በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትልቅ ቦታ ለሚሰጠው ቀን ተዘጋጅተሃል?

ትልቅ ቦታ ለሚሰጠው ቀን ተዘጋጅተሃል?

ትልቅ ቦታ ለሚሰጠው ቀን ተዘጋጅተሃል?

ኢየሱስ ከመሞቱ ጥቂት ሰዓታት ቀደም ብሎ ሞቱን ለማሰብ የሚያስችል ለየት ያለ ዝግጅት አደረገ። ይህ ዝግጅት ‘የጌታ ራት’ በመባል ይታወቃል። (1 ቆሮንቶስ 11:20) ኢየሱስ ይህ ቀን ትልቅ ቦታ የሚሰጠው መሆኑን ለማስገንዘብ “ይህን ሁልጊዜ ለመታሰቢያዬ አድርጉት” የሚል ትእዛዝ ሰጥቷል። (ሉቃስ 22:19) አንተስ ኢየሱስ የሰጠውን ይህን መመሪያ መታዘዝ ትፈልጋለህ? ከሆነ የኢየሱስ ሞት የሚከበርበትን ዕለት በዓመቱ ውስጥ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው ቀን እንደሆነ አድርገህ ትመለከተዋለህ ማለት ነው።

ይሁንና የክርስቶስን ሞት ማሰብ ያለብህ መቼ ነው? ትልቅ ቦታ የሚሰጠው ይህ ዕለት ምን ትርጉም እንዳለው ሙሉ በሙሉ መረዳት የምትችለውስ እንዴት ነው? እያንዳንዱ ክርስቲያን እነዚህን ጥያቄዎች በጥሞና ሊያስብባቸው ይገባል።

በየስንት ጊዜው?

ትልቅ ቦታ የሚሰጣቸውን ዕለቶች አብዛኛውን ጊዜ የምናስበው በዓመት አንድ ጊዜ ነው። ለምሳሌ ያህል፣ መስከረም 11, 2001 በዓለም አቀፉ የንግድ ማዕከል ላይ በተሰነዘረው ጥቃት ሳቢያ ቤተሰባቸውንና ወዳጅ ዘመዳቸውን በሞት ያጡት የኒው ዮርክ ሲቲ ነዋሪዎች ይህ አሳዛኝ ሁኔታ ሁልጊዜ ከአእምሯቸው ባይጠፋም በየዓመቱ ያ ቀን ሲመጣ ዕለቱን ለየት ባለ መንገድ ያስቡታል።

በተመሳሳይም በጥንት ጊዜ ትልቅ ቦታ የሚሰጣቸው ዕለቶች የሚታወሱት በዓመት አንድ ጊዜ ነበር። (አስቴር 9:21, 27) እስራኤላውያን በተአምራዊ ሁኔታ ከግብፅ ባርነት ነፃ የወጡበትን ዕለት በየዓመቱ እንዲያከብሩት ይሖዋ አዟቸው ነበር። መጽሐፍ ቅዱስ ይህን በዓል ፋሲካ ብሎ የሚጠራው ሲሆን እስራኤላውያንም ነፃ የወጡበትን ያንኑ ቀን ጠብቀው ዕለቱን በዓመት አንድ ጊዜ ያከብሩት ነበር።—ዘፀአት 12:24-27፤ 13:10

ኢየሱስ የሞቱን መታሰቢያ ለማክበር እንደ ናሙና ሆኖ የሚያገለግለውን ልዩ የእራት ዝግጅት ያደረገው የፋሲካን በዓል ከሐዋርያቱ ጋር አክብሮ እንደጨረሰ ነበር። (ሉቃስ 22:7-20) ፋሲካ የሚከበረው በየዓመቱ ነበር። በመሆኑም ፋሲካን የተካው ይህ አዲስ በዓልም ሊከበር የሚገባው በዓመት አንድ ጊዜ ነው ብለን መደምደም እንችላለን። ይሁንና በየትኛው ቀን?

መቼ?

