በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ይህን ያውቁ ኖሯል?

ይህን ያውቁ ኖሯል?

ይህን ያውቁ ኖሯል?

ኢየሩሳሌም በነበረው ቤተ መቅደስ ውስጥ ገንዘብ መንዛሪዎች ሊኖሩ የቻሉት ለምንድን ነው?

ኢየሱስ ከመሞቱ ጥቂት ቀደም ብሎ ቤተ መቅደሱ ውስጥ ከሚካሄደው ፈጽሞ ተገቢ ያልሆነ ድርጊት ጋር በተያያዘ የወሰደው እርምጃ ነበር። መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ “ኢየሱስም . . . በቤተ መቅደሱ የሚሸጡትንና የሚገዙትን ሁሉ አስወጣ፤ የገንዘብ መንዛሪዎችን ጠረጴዛዎችና የርግብ ሻጮችን መቀመጫዎችም ገለባበጠ። እንዲህም አላቸው፦ ‘“ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል” ተብሎ ተጽፏል፤ እናንተ ግን የዘራፊዎች ዋሻ እያደረጋችሁት ነው።’”​—ማቴዎስ 21:12, 13

በመጀመሪያው መቶ ዘመን የነበሩ አይሁዳውያንና ወደ ይሁዲነት የተለወጡ ሰዎች በአካባቢያቸው የሚጠቀሙባቸውን ሳንቲሞች ይዘው ከበርካታ አገሮችና ከተሞች በመጓዝ ኢየሩሳሌም ወደሚገኘው ቤተ መቅደስ ይመጡ ነበር። ይሁንና ዓመታዊውን የቤተ መቅደስ ግብር ለመክፈል፣ ለመሥዋዕት የሚሆኑ እንስሳትን ለመግዛት እንዲሁም በፈቃደኝነት የሚሰጡ ሌሎች መባዎችን ለማቅረብ በኢየሩሳሌም አካባቢ በሚሠራበት ገንዘብ መጠቀም ይጠበቅባቸዋል። በመሆኑም ገንዘብ መንዛሪዎች ሰዎቹ ከተለያየ አካባቢ ይዘውት የመጡትን ሳንቲም፣ ክፍያ በመጠየቅ ወደፈለጉት የገንዘብ ዓይነት ይለውጡላቸዋል። አይሁዳውያን የሚያከብሯቸው በዓላት በሚቃረቡበት ጊዜ እነዚህ ገንዘብ መንዛሪዎች በቤተ መቅደሱ የአሕዛብ አደባባይ ውስጥ ትልልቅ ጠረጴዛዎችን ያስቀምጣሉ።

ኢየሱስ ገንዘብ መንዛሪዎቹ ቤተ መቅደሱን “የዘራፊዎች ዋሻ” እንዳደረጉት በመግለጽ ማውገዙ ሰዎቹ ለሚሰጡት አገልግሎት በጣም ከፍተኛ ክፍያ የሚጠይቁ መሆኑን እንደሚያሳይ ግልጽ ነው።

በመጽሐፍ ቅዱስ ዘመን የወይራ ዛፍ ትልቅ ቦታ ይሰጠው የነበረው ለምንድን ነው?

አምላክ፣ ሕዝቦቹ ለእሱ ታማኝ ሆነው ከተገኙ ከሌሎች ነገሮች በተጨማሪ የወይራ ዛፎችንና የወይን ተክሎችን በመስጠት እንደሚባርካቸው ቃል ገብቶላቸው ነበር። (ዘዳግም 6:10, 11) የወይራ ዛፍ በሚበቅልባቸው አካባቢዎች የሚኖሩ ሰዎች ዛሬም ድረስ ለዚህ ዛፍ ትልቅ ቦታ ይሰጣሉ። ይህ ዛፍ በአንጻራዊ ሁኔታ እምብዛም እንክብካቤ ሳይደረግለት በመቶዎች ለሚቆጠሩ ዓመታት በጣም ብዙ ፍሬ መስጠት ይችላል። አንድ የወይራ ዛፍ ድንጋያማ በሆነ አፈር ላይ ቢተከልም ማደግ የሚችል ከመሆኑም በላይ በተደጋጋሚ የሚከሰት ድርቅን መቋቋም ይችላል። ዛፉ ቢቆረጥ እንኳ ሥሩ መልሶ ትንንሽ ቅርንጫፎችን የሚያቆጠቁጥ ሲሆን ቅርንጫፎቹ ደግሞ ራሳቸውን የቻሉ ግንዶች ይሆናሉ።

በጥንት ዘመን፣ ሰዎች የዚህን ዛፍ ቅርፊትና ቅጠሎች ትኩሳት ለማብረድ ስለሚጠቀሙባቸው በጣም ተፈላጊ ነበሩ። ካረጁ ቅርንጫፎች ላይ እየተንጠባጠበ የሚወርደውና የቫኒላ መዓዛ ያለው ሙጫ ሽቶ ለመቀመም ያገለግላል። ሆኖም ዛፉ በዋነኝነት ትልቅ ቦታ የሚሰጠው ፍሬዎቹ በተለይም ዘይቱ ለምግብነት ይውሉ ስለነበር ነው። የአንድ የበሰለ የወይራ ፍሬ ውስጠኛ ክፍል ግማሽ የሚያህለው ዘይት ነው።

አንድ ጥሩ የወይራ ዛፍ በአንድ ዓመት ውስጥ እስከ 57 ሊትር ዘይት መስጠት ይችላል። ከዚህም በተጨማሪ የወይራ ዘይት ለመብራት እንደ ነዳጅ ሆኖ ያገለግላል፤ ከበዓላትና ከሃይማኖታዊ ሥነ ሥርዓቶች ጋር በተያያዘ ይሠራበታል፤ ሰውነትንና ፀጉርን ለማስዋብ ይጠቅማል፤ እንዲሁም ቁስልን ለማከምና ሕመሙን ለማስታገስ እንደ መድኃኒት ሆኖ ያገለግላል።​—ዘፀአት 27:20፤ ዘሌዋውያን 2:1-7፤ 8:1-12፤ ሩት 3:3፤ ሉቃስ 10:33, 34