በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

‘በመካከላችሁ በትጋት እየሠሩ ያሉትን አክብሯቸው’

‘በመካከላችሁ በትጋት እየሠሩ ያሉትን አክብሯቸው’

‘በመካከላችሁ በትጋት እየሠሩ ያሉትን አክብሯቸው’

“በመካከላችሁ በትጋት እየሠሩና በጌታ ሥራ አመራር እየሰጧችሁ ያሉትን እንዲሁም ምክር እየለገሷችሁ ያሉትን [አክብሯቸው]።”​—1 ተሰ. 5:12

1, 2. (ሀ) ጳውሎስ ለተሰሎንቄ ክርስቲያኖች የመጀመሪያውን መልእክት በጻፈበት ወቅት የጉባኤው ሁኔታ ምን ይመስል ነበር? (ለ) ጳውሎስ የተሰሎንቄ ክርስቲያኖችን ምን እንዲያደርጉ አሳስቧቸዋል?

በአውሮፓ⁠ መጀመሪያ ከተቋቋሙት ጉባኤዎች መካከል አንዱ የሆነው የተሰሎንቄ ጉባኤ አባል እንደሆንክ አድርገህ አስብ። ሐዋርያው ጳውሎስ፣ በመጀመሪያው መቶ ዘመን የነበረውን የዚህን ጉባኤ አባላት በመንፈሳዊ በመገንባት ብዙ ጊዜ አሳልፏል። በሌሎች ጉባኤዎች እንዳደረገው ሁሉ በተሰሎንቄም ጉባኤውን የሚመሩ ሽማግሌዎችን ሾሞ ሊሆን ይችላል። (ሥራ 14:23) ይሁንና ጉባኤው ከተቋቋመ ብዙም ሳይቆይ አይሁዳውያን፣ ጳውሎስንና ሲላስን ከከተማዋ ለማባረር ስለፈለጉ ሕዝቡን አሳድመው ረብሻ አስነሱ። በዚያ የቀሩት ክርስቲያኖች ብቻቸውን እንደተተዉ ተሰምቷቸው ምናልባትም በፍርሃት ተውጠው ሊሆን ይችላል።

2 ጳውሎስ፣ ተሰሎንቄን ለቅቆ ከሄደ በኋላ ገና ያልጠነከረው የዚህ ጉባኤ ሁኔታ አሳስቦት እንደሚሆን ግልጽ ነው። ሐዋርያው ወደ ተሰሎንቄ ለመመለስ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ‘ሰይጣን መንገዱን እንደዘጋበት’ ተናግሯል። በመሆኑም ጉባኤውን ለማበረታታት ጢሞቴዎስን ላከው። (1 ተሰ. 2:18፤ 3:2) ጢሞቴዎስ ጥሩ ዜና ይዞለት ስለተመለሰ ጳውሎስ ለተሰሎንቄ ክርስቲያኖች ደብዳቤ ለመጻፍ ተነሳሳ። ጳውሎስ ከጻፋቸው ነገሮች መካከል “አመራር እየሰጧችሁ ያሉትን . . . እንድታከብሯቸው እንለምናችኋለን” የሚለው ሐሳብ ይገኝበታል።​—1 ተሰሎንቄ 5:12, 13ን አንብብ።

3. የተሰሎንቄ ክርስቲያኖች ለሽማግሌዎች የላቀ አክብሮት እንዲሰጡ የሚያነሳሷቸው ምን ምክንያቶች ነበሯቸው?