ለዚህ ጥያቄ መልስ ለማግኘት በቅድሚያ ሁለት ነገሮችን መገንዘብ ይኖርብናል። በመጀመሪያ ደረጃ፣ በጥንት ዘመን እስራኤላውያን አንድን ቀን መቆጠር የሚጀምሩት ምሽት ላይ ፀሐይ ስትጠልቅ ሲሆን ቀኑ የሚያበቃው ደግሞ በቀጣዩ ቀን ፀሐይ ስትጠልቅ ነው። በመሆኑም አንድ ቀን የሚባለው ከምሽት አንስቶ እስከሚቀጥለው ቀን ምሽት ያለው ጊዜ ነው።—ዘሌዋውያን 23:32

በሁለተኛ ደረጃ፣ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተጠቀሰው የቀን አቆጣጠር በአሁኑ ጊዜ ከምንጠቀምበት የተለየ ነው። ለምሳሌ እኛ መጋቢትና ሚያዝያ የምንላቸውን ወራት መጽሐፍ ቅዱስ አዳር እና ኒሳን በማለት ይጠራቸዋል። (አስቴር 3:7) አይሁዳውያን አንድ ወር የሚሉት አዲስ ጨረቃ ከታየችበት ዕለት አንስቶ ሌላ አዲስ ጨረቃ እስከምትታይበት ዕለት ድረስ ያለውን ጊዜ ነው። አይሁዶች ፋሲካን የሚያከብሩት በእነሱ የቀን አቆጣጠር መሠረት ኒሳን የሚባለው የመጀመሪያው ወር በገባ በ14ኛው ቀን ላይ ነበር። (ዘሌዋውያን 23:5፤ ዘኍልቍ 28:16) ሮማውያን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የሰቀሉትም በዚሁ ቀን ማለትም ኒሳን 14 ላይ ነው። ኢየሱስ የሞተው የመጀመሪያው ፋሲካ ከተከበረ ከ1,545 ዓመት በኋላ ነበር። በእርግጥም ኒሳን 14 ልዩ ቀን ነው!

ይሁንና በእኛ የቀን አቆጣጠር ኒሳን 14 የሚውለው የትኛው ቀን ላይ ነው? ቀለል ያለ ስሌት በመጠቀም ትክክለኛውን ቀን ማወቅ እንችላለን። ኒሳን 1 የሚጀምረው ለጸደይ ኢኪወኖክስ (በሰሜናዊ ንፍቀ ክበብ ላይ የቀኑና የምሽቱ ርዝመት እኩል የሚሆንበት ዕለት ነው) ቅርብ የሆነ ቀን ላይ በኢየሩሳሌም አዲስ ጨረቃ ስትታይ ነው። ከዚህ ዕለት አንስተን 14 ቀን ብንቆጥር ኒሳን 14 ላይ እንደርሳለን። አብዛኛውን ጊዜ በዚህ ዕለት ጨረቃዋ ሙሉ ትሆናለች። በዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ የቀን አቆጣጠር ስሌት መሠረት በያዝነው ዓመት ኒሳን 14 የሚውለው ሚያዝያ 9, 2003 (እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር ሚያዝያ 17, 2011) ላይ ይሆናል ማለት ነው። *

በመሆኑም በዚህ ዓመት የይሖዋ ምሥክሮች፣ የኢየሱስን ሞት መታሰቢያ ማክበር ከሚፈልጉ ሰዎች ጋር አንድ ላይ ሆነው ይህን ዕለት ለማሰብ እየተዘጋጁ ነው። አንተም በዚህ ቀን አብረሃቸው እንድትሆን በአክብሮት ይጋብዙሃል። በዓሉ የሚከበርበትን ቦታና ሰዓት ለማወቅ በአካባቢህ ያሉትን የይሖዋ ምሥክሮች መጠየቅ ትችላለህ። በዓሉን የሚያከብሩት ጠዋት ወይም ከሰዓት በኋላ ሳይሆን ምሽት ላይ ፀሐይ ከጠለቀች በኋላ ነው። ለምን? ምክንያቱም መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚነግረን ጊዜው ‘የራት’ ሰዓት ነው። (1 ቆሮንቶስ 11:25) እሁድ፣ ሚያዝያ 9, 2003 (እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር ሚያዝያ 17, 2011) ምሽት ላይ ኢየሱስ ከዛሬ 1,978 ዓመት በፊት ያቋቋመው ልዩ የመታሰቢያ በዓል ይከበራል። ኢየሱስ የሞተበት ቀን የሚጀምረውም በዚህ ምሽት ማለትም ኒሳን 14 ላይ ነው። ታዲያ የኢየሱስን ሞት ለማሰብ ከዚህ የተሻለ ቀን ሊኖር ይችላል?

