በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

‘የሰውን ልብ ያውቃል’

‘የሰውን ልብ ያውቃል’

ወደ አምላክ ቅረብ

‘የሰውን ልብ ያውቃል’

2 ዜና መዋዕል 6:29, 30

በሕይወቱ ውስጥ ባጋጠሙት ተፈታታኝ ሁኔታዎችና ችግሮች የተነሳ ተስፋ ቆርጦ የማያውቅ ማን አለ? አንዳንድ ጊዜ እየታገልን ያለነውን ችግር ወይም የሚሰማንን የስሜት ሥቃይ የሚረዳልን እንደሌለ ይሰማን ይሆናል። ይሁንና ስሜታችንን ሙሉ በሙሉ ሊረዳልን የሚችል አካል ያለ ሲሆን እሱም ይሖዋ አምላክ ነው። በዚህ ረገድ እኛም በ⁠2 ዜና መዋዕል 6:29, 30 ላይ ከሚገኘው ሰለሞን ከተናገረው ሐሳብ ማጽናኛ ማግኘት እንችላለን።

ጊዜው 1026 ዓ.ዓ. ሲሆን ሰለሞን በቤተ መቅደሱ ምረቃ ላይ ጸሎት እያቀረበ ነው። ሰለሞን፣ አሥር ደቂቃ ገደማ ሊፈጅ በሚችለው በዚህ ጸሎት ላይ ይሖዋ ታማኝ፣ የሰጠውን ተስፋ የሚፈጽምና ጸሎት ሰሚ አምላክ እንደሆነ በመግለጽ ይሖዋን አወድሶታል።—1 ነገሥት 8:23-53፤ 2 ዜና መዋዕል 6:14-42

ሰለሞን፣ አምላክ አገልጋዮቹ የሚያቀርቡትን ልመና እንዲሰማ ተማጽኗል። (ቁጥር 29) ሰለሞን ብዙ ችግሮችን (ቁጥር 28) የገለጸ ቢሆንም እንያንዳንዱ የይሖዋ አገልጋይ የራሱን ‘ጭንቀት’ እንደሚያውቅና የራሱ ‘ሕመም’ እንደሚሰማው ጠቅሷል። አንድ ሰው በአንድ ጉዳይ ሲያዝን ሌላው ደግሞ ከዚያ የተለየ ችግር ይኖርበት ይሆናል።

አምላክን የሚፈሩ ሰዎች ያጋጠማቸው ችግር ምንም ይሁን ምን ችግሩን ብቻቸውን መጋፈጥ አያስፈልጋቸውም። ሰለሞን ይህን ጸሎት ያቀረበው ‘እጁን ዘርግቶ’ ወደ ይሖዋ ልባዊ ጸሎት የሚያቀርብን ማንኛውንም የአምላክ አገልጋይ በአእምሮው ይዞ ነው። ምናልባትም አባቱ ዳዊት በጣም በተጨነቀበት ወቅት “የከበደህን ነገር በእግዚአብሔር ላይ ጣል” በማለት የተናገረውን ሐሳብ አስታውሶ ሊሆን ይችላል።—መዝሙር 55:4, 22

ታዲያ ይሖዋ ከልብ የመነጨ ልመና ለሚያቀርቡ ሰዎች መልስ የሚሰጠው እንዴት ነው? ሰለሞን “በሰማይ በማደሪያህ ሆነህ ስማ፤ ይቅርም በል፤ . . . ለእያንዳንዱ እንደ ሥራው መጠን ክፈለው” በማለት ይሖዋን ተማጽኗል። (ቁጥር 30) ሰለሞን ‘ጸሎት ሰሚ’ የሆነው አምላክ ለአገልጋዮቹ በቡድን ደረጃ ብቻ ሳይሆን በግለሰብ ደረጃ እንደሚያስብም ተገንዝቦ ነበር። (መዝሙር 65:2) ይሖዋ በፍጹም ልቡ ወደ እሱ የሚመለስን ኃጢአተኛ ይቅር የሚል ከመሆኑም በላይ ግለሰቡ የሚያስፈልገውን እርዳታ ሁሉ ይሰጠዋል።—2 ዜና መዋዕል 6:36-39

ሰለሞን፣ ይሖዋ ንስሐ የገባ አንድ የአምላክ አገልጋይ የሚያቀርበውን ልመና እንደሚሰማ እርግጠኛ የነበረው ለምንድን ነው? ሰለሞን በዚያው ቁጥር ላይ “የሰውን ልብ የምታውቅ አንተ ብቻ [ነህ]” በማለት ምክንያቱን ጠቅሷል። ይሖዋ በእያንዳንዱ ታማኝ አገልጋይ ልብ ውስጥ ያለውን ጭንቀት ወይም ሕመም የሚረዳ ሲሆን የሚደርስበትም መከራ ያሳስበዋል።—መዝሙር 37:4

እኛም ሰለሞን ካቀረበው ጸሎት ማጽናኛ ማግኘት እንችላለን። ሰዎች ውስጣዊ ስሜታችንን ማለትም ‘ጭንቀታችንን’ እና ‘ሕመማችንን’ ሙሉ በሙሉ አይረዱልን ይሆናል። (ምሳሌ 14:10) ይሁንና ይሖዋ ልባችንን የሚያውቅ ከመሆኑም በላይ ስለ እኛ በጥልቅ ይስባል። በጸሎት፣ የውስጥ ስሜታችንን አውጥተን ለይሖዋ መናገራችን ሸክማችንን ቀላል ያደርግልናል። መጽሐፍ ቅዱስ “የሚያስጨንቃችሁንም ነገር ሁሉ በእሱ ላይ ጣሉ፤ ምክንያቱም እሱ ስለ እናንተ ያስባል” ይላል።—1 ጴጥሮስ 5:7