3 በተሰሎንቄ ጉባኤ ውስጥ አመራር የሚሰጡት ወንድሞች እንደ ጳውሎስና የጉዞ ጓደኞቹ ተሞክሮ ያካበቱ አልነበሩም፤ እንዲሁም በኢየሩሳሌም የነበሩትን ሽማግሌዎች ያህል በእውነት ውስጥ ረጅም ጊዜ አልቆዩም። ጉባኤው ከተቋቋመ ገና ዓመት እንኳ አልሞላውም ነበር! ያም ቢሆን የጉባኤው አባላት፣ በመካከላቸው ‘በትጋት ለሚሠሩት’ እና ለጉባኤው ‘አመራር ለሚሰጡት’ እንዲሁም ለወንድሞች ‘ምክር ለሚለግሱት’ ሽማግሌዎች አመስጋኝ እንዲሆኑ የሚገፋፋቸው ምክንያት ነበራቸው። በእርግጥም ለእነዚህ ሽማግሌዎች “በፍቅር የላቀ አክብሮት [እንዲያሳዩ]” የሚያነሳሳቸው በቂ ምክንያት ነበራቸው። ጳውሎስ ለተሰሎንቄ ክርስቲያኖች ይህን ካለ በኋላ “እርስ በርስ ባላችሁ ግንኙነት ሰላማውያን ሁኑ” የሚል ምክር ሰጥቷቸዋል። አንተ የተሰሎንቄ ጉባኤ አባል ብትሆን ኖሮ ሽማግሌዎቹ ለሚያከናውኑት ሥራ ጥልቅ አድናቆት እንዳለህ ታሳይ ነበር? አምላክ በክርስቶስ በኩል ለጉባኤህ ‘እንደ ስጦታ አድርጎ የሰጣቸውን ወንዶች’ እንዴት ትመለከታቸዋለህ?​—ኤፌ. 4:8

‘በትጋት የሚሠሩ’

4, 5. በጳውሎስ ዘመን የነበሩት ሽማግሌዎች ጉባኤውን ለማስተማር በትጋት መሥራት ያስፈለጋቸው ለምን ነበር? ዛሬስ ሁኔታው ተመሳሳይ የሆነው እንዴት ነው?

4 በተሰሎንቄ የነበሩት ሽማግሌዎች፣ ጳውሎስንና ሲላስን ወደ ቤርያ ከላኳቸው በኋላ “በትጋት እየሠሩ” የነበሩት እንዴት ነው? የጳውሎስን ምሳሌ በመከተል በቅዱሳን መጻሕፍት እየተጠቀሙ ጉባኤውን ያስተምሩ እንደነበር ምንም ጥርጥር የለውም። ‘የተሰሎንቄ ክርስቲያኖች የአምላክን ቃል በአድናቆት ተቀብለውት ይሆን?’ ብለህ ታስብ ይሆናል። ደግሞም መጽሐፍ ቅዱስ ራሱ እንዲህ ይላል፦ “በቤርያ የነበሩት አይሁዳውያን በተሰሎንቄ ከነበሩት ይልቅ ልበ ቀና ነበሩ፤ . . . በየዕለቱ ቅዱሳን መጻሕፍትን በሚገባ [ይመረምሩ]” ነበር። (ሥራ 17:11) ይሁንና ጳውሎስ ያወዳደረው በቤርያ የነበሩትን እውነትን የተቀበሉ አይሁዳውያን በተሰሎንቄ ከነበሩት እውነትን ያልተቀበሉ በርካታ አይሁዳውያን ጋር እንጂ ከተሰሎንቄ ክርስቲያኖች ጋር እንዳልሆነ ልብ በል። እውነትን የተቀበሉት በተሰሎንቄ የነበሩት አይሁዳውያን ‘የአምላክን ቃል እንደ ሰው ቃል ሳይሆን እንደ አምላክ ቃል አድርገው ተቀብለውታል።’ (1 ተሰ. 2:13) ሽማግሌዎቹ ጉባኤውን በመንፈሳዊ ለመመገብ በትጋት ሠርተው መሆን አለበት።