ለበዓሉ መዘጋጀት የሚቻለው እንዴት ነው?

በዓመት አንዴ ለሚከበረው ለዚህ በዓል ለመዘጋጀት ከወዲሁ ምን ማድረግ ትችላለህ? ለዚህ ዕለት ራስህን ለማዘጋጀት ከሚረዱህ መንገዶች አንዱ ኢየሱስ ለእኛ ባደረገልን ነገሮች ላይ ማሰላሰል ነው። ትክክለኛው የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ምንድን ነው? * የተባለው መጽሐፍ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች የኢየሱስ ሞት ያለውን ትርጉም ይበልጥ እንዲገነዘቡ ረድቷቸዋል።—ማቴዎስ 20:28

ለዚህ ልዩ ዕለት ልባችንን ማዘጋጀት የምንችልበት ሌላው መንገድ ደግሞ ኢየሱስ በምድር ላይ ያሳለፈውን የመጨረሻ ቀን ጨምሮ ከዚያ በፊት ባለው ሳምንት ውስጥ ስለተከናወኑት ነገሮች ማንበብ ነው። በቀጣዮቹ ገጾች ላይ አንድ ሣጥን ይገኛል። በስተቀኝ ያለው የሣጥኑ ክፍል ከኢየሱስ ሞት በፊት ባለው ሳምንት የተፈጸመውን የየቀኑን ክስተት ከተለያዩ የመጽሐፍ ቅዱስ ዘገባዎች በማውጣጣት በአንድነት ያቀርባል። በተጨማሪም እነዚህ ክንውኖች እስከ ዛሬ ከኖሩት ሁሉ የሚበልጠው ታላቅ ሰው * በተባለው መጽሐፍ ውስጥ የተብራሩባቸውን ምዕራፎች ይዟል።

በስተግራ በኩል ያለው የሣጥኑ ክፍል ደግሞ ኢየሱስ ከመሞቱ በፊት ባለው ሳምንት ውስጥ የተከናወኑት ነገሮች የተፈጸሙበትን ዕለት እና ይህ ዕለት በዚህ ዓመት በየትኛው ቀን ላይ እንደሚውል ያመለክታል። የጌታ ራት የሚውልበትን ቀን ጨምሮ ከዚያ በፊት ባለው ሳምንት ውስጥ በእያንዳንዱ ቀን ስለተከናወኑት ነገሮች የሚገልጹ ቢያንስ የተወሰኑ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶችን ለምን አታነብም? ጥቂት ጊዜ በመመደብ እንዲህ ማድረግህ በዓመቱ ውስጥ ትልቅ ቦታ ለሚሰጠው ለዚያ ቀን እንድትዘጋጅ ይረዳሃል።

[የግርጌ ማስታወሻዎች]

^ አን.11 ይህ ቀን በአሁኑ ጊዜ ያሉ አይሁዶች ፋሲካን ከሚያከብሩበት ቀን ጋር ተመሳሳይ ላይሆን ይችላል። ለምን? ምክንያቱም በዛሬው ጊዜ ያሉ አብዛኞቹ አይሁዶች በ⁠ዘፀአት 12:6 ላይ የሚገኘው ትእዛዝ የሚያመለክተው ኒሳን 15⁠ን እንደሆነ ስለሚሰማቸው ፋሲካን የሚያከብሩት በዚህ ዕለት ነው። (የየካቲት 15, 1990 መጠበቂያ ግንብ (እንግሊዝኛ) ገጽ 14⁠ን ተመልከት።) ኢየሱስ ግን ፋሲካን ያከበረው በሙሴ ሕግ ውስጥ በተገለጸው መሠረት ኒሳን 14 ላይ ነው። ይህን ቀን ማስላት የሚቻልበትን መንገድ በተመለከተ ተጨማሪ መረጃ ለማግኘት የሰኔ 15, 1977 መጠበቂያ ግንብ (እንግሊዝኛ) ከገጽ 383-384 ተመልከት።

