በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ቤተሰብህ ደስተኛ መሆን የሚችለው እንዴት ነው?

ቤተሰብህ ደስተኛ መሆን የሚችለው እንዴት ነው?

ከአምላክ ቃል ተማር

ቤተሰብህ ደስተኛ መሆን የሚችለው እንዴት ነው?

ይህ ርዕሰ ትምህርት በአእምሮህ ሊመላለሱ የሚችሉ ጥያቄዎችን የሚያነሳ ሲሆን መልሶቹን ከመጽሐፍ ቅዱስህ ውስጥ የት ቦታ ላይ ማግኘት እንደምትችልም ይጠቁምሃል። የይሖዋ ምሥክሮች ለጥያቄዎቹ በተሰጡት መልሶች ላይ ከአንተ ጋር ቢወያዩ ደስ ይላቸዋል።

1. በሕጋዊ መንገድ መጋባት ለቤተሰብ ደስታ ወሳኝ የሆነው ለምንድን ነው?

የጋብቻን ዝግጅት ያቋቋመው ደስተኛ አምላክ የሆነው ይሖዋ ነው። ትዳር ለቤተሰብ ደስታ ወሳኝ የሆነው ጥሩ ወዳጅነት እንዲኖር ስለሚያደርግ ብቻ ሳይሆን ልጆችን ማሳደግ የሚቻልበት አስተማማኝና ምቹ ሁኔታም ስለሚፈጥር ነው። አምላክ ለጋብቻ ምን አመለካከት አለው? አንድ ባልና ሚስት ጋብቻቸውን ሕጋዊ በሆነ መንገድ እንዲፈጽሙና ጥምረታቸው ዘላቂ እንዲሆን ይፈልጋል። (ሉቃስ 2:1-5) አምላክ ባልና ሚስት አንዳቸው ለሌላው ታማኞች እንዲሆኑ ይፈልጋል። (ዕብራውያን 13:4) ይሖዋ፣ ክርስቲያኖች የትዳር ጓደኛቸውን እንዲፈቱ እንዲሁም በድጋሚ እንዲያገቡ የሚፈቅደው አንደኛው የትዳር ጓደኛ ምንዝር ከፈጸመ ብቻ ነው።​—ማቴዎስ 19:3-6, 9ን አንብብ።

2. ባልና ሚስት አንዳቸው ሌላውን እንዴት መያዝ ይኖርባቸዋል?

ይሖዋ ወንዶችንና ሴቶችን የፈጠረው በጋብቻ ውስጥ አንዳቸው የሌላውን ጉድለት እንዲያሟሉ አድርጎ ነው። (ዘፍጥረት 2:18) አንድ ባል የቤተሰብ ራስ እንደመሆኑ መጠን ለቤተሰቡ የሚያስፈልገውን ቁሳዊ ነገር ለማቅረብም ሆነ እነሱን ስለ አምላክ ለማስተማር ግንባር ቀደም መሆን አለበት። ለሚስቱ ከራስ ወዳድነት ነፃ የሆነ ፍቅር ማሳየት ይኖርበታል። የትዳር ጓደኛሞች እርስ በርስ መዋደድና መከባበር አለባቸው። ሁሉም ባልና ሚስት ፍጽምና የሚጎድላቸው በመሆኑ ይቅር ባይ መሆናቸው ደስተኛ የቤተሰብ ሕይወት እንዲኖራቸው ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያደርጋል።​—ኤፌሶን 4:31, 32⁠ን፤ ኤፌሶን 5:22-25, 33ን እና 1 ጴጥሮስ 3:7ን አንብብ።

3. በትዳርህ ደስተኛ ካልሆንክ መለያየት ይኖርብሃል?

ከትዳር ጓደኛህ ጋር አለመግባባት ቢፈጠር አንዳችሁ ሌላውን በፍቅር ለመያዝ ጥረት አድርጉ። (1 ቆሮንቶስ 13:4, 5) የአምላክ ቃል በትዳር ውስጥ ለሚፈጠሩ ችግሮች መፍትሔው መለያየት እንዳልሆነ ይናገራል። ይሁን እንጂ ሁኔታዎች አስከፊ ደረጃ ላይ ከደረሱ አንድ ክርስቲያን መለያየት ያስፈልገው እንደሆነ ሊወስን ይችላል።​—1 ቆሮንቶስ 7:10-13ን አንብብ።

4. ልጆች፣ አምላክ ምን እንድታገኙ ይፈልጋል?

ይሖዋ ደስተኛ እንድትሆኑ ይፈልጋል። የወጣትነት ዕድሜያችሁን በደስታ ማሳለፍ የምትችሉበትን ከሁሉ የተሻለ ምክር ይሰጣችኋል። ወላጆቻችሁ ካካበቱት ጥበብና ካሳለፉት የሕይወት ተሞክሮ ጥቅም እንድታገኙ ይፈልጋል። (ቆላስይስ 3:20) ይሖዋ እሱን ለማክበር የምታደርጉትን ጥረት ሁሉ ይመለከታል።​—መክብብ 11:9 እስከ 12:1⁠ን፤ ማቴዎስ 19:13-15ን እና ማቴዎስ 21:15, 16ን አንብብ።

5. ወላጆች፣ ልጆቻችሁ ደስተኞች እንዲሆኑ ማድረግ የምትችሉት እንዴት ነው?

ለልጆቻችሁ ምግብ፣ መጠለያና ልብስ ለማቅረብ በትጋት መሥራት ይኖርባችኋል። (1 ጢሞቴዎስ 5:8) ሆኖም ልጆቻችሁ ደስተኞች እንዲሆኑ አምላክን እንዲወዱና እሱ የሚላቸውን ነገር እንዲሰሙ ማስተማርም ያስፈልጋችኋል። (ኤፌሶን 6:4) ለአምላክ ፍቅር እንዳላችሁ በተግባር የምታሳዩ ከሆነ ይህ ምሳሌነታችሁ የልጆቻችሁን ልብ በጥልቅ ሊነካ ይችላል። በአምላክ ቃል ላይ ተመሥርታችሁ የምትሰጧቸው መመሪያዎች የልጆቻችሁን አስተሳሰብ በጥሩ መንገድ ሊቀርጹት ይችላሉ።​—ዘዳግም 6:4-7ን እና ምሳሌ 22:6ን አንብብ።

ልጆቻችሁ የእናንተን ምስጋና እና ማበረታቻ ማግኘታቸው ይጠቅማቸዋል። በሌላ በኩል ደግሞ እርማትና ተግሣጽ ያስፈልጋቸዋል። እንዲህ ዓይነቱ ሥልጠና ደስታቸውን እንዲያጡ ከሚያደርጉ ድርጊቶች እንዲርቁ ይረዳቸዋል። (ምሳሌ 22:15) ያም ቢሆን ልጆችን በኃይል ወይም በጭካኔ መቅጣት ተገቢ አይደለም።​—ቆላስይስ 3:21ን አንብብ።

የይሖዋ ምሥክሮች ወላጆችንም ሆነ ልጆችን ለመርዳት ታስበው የተዘጋጁ በርካታ መጻሕፍት አሳትመዋል። እነዚህ መጻሕፍት በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ተመሥርተው የተዘጋጁ ናቸው።​—መዝሙር 19:7, 11ን አንብብ።

ተጨማሪ ማብራሪያ ለማግኘት በይሖዋ ምሥክሮች የተዘጋጀውን ትክክለኛው የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ምንድን ነው? የተባለውን መጽሐፍ ምዕራፍ 14 ተመልከት።