5 በአሁኑ ወቅት ታማኝና ልባም ባሪያ ለአምላክ መንጋ “በተገቢው ጊዜ ምግባቸውን” እየሰጣቸው ነው። (ማቴ. 24:45) በየጉባኤው ያሉት ሽማግሌዎች በባሪያው እየተመሩ ወንድሞቻቸውን በመንፈሳዊ ለመመገብ በትጋት ይሠራሉ። የጉባኤው አባላት በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሠረቱ በርካታ ጽሑፎች ይኖሯቸዋል፤ በአንዳንድ ቋንቋዎች ደግሞ የመጠበቂያ ግንብ ማኅበር ጽሑፎች ማውጫ (እንግሊዝኛ)፣ በሲዲ የተዘጋጀው ዎችታወር ላይብረሪ (እንግሊዝኛ) እና እንደነዚህ የመሳሰሉ መሣሪያዎች ተዘጋጅተዋል። ሽማግሌዎች በስብሰባ ላይ እንዲያቀርቡ የተሰጣቸውን ክፍል ጠቃሚ በሆነ መልኩ ለማቅረብ ሲሉ ክፍሎቻቸውን በመዘጋጀት በርካታ ሰዓታት ያሳልፋሉ፤ በዚህ መንገድ የጉባኤውን መንፈሳዊ ፍላጎት ለማሟላት ይጥራሉ። ሽማግሌዎች በጉባኤና በትላልቅ ስብሰባዎች ላይ የሚያቀርቧቸውን ክፍሎች ለመዘጋጀት ምን ያህል ጊዜ እንደሚያሳልፉ አስበህ ታውቃለህ?

6, 7. (ሀ) በተሰሎንቄ የነበሩት ሽማግሌዎች ከጳውሎስ ምን መማር ይችሉ ነበር? (ለ) በዛሬው ጊዜ ያሉ ሽማግሌዎች የጳውሎስን ምሳሌ መከተል ፈታኝ ሊሆንባቸው የሚችለው ለምንድን ነው?

6 በተሰሎንቄ ጉባኤ የነበሩት ሽማግሌዎች፣ ጳውሎስ መንጋውን እንደ እረኛ ሆኖ በመንከባከብ ረገድ የተወውን ግሩም ምሳሌ አልዘነጉም። ጳውሎስ የእረኝነት ሥራውን ያከናውን የነበረው በፍቅርና በአሳቢነት እንጂ ግድ ስለሆነበት አልነበረም። ከዚህ በፊት ባለው ርዕስ ላይ እንደተብራራው ጳውሎስ “የምታጠባ እናት ልጆቿን እንደምትንከባከብ . . . በገርነት [ተንከባክቧቸዋል]።” (1 ተሰሎንቄ 2:7, 8ን አንብብ።) ሌላው ቀርቶ ‘የገዛ ነፍሱን እንኳ ለእነሱ ለማካፈል’ ፈቃደኛ ነበር! ሽማግሌዎቹም እረኝነት ሲያደርጉ ጳውሎስን ሊመስሉት ይገባ ነበር።

7 በዛሬው ጊዜ ያሉ ክርስቲያን እረኞችም መንጋውን በመንከባከብ ረገድ ጳውሎስን ይመስላሉ። አንዳንድ በጎች በተፈጥሯቸው በቀላሉ የማይቀረቡ ሊሆኑ ይችላሉ። ያም ቢሆን ሽማግሌዎች ነገሮችን ጠለቅ ብለው ለማስተዋል መሞከርና የበጎቹን “መልካም ነገር” ለማግኘት መጣር አለባቸው። (ምሳሌ 16:20 የ1954 ትርጉም) እውነት ነው፣ ሽማግሌዎች ፍጹማን ባለመሆናቸው ለእያንዳንዱ ሰው ቀና አመለካከት ለመያዝ መታገል ያስፈልጋቸው ይሆናል። ይሁንና በተቻለ መጠን ለሰው ሁሉ ገር እንዲሁም በክርስቶስ የሚመሩ ጥሩ እረኞች ለመሆን ጥረት ስለሚያደርጉ ሊመሰገኑ አይገባም?

8, 9. በዛሬው ጊዜ ያሉ ሽማግሌዎች ‘ነፍሳችንን ተግተው ከሚጠብቁባቸው’ መንገዶች አንዳንዶቹ የትኞቹ ናቸው?