^ አን.14 በይሖዋ ምሥክሮች የተዘጋጀውን ይህን መጽሐፍ ከገጽ 47-56, 206-208 ተመልከት። መጽሐፉን www.watchtower.org በተባለው ድረ ገጽ ውስጥ ማግኘት ትችላለህ።

^ አን.15 በይሖዋ ምሥክሮች የተዘጋጀ።

[በገጽ 22 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

እሁድ፣ ሚያዝያ 9, 2003 የኢየሱስን ሞት መታሰቢያ እንድታከብር ተጋብዘሃል

[በገጽ 23 እና 24 ላይ የሚገኝ ቻርት/​ሥዕል]

(መልክ ባለው መንገድ የተቀናበረውን ለማየት ጽሑፉን ተመልከት)

የመጨረሻው ሳምንት

2011 ማክሰኞ፣ ሚያዝያ 12

ሰንበት

ዮሐንስ 11:55 እስከ 12:1

gt 101 አን. 2-4 *

ኒሳን 9 (ፀሐይ ስትጠልቅ ይጀምራል)

በጥንት ዘመን አዲስ ቀን የሚጀምረው ምሽት ላይ ፀሐይ ከጠለቀች በኋላ ሲሆን የሚያበቃው ደግሞ በቀጣዩ ቀን ፀሐይ ስትጠልቅ ነው

የሥጋ ደዌ በያዘው በስምዖን ቤት ተጋበዘ

ማርያም የናርዶስ ሽቱ ቀባችው

አይሁዶች ኢየሱስንና አልዓዛርን ለማየት መጡ

ማቴዎስ 26:6-13

ማርቆስ 14:3-9

ዮሐንስ 12:2-11

gt 101, አን. 5-9

2011 ረቡዕ፣ ሚያዝያ 13

▪ እንደ ድል አድራጊ ሆኖ ወደ ኢየሩሳሌም ገባ

በቤተ መቅደስ አስተማረ

ማቴዎስ 21:1-11, 14-17

ማርቆስ 11:1-11

ሉቃስ 19:29-44

ዮሐንስ 12:12-19

gt 102

ኒሳን 10 (ፀሐይ ስትጠልቅ ይጀምራል)

በቢታንያ አደረ

2011 ሐሙስ፣ ሚያዝያ 14

▪ በጠዋት ወደ ኢየሩሳሌም ሄደ

▪ ቤተ መቅደሱን አጠራ

▪ ይሖዋ ከሰማይ ተናገረ

ማቴዎስ 21:12, 13, 18, 19

ማርቆስ 11:12-19

ሉቃስ 19:45-48

ዮሐንስ 12:20-50

gt 103, 104

ኒሳን 11 (ፀሐይ ስትጠልቅ ይጀምራል)

2011 ዓርብ፣ ሚያዝያ 15

▪ ምሳሌዎችን በመጠቀም በቤተ መቅደስ አስተማረ

▪ ፈሪሳውያንን አወገዘ

▪ መበለቲቷ መዋጮ ስታደርግ ተመለከተ

▪ ኢየሩሳሌም እንደምትወድቅ ትንቢት ተናገረ

▪ መገኘቱን ስለሚጠቁመው ምልክት ተናገረ

ማቴዎስ 21:19 እስከ 25:46

ማርቆስ 11:20 እስከ 13:37

ሉቃስ 20:1 እስከ 21:38

gt 105 እስከ 112 አን. 1

ኒሳን 12 (ፀሐይ ስትጠልቅ ይጀምራል)

2011 ቅዳሜ፣ ሚያዝያ 16

▪ ኢየሱስና ደቀ መዛሙርቱ በቢታኒያ ለብቻቸው ያሳለፉት ቀን

▪ ይሁዳ እሱን አሳልፎ ለመስጠት ተደራደረ

ማቴዎስ 26:1-5, 14-16

ማርቆስ 14:1, 2, 10, 11

ሉቃስ 22:1-6

gt 112, አን. 2-4

ኒሳን 13 (ፀሐይ ስትጠልቅ ይጀምራል)

