይወታቸው አሊያም እዚያው ማኬለም ታርደው ይሸጡ እንደነበር” ይጠቁማል።

እዚህ ጥቅስ ላይ ጳውሎስ፣ ክርስቲያኖች በአረማውያን አምልኮ ባይካፈሉም እንኳ በቤተ መቅደስ መሥዋዕት ሆኖ የሚቀርበውን እንስሳ ሥጋ ሊገዙ እንደሚችሉ መግለጹ ነበር፤ ምክንያቱም እንስሳው በቤተ መቅደስ መሥዋዕት ሆኖ መቅረቡ ብቻውን ሥጋውን የረከሰ እንዲሆን አያደርገውም።

በኢየሱስ ዘመን አይሁዳውያንና ሳምራውያን የማይስማሙት ለምን ነበር?

ዮሐንስ 4:9 ‘አይሁዳውያን ከሳምራውያን ጋር ምንም ግንኙነት አልነበራቸውም’ ይላል። ይህ ልዩነት የተፈጠረው ኢዮርብዓም በሰሜናዊው የአሥሩ ነገድ መንግሥት ላይ የጣዖት አምልኮ ባቋቋመበት ጊዜ ይመስላል። (1 ነገሥት 12:26-30) ሳምራውያን የሰሜናዊው መንግሥት ዋና ከተማ በሆነችው በሰማርያ ይኖሩ ነበር። ከጊዜ በኋላ የሰሜናዊው መንግሥት ነዋሪዎች በሙሉ ሳምራውያን ተብለው መጠራት ጀመሩ። የአሥሩ ነገድ መንግሥት በ740 ዓ.ዓ. በአሦራውያን እጅ በወደቀበት ጊዜ የባዕድ አገር ሰዎች በመላዋ ሰማርያ እንዲሰፍሩ አደረጉ። ከጊዜ በኋላ በእነዚህ ሰፋሪዎችና በከተማዋ ነዋሪዎች መካከል የጋብቻ ዝምድና መፈጠሩ የሳምራውያን አምልኮ ይበልጥ እንዲበከል እንዳደረገ ምንም ጥርጥር የለውም።

ከበርካታ መቶ ዓመታት በኋላ ደግሞ ሳምራውያን፣ ከባቢሎን ግዞት የተመለሱት አይሁዳውያን የይሖዋን ቤተ መቅደስና የኢየሩሳሌምን ቅጥሮች ለማደስ ያደርጉት የነበረውን ጥረት ለማደናቀፍ ሞክረዋል። (ዕዝራ 4:1-23፤ ነህምያ 4:1-8) ሳምራውያን በአራተኛው መቶ ዘመን ዓ.ዓ. በገሪዛን ተራራ ላይ የራሳቸውን ቤተ መቅደስ በገነቡ ጊዜ በመካከላቸው የነበረው ሃይማኖታዊ ፉክክር እየጨመረ ሄደ።

በኢየሱስ ዘመን “ሳምራዊ” ሲባል ሰዎች ቶሎ ወደ አእምሯቸው የሚመጣው አካባቢው ሳይሆን በዚያች ከተማ የተስፋፋው ሃይማኖት ነበር። በዚያ ዘመንም ሳምራውያን በገሪዛን ተራራ ማምለካቸውን ቀጥለው የነበረ ሲሆን አይሁዳውያን በንቀት ይመለከቷቸው ነበር።—ዮሐንስ 4:20-22፤ 8:48

[በገጽ 12 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

የእንስሳ መሥዋዕትን የሚያሳይ በሸክላ ሳህን ላይ የተቀረጸ ሥዕል፣ ስድስተኛው መቶ ዘመን ዓ.ዓ.

[ምንጭ]

Musée du Louvre, Paris

[በገጽ 12 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ኢዮርብዓም የጣዖት አምልኮ አቋቋመ