8 ሁላችንም ለሽማግሌዎች ‘ለመገዛት’ የሚያነሳሳን ምክንያት አለን። ጳውሎስ እንደጻፈው ሽማግሌዎች ‘ነፍሳችንን ተግተው ይጠብቃሉ።’ (ዕብ. 13:17) ይህ አገላለጽ መንጋውን ለመጠበቅ ሲል እንቅልፍ አጥቶ የሚያድረውን የበጎች እረኛ ያስታውሰናል። በተመሳሳይም በዛሬው ጊዜ የሚገኙ ሽማግሌዎች የጤና እክል ያለባቸውን ወይም ስሜታቸው የተጎዳ አሊያም መንፈሳዊ ችግር ያጋጠማቸውን በጎች ለመርዳት ሲሉ እንቅልፋቸውን መሥዋዕት ማድረግ ያስፈልጋቸው ይሆናል። ለምሳሌ ያህል፣ በሆስፒታል አገናኝ ኮሚቴዎች ውስጥ የሚሠሩ ወንድሞች ከሕክምና ጋር ለተያያዙ ችግሮች መፍትሔ ለማፈላለግ ሲባል ከሞቀ እንቅልፋቸው መነሳት አስፈልጓቸዋል። ያም ቢሆን እንደነዚህ ዓይነት ሁኔታዎች አጋጥመውን ሽማግሌዎች ሲረዱን ያደረጉልንን ነገር በጣም እንደምናደንቅ ጥርጥር የለውም!

9 ከመንግሥት አዳራሽ ግንባታ እና ከእርዳታ ኮሚቴዎች ጋር የተያያዘ ሥራ የሚያከናውኑ ሽማግሌዎችም ወንድሞቻቸውን ለመርዳት ተግተው ይሠራሉ። እነዚህን ወንድሞች በሙሉ ልባችን ልንደግፋቸው ይገባል! ምያንማር በ2008 ናርጊስ በተባለች አውሎ ነፋስ ከተመታች በኋላ የተከናወነውን የእርዳታ ሥራ እንመልከት። የእርዳታ ኮሚቴው፣ ከፍተኛ ጉዳት በደረሰበት ኢራዋዲ በተባለው አካባቢ ወደሚገኘው የቦቲንጎን ጉባኤ ለመድረስ በአደጋው ክፉኛ የተጎዱ አካባቢዎችን እያቋረጠ በአስከሬኖች መካከል አልፎ መሄድ ነበረበት። የቦቲንጎን ጉባኤ ወንድሞች፣ ወደ አካባቢው በደረሰው የመጀመሪያው የእርዳታ ቡድን ውስጥ የቀድሞ የወረዳ የበላይ ተመልካቻቸውን ሲመለከቱ “አያችሁ! የወረዳ የበላይ ተመልካቻችን እኮ ነው! ይሖዋ ደረሰልን!” በማለት በደስታ ተናገሩ። አንተስ ሽማግሌዎች ቀን ከሌት በትጋት የሚያከናውኑትን ሥራ ታደንቃለህ? አንዳንድ ሽማግሌዎች አስቸጋሪ የሆኑ የፍርድ ጉዳዮችን በሚመለከቱ ልዩ ኮሚቴዎች ውስጥ እንዲሠሩ ይመደባሉ። እነዚህ ሽማግሌዎች ስላከናወኑት ነገር በጉራ አይናገሩም፤ ሆኖም እነሱ ከሚያከናውኑት አገልግሎት ተጠቃሚ የሆኑት ወንድሞች ለሥራቸው በጣም አመስጋኝ ናቸው።​—ማቴ. 6:2-4

10. ሽማግሌዎች፣ ሌሎች እምብዛም የማያውቋቸውን የትኞቹን ሥራዎች ያከናውናሉ?