2011 እሁድ፣ ሚያዝያ 17

▪ ጴጥሮስና ዮሐንስ ፋሲካን አዘጋጁ

▪ ኢየሱስና አሥሩ ሐዋርያት አመሻሹ ላይ ወደተዘጋጀው ቦታ ሄዱ

ማቴዎስ 26:17-19

ማርቆስ 14:12-16

ሉቃስ 22:7-13

gt 112 አን. 5 እስከ 113 አን. 1

ኒሳን 14 (ፀሐይ ስትጠልቅ ይጀምራል)

▪ ፋሲካን አከበረ

▪ የሐዋርያቱን እግር አጠበ

▪ ይሁዳን አሰናበተ

▪ የሞቱን መታሰቢያ አቋቋመ

ማቴዎስ 26:20-35

ማርቆስ 14:17-31

ሉቃስ 22:14-38

ዮሐንስ 13:1 እስከ 17:26

gt 113, አን. 2 እስከ 116 መጨረሻ

እኩለ ሌሊት

2011 ሰኞ፣ ሚያዝያ 18

▪ በጌቴሴማኒ የአትክልት ስፍራ አልፎ ተሰጠ

▪ ሐዋርያቱ ጥለውት ሸሹ

▪ በሳንሄድሪን ፊት ለፍርድ ቀረበ

▪ ጴጥሮስ ኢየሱስን ካደው

ማቴዎስ 26:36-75

ማርቆስ 14:32-72

ሉቃስ 22:39-62

ዮሐንስ 18:1-27

gt 117 እስከ 120 መጨረሻ

▪ በሳንሄድሪን ፊት በድጋሚ ቀረበ

▪ ወደ ጲላጦስ ተወሰደ፤ ቀጥሎ ወደ ሄሮድስ፤ ከዚያ ወደ ጲላጦስ

▪ ሞት ተፈረደበት፤ ከዚያም ተሰቀለ

▪ ከቀትር በኋላ ዘጠኝ ሰዓት ገደማ ላይ ሞተ

▪ አስከሬኑ ከተሰቀለበት ወርዶ ተቀበረ

ማቴዎስ 27:1-61

ማርቆስ 15:1-47

ሉቃስ 22:63 እስከ 23:56

ዮሐንስ 18:28-40

gt 121 እስከ 127 አን. 7

ኒሳን 15 (ፀሐይ ስትጠልቅ ይጀምራል)

ሰንበት

2011 ማክሰኞ፣ ሚያዝያ 19

▪ ጲላጦስ የኢየሱስ መቃብር እንዲጠበቅ ፈቃድ ሰጠ

ማቴዎስ 27:62-66

gt 127 አን. 8-9

ኒሳን 16 (ፀሐይ ስትጠልቅ ይጀምራል)

ማርቆስ 16:1

2011 ረቡዕ፣ ሚያዝያ 20

▪ ከሞት ተነሳ

▪ ለደቀ መዛሙርቱ ታየ

ማቴዎስ 28:1-15

ማርቆስ 16:1-8

ሉቃስ 24:1-49

ዮሐንስ 20:1-25

gt 127 አን. 10

እስከ 129 አን. 10

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.29 እዚህ ላይ የተጠቀሱት ቁጥሮች እስከ ዛሬ ከኖሩት ሁሉ የሚበልጠው ታላቅ ሰው (gt) የተባለውን መጽሐፍ ምዕራፎች የሚያመለክቱ ናቸው። ኢየሱስ በምድር ላይ ያከናወነውን የመጨረሻ አገልግሎት በተመለከተ ተጨማሪ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶችን ለማየት ከፈለግህ በይሖዋ ምሥክሮች ከተዘጋጀው የክርስቲያን ግሪክኛ ቅዱሳን መጻሕፍት አዲስ ዓለም ትርጉም ከተባለው መጽሐፍ ቅዱስ ላይ ከገጽ 429-431 ድረስ ያለውን ሠንጠረዥ ተመልከት።