በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትልቅ ቦታ ሊሰጠው የሚገባ ትንቢት

ትልቅ ቦታ ሊሰጠው የሚገባ ትንቢት

ትልቅ ቦታ ሊሰጠው የሚገባ ትንቢት

“ይህ የመንግሥቱ ምሥራች ለሕዝቦች ሁሉ ምሥክር እንዲሆን በመላው ምድር ይሰበካል፤ ከዚያም መጨረሻው ይመጣል።”—ማቴዎስ 24:14

ይህ ጥቅስ ትልቅ ቦታ ሊሰጠው እንደሚገባ ምሑራን ይስማማሉ። ለዚህም አንዱ ምክንያት ጥቅሱ ዓለም አቀፋዊ ይዘት ስላለው ሥራ የሚገልጽ መሆኑ ነው። ሌላው ምክንያት ደግሞ ክርስቲያኖች ሊያከናውኑት ስለሚገባው ሥራ ይኸውም ኢየሱስ “መጨረሻው” ብሎ የጠራው ታላቅ ክንውን ከመፈጸሙ በፊት እንደ ምልክት ሆኖ ስለሚያገለግለው የስብከት ሥራ የሚጠቅስ መሆኑ ነው።

ይህ ትንቢታዊ ጥቅስ በዘመናችን ፍጻሜውን እያገኘ ነው። ምሥራቹ ግብዣም ማስጠንቀቂያም የያዘ እንደመሆኑ መጠን ትንቢቱ አንተንም ይመለከታል። ይህ ምሥራች አንድ ምርጫ አቅርቦልሃል፦ የአምላክን መንግሥት መቀበል ወይም መቃወም። በመሆኑም የምታደርገው ምርጫ ሕይወትህን ይነካል።

እስቲ በጥቅሱ ዙሪያ ያለውን ሐሳብ እንመልከት። ኢየሱስ ተሰቅሎ ከመገደሉ ከበርካታ ቀናት በፊት ደቀ መዛሙርቱ ወደ እሱ ቀርበው ስለወደፊቱ ጊዜ ጥያቄ አቀረቡለት። ኢየሱስ በተደጋጋሚ ጊዜ ሲገልጸው የነበረው የአምላክ መንግሥት መቼ እንደሚቋቋም ለማወቅ ጓጉተው ነበር። በተጨማሪም ‘ስለዚህ ሥርዓት መደምደሚያ’ ወይም አንዳንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉሞች እንዳስቀመጡት ‘ስለ ዓለም መጨረሻ’ ማወቅ ፈልገው ነበር።—ማቴዎስ 24:3አ.መ.ት.

ኢየሱስ ለጥያቄያቸው መልስ ሲሰጥ በዓለም አቀፍ ደረጃ ጦርነት፣ ረሃብ፣ ቸነፈርና ታላላቅ የምድር ነውጦች እንደሚከሰቱ ትንቢት ተናገረ። በተጨማሪም ዓመፅ እየተስፋፋ እንደሚሄድ፣ የሐሰት ሃይማኖት አስተማሪዎች ብዙዎችን እንደሚያስቱ እንዲሁም እውነተኛ ክርስቲያኖች እንደሚጠሉና እንደሚሰደዱ ገለጸ። እነዚህ ሁሉ ነገሮች ምሥራች አይደሉም።—ማቴዎስ 24:4-13፤ ሉቃስ 21:11

ይሁን እንጂ ምሥራች የሆነ ነገርም አለ። ቀጥሎ ኢየሱስ በዚህ ርዕስ መግቢያ ላይ በተጠቀሰው ጥቅስ ላይ ያሉትን ትኩረት የሚስቡና ተስፋ የሚፈነጥቁ ቃላትን ተናገረ። ሰዎች ኢየሱስ በዚህ ጥቅስ ላይ የተናገረው ሐሳብ ትልቅ ቦታ ሊሰጠው እንደሚገባ ቢስማሙም ለጥቅሱ የሚሰጡት ትርጉም ግን አንድ ዓይነት አይደለም። ይህ ምሥራች በእርግጥ ምንድን ነው? መንግሥት የተባለው ምንድን ነው? ይህ ትንቢት የሚፈጸመው መቼ ነው? ወደ ፍጻሜ የሚያደርሱት እነማን ናቸው? መጨረሻ የተባለውስ ምንድን ነው? እስቲ የእነዚህን ጥያቄዎች መልስ አንድ በአንድ እንመልከት።

[በገጽ 2 እና 3 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

የጥንቶቹን አራት ወንጌሎች በማስመሰል የተዘጋጁ የዋሽንግተን ቅጂዎች። ጎላ የተደረገው ማቴዎስ 24:14 ነው

[የሥዕሉ ምንጭ]

From the book Facsimile of the Washington Manuscript of the Four Gospels in the Freer Collection 1912