10 በዛሬው ጊዜ ያሉ በርካታ ሽማግሌዎች ሌሎች ሥራዎችንም ያከናውናሉ። ለምሳሌ ያህል፣ የሽማግሌዎች አካል አስተባባሪ የሳምንታዊ ስብሰባ ፕሮግራሞችን ያወጣል። የጉባኤው ጸሐፊ ወርሃዊና ዓመታዊ የመስክ አገልግሎት ሪፖርቶችን ያጠናቅራል። የትምህርት ቤቱ የበላይ ተመልካች ደግሞ የትምህርት ቤቱን ፕሮግራም በጥንቃቄ አስቦበት ያዘጋጃል። በየሦስት ወሩ የጉባኤው ሒሳብ ይመረመራል። ሽማግሌዎች ከቅርንጫፍ ቢሮ የተላኩ ደብዳቤዎችን በማንበብ የተሰጣቸውን መመሪያ በተግባር ያውላሉ፤ ይህም ‘በእምነት የሚገኘውን አንድነት’ ለመጠበቅ ይረዳል። (ኤፌ. 4:3, 13) እንደነዚህ ያሉት በትጋት የሚሠሩ ሽማግሌዎች የሚያደርጉት ጥረት “ሁሉም ነገር በአግባብና በሥርዓት” እንዲከናወን ያስችላል።​—1 ቆሮ. 14:40

‘አመራር የሚሰጡ’

11, 12. በጉባኤ ውስጥ አመራር የሚሰጡት እነማን ናቸው? ይህስ ምንን ይጨምራል?

11 ጳውሎስ በተሰሎንቄ የነበሩት በትጋት የሚሠሩ ሽማግሌዎች ለጉባኤው ‘አመራር የሚሰጡ’ እንደሆኑ ገልጿል። ‘አመራር የሚሰጡ’ ተብሎ የተተረጎመው የግሪክኛው ቃል “በፊታችሁ የሚቆሙ” ተብሎም ሊገለጽ ይችላል። (1 ተሰ. 5:12) ጳውሎስ እነዚሁ ሽማግሌዎች ‘በትጋት የሚሠሩ’ እንደሆኑ ገልጿል። ሐዋርያው ይህን ሲል በጉባኤ ውስጥ ስላሉት ስለ ሁሉም ሽማግሌዎች መናገሩ ነበር። በዛሬው ጊዜ አብዛኞቹ ሽማግሌዎች በጉባኤው ፊት ቆመው ስብሰባዎችን ይመራሉ። “የሽማግሌዎች አካል አስተባባሪ” የሚለውን መጠሪያ እንድንጠቀም በቅርቡ የተደረገው ማስተካከያ ሁሉንም ሽማግሌዎች የአንድ አካል ክፍሎች እንደሆኑ አድርገን እንድንመለከታቸው ይረዳናል።

12 በጉባኤ ውስጥ ‘አመራር መስጠት’ ከማስተማር የበለጠ ነገርን ይጨምራል። በ1 ጢሞቴዎስ 3:4 ላይ “የሚያስተዳድር” ተብሎ የተተረጎመው ቃልም ‘አመራር መስጠት’ ከሚለው አገላለጽ ጋር ተመሳሳይ ትርጉም አለው። ጳውሎስ፣ የበላይ ተመልካች “ልጆቹን ታዛዥና የታረመ ጠባይ ያላቸው አድርጎ በማሳደግ የራሱን ቤተሰብ በተገቢው ሁኔታ የሚያስተዳድር ሊሆን ይገባዋል” በማለት ተናግሯል። እዚህ ላይ የገባው “የሚያስተዳድር” የሚለው ቃል ልጆቹን ማስተማርን ብቻ ሳይሆን በቤተሰቡ ውስጥ አመራር መስጠትንና “ልጆቹን ታዛዥ” አድርጎ ማሳደግን እንደሚጨምር ግልጽ ነው። አዎን፣ ሽማግሌዎች ግንባር ቀደም ሆነው ጉባኤውን በመምራት ሁሉም የጉባኤው አባላት ለይሖዋ ታዛዥ እንዲሆኑ ይረዷቸዋል።​—1 ጢሞ. 3:5

13. ሽማግሌዎች ስብሰባ በሚያደርጉበት ወቅት አንድ ውሳኔ ላይ ለመድረስ ጊዜ ሊወስድ የሚችለው ለምንድን ነው?

