በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ወደ አምላክ መቅረብ የምትችለው እንዴት ነው?

ወደ አምላክ መቅረብ የምትችለው እንዴት ነው?

ከአምላክ ቃል ተማር

ወደ አምላክ መቅረብ የምትችለው እንዴት ነው?

ይህ ርዕሰ ትምህርት በአእምሮህ ሊመላለሱ የሚችሉ ጥያቄዎችን የሚያነሳ ሲሆን መልሶቹን ከመጽሐፍ ቅዱስህ ውስጥ የት ቦታ ላይ ማግኘት እንደምትችልም ይጠቁምሃል። የይሖዋ ምሥክሮች ለጥያቄዎቹ በተሰጡት መልሶች ላይ ከአንተ ጋር ቢወያዩ ደስ ይላቸዋል።

1. አምላክ የሚሰማው ሁሉንም ጸሎቶች ነው?

ይሖዋ ሰዎች ሁሉ በጸሎት አማካኝነት ወደ እሱ እንዲቀርቡ ይጋብዛል። (መዝሙር 65:2) ይሁንና የሚሰማው ሁሉንም ጸሎቶች አይደለም። ለምሳሌ ያህል፣ እስራኤላውያን መጥፎ አካሄዳቸውን ለመተው አሻፈረኝ በማለታቸው አምላክ የሚያቀርቡትን ጸሎት ለመስማት ፈቃደኛ ሳይሆን ቀርቷል። (ኢሳይያስ 1:15) በተጨማሪም በሚስቱ ላይ በደል የሚፈጽም ባል ወደ አምላክ የሚያቀርበው ጸሎት ሊታገድበት ይችላል። (1 ጴጥሮስ 3:7) ያም ሆኖ አምላክ፣ ሰዎች ከባድ ኃጢአት ቢሠሩም እንኳ ንስሐ እስከገቡ ድረስ ጸሎታቸውን ይሰማል።​—2 ዜና መዋዕል 33:9-13ን አንብብ።

2. መጸለይ ያለብን እንዴት ነው?

ጸሎት መብት ከመሆኑም ሌላ የአምልኳችን ክፍል ነው፤ ስለሆነም መጸለይ ያለብን ወደ ይሖዋ ብቻ ነው። (ማቴዎስ 4:10፤ 6:9) ፍጹማን ባለመሆናችን የተነሳ መጸለይ ያለብን በኢየሱስ ስም ብቻ ነው፤ ወደ አምላክ መቅረብ የሚቻልበት “መንገድ” እሱ ነው። (ዮሐንስ 14:6) ይሖዋ ከልብ በመነጨ ስሜት እንድንጸልይ እንጂ አንድን ሐሳብ በመሸምደድ ወይም በማንበብ ሁልጊዜ ተመሳሳይ ጸሎት እንድናቀርብ አይፈልግም።​—ማቴዎስ 6:7ን እና ፊልጵስዩስ 4:6, 7ን አንብብ።

ፈጣሪያችን በልባችን እንኳ የምናቀርበውን ጸሎት ይሰማል። (1 ሳሙኤል 1:12, 13) አምላክ ዘወትር ወደ እሱ እንድንጸልይ ለምሳሌ ጠዋትና ማታ፣ በምግብ ሰዓት እንዲሁም ችግሮች ሲያጋጥሙን ወደ እሱ እንድንቀርብ ይጋብዘናል።​—መዝሙር 55:22ን እና ማቴዎስ 15:36ን አንብብ።

3. ክርስቲያኖች አንድ ላይ የሚሰበሰቡት ለምንድን ነው?

የምንኖረው በአምላክ ላይ እምነት በሌላቸው እንዲሁም እሱ በምድር ላይ ሰላም እንደሚያሰፍን በገባው ቃል ላይ በሚያፌዙ ሰዎች መካከል ስለሆነ ወደ አምላክ መቅረብ ቀላል አይደለም። (2 ጢሞቴዎስ 3:1, 4፤ 2 ጴጥሮስ 3:3, 13) በመሆኑም ከእምነት ባልንጀሮቻችን ጋር አንድ ላይ በመሰብሰብ እርስ በርስ መበረታታት ያስፈልገናል።​—ዕብራውያን 10:24, 25ን አንብብ።

አንተም አምላክን ከሚወዱ ሰዎች ጋር ከተወዳጀህ ወደ አምላክ መቅረብ ትችላለህ። የይሖዋ ምሥክሮች በሚያደርጓቸው ስብሰባዎች ላይ ከተገኘህ የሌሎችን እምነት በማየት ብርታት ታገኛለህ።​—ሮም 1:11, 12ን አንብብ።

4. ወደ አምላክ መቅረብ የምትችለው እንዴት ነው?

ከመጽሐፍ ቅዱስ በተማርካቸው ነገሮች ላይ በማሰላሰል ወደ ይሖዋ መቅረብ ትችላለህ። ይሖዋ ባደረጋቸው ነገሮች፣ በሰጣቸው መመሪያዎችና በገባቸው ተስፋዎች ላይ አሰላስል። ጸሎት የታከለበት ማሰላሰል ለአምላክ ፍቅርና ጥበብ ከልብ የመነጨ አድናቆት እንዲኖረን ያደርጋል።​—ኢያሱ 1:8ን እና መዝሙር 1:1-3ን አንብብ።

ወደ አምላክ መቅረብ የምትችለው በእሱ ላይ እምነት የምታሳድር ከሆነ ብቻ ነው። ይሁንና እምነት እንክብካቤ ሊደረግለት እንደሚገባ ሕይወት ያለው ነገር ነው። ለምታምንባቸው ነገሮች መሠረት የሆኑትን ሐሳቦች በመመርመር እምነትህን በምሳሌያዊ ሁኔታ ያለማቋረጥ መመገብ ይኖርብሃል።​—1 ተሰሎንቄ 5:21ን እና ዕብራውያን 11:1, 6ን አንብብ።

5. ወደ አምላክ መቅረብህ የሚጠቅምህ እንዴት ነው?

ይሖዋ ለሚወዱት ሰዎች ያስብላቸዋል። እምነታቸውንና የዘላለም ሕይወት ተስፋቸውን አደጋ ላይ ሊጥል ከሚችል ከማንኛውም ነገር ይጠብቃቸዋል። (መዝሙር 91:1, 2, 7-10) ጤንነታችንን እና ደስታችንን ሊያሳጣ ከሚችል የአኗኗር ዘይቤ እንድንርቅ ያስጠነቅቀናል። እንዲሁም ይሖዋ ሕይወታችንን ከሁሉ በተሻለ መንገድ መምራት እንድንችል ያስተምረናል።​—መዝሙር 73:27, 28 እና ያዕቆብ 4:4, 8ን አንብብ።

ተጨማሪ ማብራሪያ ለማግኘት በይሖዋ ምሥክሮች የተዘጋጀውን ትክክለኛው የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ምንድን ነው? የተባለውን መጽሐፍ ምዕራፍ 17 ተመልከት።