13 ሽማግሌዎች ጉባኤው የሚያስፈልገውን ነገር እንዴት እንደሚያሟሉ በመወያየት ለመንጋው ጥሩ አመራር ለመስጠት ይጥራሉ። አንድ ሽማግሌ ሁሉንም ውሳኔዎች ቢያደርግ ጊዜና ጉልበት ይቆጥብ ይሆናል። ይሁንና በዘመናችን ያሉ የሽማግሌዎች አካላት በመጀመሪያው መቶ ዘመን የነበረውን የበላይ አካል ምሳሌ ይከተላሉ፤ በአንድ ጉዳይ ላይ ሲወያዩ ሁሉም ሐሳባቸውን በነፃነት የሚገልጹ ሲሆን ከቅዱሳን መጻሕፍት መመሪያ ለማግኘት ጥረት ያደርጋሉ። ዓላማቸው ጉባኤው ከሚያስፈልጉት ነገሮች ጋር በተያያዘ መጽሐፍ ቅዱሳዊ መመሪያዎችን ተግባራዊ ማድረግ የሚችሉበትን መንገድ መፈለግ ነው። እዚህ ግብ ላይ መድረስ የሚቻለው እያንዳንዱ የበላይ ተመልካች፣ ሽማግሌዎች በሚያደርጉት ስብሰባ ላይ በሚገኝበት ጊዜ ቅዱሳን መጻሕፍትን እንዲሁም ታማኝና ልባም ባሪያ ያወጣቸውን መመሪያዎች ከግምት በማስገባት በሚገባ የሚዘጋጅ ከሆነ ነው። እርግጥ እንዲህ ማድረግ ጊዜ ይወስዳል። በመጀመሪያው መቶ ዘመን የነበረው የበላይ አካል የግርዘት ጉዳይን አስመልክቶ ውይይት ባደረገበት ወቅት እንደተፈጠረው ዓይነት የሐሳብ ልዩነት በሚኖርበት ጊዜ በቅዱሳን መጻሕፍት ላይ ተመሥርቶ ሁሉም የሚስማማበት ውሳኔ ላይ ለመድረስ ተጨማሪ ጊዜ መስጠትና ምርምር ማድረግ ሊያስፈልግ ይችላል።​—ሥራ 15:2, 6, 7, 12-14, 28

14. የሽማግሌዎች አካል አባላት እንደ አንድ አካል ተባብረው መሥራታቸውን ታደንቃለህ? እንዲህ የሚሰማህ ለምንድን ነው?

14 አንድ ሽማግሌ፣ እኔ ያልኩት ካልሆነ ብሎ ድርቅ የሚል አሊያም የራሱን አመለካከት በሌሎች ላይ ለመጫን የሚሞክር ከሆነ ምን ሊፈጠር ይችላል? ወይም ደግሞ አንድ ሰው በመጀመሪያው መቶ ዘመን እንደነበረው እንደ ዲዮጥራጢስ መከፋፈል የሚፈጥር ቢሆንስ? (3 ዮሐ. 9, 10) ይህ መላውን ጉባኤ እንደሚጎዳ ጥርጥር የለውም። ሰይጣን በአንደኛው መቶ ዘመን የነበረውን ጉባኤ ለመበጥበጥ ከሞከረ በዛሬው ጊዜ ያለውን ጉባኤ ሰላምም ለማደፍረስ እንደሚፈልግ እርግጠኞች መሆን እንችላለን። ዲያብሎስ፣ ትልቅ ቦታ ለማግኘት እንደ መፈለግ ባሉት በሰዎች ላይ የሚታዩ የራስ ወዳድነት ዝንባሌዎች ሊጠቀም ይችላል። ስለዚህ ሽማግሌዎች ትሕትናን ማዳበርና እንደ አንድ አካል ተባብረው መሥራት ይኖርባቸዋል። በእርግጥም እንደ አንድ አካል ተባብረው የሚሠሩ ሽማግሌዎች የሚያሳዩትን ትሕትና በጣም እናደንቃለን!

‘ምክር የሚለግሱ’

15. ሽማግሌዎች አንድን ወንድም ወይም እህት ለመምከር የሚያነሳሳቸው ምንድን ነው?

15 ጳውሎስ ቀጥሎ ትኩረት ያደረገው ሽማግሌዎች በሚያከናውኑት ከባድ ሆኖም በጣም አስፈላጊ ሥራ ላይ ሲሆን ይህም ለመንጋው ምክር መለገስ ነው። በክርስቲያን ግሪክኛ ቅዱሳን መጻሕፍት ውስጥ ‘ምክር መለገስ’ ተብሎ የተተረጎመውን የግሪክኛ ቃል የተጠቀመው ጳውሎስ ብቻ ነው። ቃሉ ጠንከር ያለ ምክር መስጠትን ቢያመለክትም ጥላቻን አይገልጽም። (ሥራ 20:31፤ 2 ተሰ. 3:15) ለምሳሌ ያህል፣ ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ክርስቲያኖች “እነዚህን ነገሮች የምጽፍላችሁ ላሳፍራችሁ ብዬ ሳይሆን እንደተወደዳችሁ ልጆቼ አድርጌ ልመክራችሁ ነው” ብሏቸዋል። (1 ቆሮ. 4:14) ምክር እንዲሰጥ ያነሳሳው ለሌሎች ያለው ፍቅራዊ አሳቢነት ነበር።

16. ሽማግሌዎች ለሌሎች ምክር ሲሰጡ ለየትኛው ነገር ትኩረት መስጠታቸው ተገቢ ነው?

16 ሽማግሌዎች፣ ለሌሎች ምክር የሚሰጡበት መንገድ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ ይገነዘባሉ። ደግ፣ አፍቃሪና ሌሎችን ለመርዳት ዝግጁ በመሆን የጳውሎስን ምሳሌ ለመከተል ይጥራሉ። (1 ተሰሎንቄ 2:11, 12ን አንብብ።) እርግጥ ነው፣ ሽማግሌዎች ‘ጤናማ በሆነው ትምህርት አጥብቀው መምከር እንዲችሉ የታመነውን ቃል አጥብቀው የሚይዙ ሊሆኑ ይገባል።’​—ቲቶ 1:5-9

17, 18. አንድ ሽማግሌ ምክር ቢሰጥህ ምን ነገር ማስታወስ ይኖርብሃል?

17 እርግጥ ነው፣ ሽማግሌዎች ፍጹማን ባለመሆናቸው በኋላ ላይ የሚቆጩበት ነገር ሊናገሩ ይችላሉ። (1 ነገ. 8:46፤ ያዕ. 3:8) በተጨማሪም ምክር መቀበል በራሱ ለወንድሞችና ለእህቶች “የሚያሳዝን እንጂ የሚያስደስት” ነገር እንዳልሆነ ሽማግሌዎች ይገነዘባሉ። (ዕብ. 12:11) በመሆኑም አንድ ሽማግሌ ለአንድ ሰው ምክር ለመስጠት የሚነሳው በጉዳዩ ላይ በደንብ ካሰበበትና ከጸለየበት በኋላ ነው። አንድ ሽማግሌ ምክር ቢሰጥህ ይህ ወንድም ያሳየህን ፍቅራዊ አሳቢነት ታደንቃለህ?

18 የሕክምና ባለሙያዎች ሊያውቁት ያልቻሉ አንድ የጤና እክል አለብህ እንበል። ይሁንና አንድ ሐኪም ችግርህ ምን እንደሆነ በትክክል ማወቅ ቻለ፤ የምርመራው ውጤት ግን ለመቀበል የሚከብድ ነው። ታዲያ በዚህ ጊዜ በሐኪሙ ላይ ቅሬታ ያድርብሃል? በፍጹም! ከዚህ ይልቅ ሐኪሙ ቀዶ ሕክምና እንድታደርግ ቢነግርህ እንኳ ለራስህ ጥቅም እንደሆነ በመገንዘብ ሕክምናውን ለመቀበል እንደምትስማማ ጥርጥር የለውም። ሐኪሙ የምርመራውን ውጤት የተናገረበት መንገድ ስሜትህን ጎድቶት ይሆናል፤ ሆኖም ይህ በምታደርገው ውሳኔ ላይ ተጽዕኖ እንዲያሳድር ትፈቅዳለህ? እንዲህ እንደማታደርግ የታወቀ ነው። በተመሳሳይም ሽማግሌዎች ለአንተ ምክር የሚሰጡበትን መንገድ ስላልወደድከው ብቻ ምክሩን ከመስማት ወደኋላ አትበል፤ ይሖዋና ኢየሱስ መንፈሳዊ እድገት ማድረግና ራስህን ከመንፈሳዊ አደጋ መጠበቅ እንድትችል አንተን ለመርዳት የሚጠቀሙት በሽማግሌዎች እንደሆነ አትዘንጋ።

ይሖዋ ላደረገው ዝግጅት አድናቆት ይኑርህ

19, 20. ‘ስጦታ ለሆኑ ወንዶች’ ያለህን አድናቆት እንዴት ማሳየት ትችላለህ?

19 ለአንተ ተብሎ የተዘጋጀ ስጦታ ቢሰጥህ ምን ታደርጋለህ? በዚህ ስጦታ በመጠቀም ለተደረገልህ ነገር አድናቆት እንዳለህ አታሳይም? ይሖዋ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ‘ስጦታ የሆኑ ወንዶችን’ በመስጠት አንተን የሚጠቅም ዝግጅት አድርጓል። ለእነዚህ ስጦታዎች አድናቆት እንዳለህ ማሳየት ከምትችልባቸው መንገዶች አንዱ ሽማግሌዎች የሚሰጧቸውን ንግግሮች በጥሞና ማዳመጥና የጠቀሷቸውን ነጥቦች ሥራ ላይ ለማዋል ጥረት ማድረግ ነው። በተጨማሪም በስብሰባዎች ላይ ትርጉም ያለው ተሳትፎ በማድረግ አድናቆትህን ማሳየት ትችላለህ። እንዲሁም ሽማግሌዎች ግንባር ቀደም ሆነው በሚያከናውኗቸው እንደ መስክ አገልግሎት ባሉ እንቅስቃሴዎች መካፈል ትችላለህ። አንድ ሽማግሌ ከሰጠህ ምክር ጥቅም አግኝተህ ከሆነ ይህንን ለሽማግሌው ለምን አትነግረውም? ለሽማግሌው ቤተሰቦችስ አድናቆትህን ለምን አትገልጽላቸውም? አንድ ሽማግሌ የጉባኤ ሥራዎችን በትጋት ማከናወን የቻለው ቤተሰቦቹ ከእሱ ጋር የሚያሳልፉትን ጊዜ መሥዋዕት ስላደረጉ እንደሆነ አስታውስ።

20 አዎን በመካከላችን በትጋት ለሚሠሩት፣ አመራር ለሚሰጡንና ምክር ለሚለግሱን ሽማግሌዎች አድናቆታችንን ለመግለጽ የሚያነሳሳን በቂ ምክንያት አለን። በእርግጥም እነዚህ ‘ስጦታ የሆኑ ወንዶች’ ይሖዋ በፍቅር ተነሳስቶ የሰጠን ስጦታዎች ናቸው!

ታስታውሳለህ?

• በተሰሎንቄ የነበሩ ክርስቲያኖች በመካከላቸው አመራር የሚሰጡትን እንዲያደንቁ የሚያነሳሷቸው ምን ምክንያቶች ነበሯቸው?

• በጉባኤህ ውስጥ የሚገኙ ሽማግሌዎች በትጋት የሚሠሩት እንዴት ነው?

• ሽማግሌዎች ከሚሰጡት አመራር የምትጠቀመው እንዴት ነው?

• አንድ ሽማግሌ ምክር ቢሰጥህ ምን ነገር ማስታወስ ይኖርብሃል?

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 27 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ሽማግሌዎች ጉባኤውን በእረኝነት የሚያገለግሉባቸውን የተለያዩ መንገዶች ታደንቃለህ?