በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ከአምላክ ቃል ተማር

መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ወደፊቱ ጊዜ ይተነብያል?

መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ወደፊቱ ጊዜ ይተነብያል?

ይህ ርዕስ በአእምሮህ ሊመላለሱ የሚችሉ ጥያቄዎችን በማንሳት መልሶቹን በመጽሐፍ ቅዱስህ ውስጥ የት ቦታ ላይ ማግኘት እንደምትችል ይጠቁምሃል። የይሖዋ ምሥክሮች ለጥያቄዎቹ በተሰጡት መልሶች ላይ ከአንተ ጋር ለመወያየት ፈቃደኞች ናቸው።

1. የመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢቶች ዝርዝር ጉዳዮችን ያካተቱ ናቸው?

ስለ ወደፊቱ ጊዜ በዝርዝር ትንቢት መናገር የሚችለው ሁሉን ቻይ የሆነው አምላክ ብቻ ነው። (አሞጽ 3:7) ለምሳሌ ያህል፣ መሲሕ ወይም ክርስቶስ ተብሎ የሚጠራ ሰው እንደሚመጣ ከጥንት ጀምሮ ተናግሯል። መሲሑ፣ ታማኝ የነበረው የአብርሃም ዝርያ እንደሚሆንም አምላክ አስቀድሞ ገልጾ ነበር። ይህ መሲሕ፣ ታዛዥ የሆኑ የሰው ልጆች ከበሽታ ነፃ የሆነ ፍጹም ሕይወት መልሰው እንዲያገኙ የሚያደርግ ገዥ ይሆናል። (ዘፍጥረት 22:18፤ ኢሳይያስ 53:4, 5) ይህ ተስፋ የተደረገበት መሲሕ የሚመጣው ከቤተልሔም እንደሚሆንም ተተንብዮ ነበር።​—ሚክያስ 5:2ን አንብብ።

ተስፋ የተሰጠበት መሲሕ ኢየሱስ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ፣ መሲሑ ከድንግል እንደሚወለድና በሰዎች እንደሚናቅ ከሰባት መቶ ዓመታት በፊት አስቀድሞ ተናግሯል። ይህ መሲሕ ለብዙዎች ኃጢአት ሲል ሕይወቱን እንደሚሰጥና ከባለጠጎች ጋር እንደሚቀበርም ተገልጿል። (ኢሳይያስ 7:14፤ 53:3, 9, 12) በተጨማሪም መጽሐፍ ቅዱስ መሲሑ በአህያ ላይ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም እንደሚገባና በ30 ብር አልፎ እንደሚሰጥ ከአምስት መቶ ዓመታት በፊት ተናግሯል። እያንዳንዱ ዝርዝር ነገር በትክክል ተፈጽሟል።​—ዘካርያስ 9:9ን እና ዘካርያስ 11:12ን አንብብ።

2. አምላክ አንድ ነገር የሚከናወንበትን ቀን በተመለከተ አስቀድሞ ትንቢት ይናገራል?

ከአምስት መቶ ዓመታት በፊት መጽሐፍ ቅዱስ መሲሑ የሚገለጥበትን ዓመት በትክክል ተንብዮአል። በዚህ ትንቢት ላይ መሲሑ እስከሚገለጥበት ዓመት ድረስ ያለው ጊዜ የተገለጸው ምሳሌያዊ ትርጉም ባለው ሱባዔ ወይም ሳምንት ሲሆን እያንዳንዱ ቀን፣ የአንድ ዓመት ርዝመት አለው። ስለዚህ እያንዳንዱ “ሱባዔ” የሰባት ዓመት ርዝመት ይኖረዋል። በትንቢቱ ላይ መሲሑ እስኪመጣ ድረስ 69 ምሳሌያዊ የዓመታት ሳምንታት (7 ሲደመር 62 ሳምንታት) እንደሚያልፉ ተገልጿል። ይህ ደግሞ 483 ዓመታት ይሆናል። ታዲያ ይህ ጊዜ የጀመረው መቼ ነው? መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚገልጸው የአምላክ አገልጋይ ነህምያ ኢየሩሳሌምን በድጋሚ መገንባት ሲጀምር ነው። የፋርስ ታሪክ እንደሚያሳየው ደግሞ ይህ የሆነው በ455 ዓ.ዓ. ነው። (ነህምያ 2:1-5) ልክ ከ483 ዓመታት በኋላ ይኸውም በ29 ዓ.ም. ኢየሱስ መሲሕ ሆኖ ተጠመቀ።​—ዳንኤል 9:25ን አንብብ።

3. የመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢቶች በዛሬው ጊዜ እየተፈጸሙ ነው?

ኢየሱስ በጊዜያችን ስለሚፈጸሙ ትልቅ ትርጉም ያላቸው ክንውኖች ትንቢት ተናግሯል። ትንቢቱ ስለ አምላክ መንግሥት ምሥራች የሚናገር ሐሳብ ይዟል፤ ይህ መንግሥት በዓለም ዙሪያ ለሚኖሩ አምላክን ለሚወዱ ሰዎች እፎይታ ያመጣል። የአምላክ መንግሥት አሁን የምንኖርበትን ክፉ ሥርዓት ሙሉ በሙሉ ያጠፋል።​—ማቴዎስ 24:14, 21, 22ን አንብብ።

የመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢቶች በዚህ ሥርዓት መደምደሚያ ላይ ስለሚከናወኑት ነገሮች በዝርዝር ይገልጻሉ። የሰው ልጅ በሥልጣኔ ከፍተኛ ደረጃ ላይ ከመድረሱ አንጻር ከሚጠበቀው ነገር በተቃራኒ፣ ሰዎች ምድርን እንደሚያበላሿት መጽሐፍ ቅዱስ ይናገራል። እንደ ጦርነት፣ የምግብ እጥረት፣ የምድር ነውጦችና ቸነፈር የመሳሰሉ ችግሮች ይባባሳሉ። (ሉቃስ 21:11፤ ራእይ 11:18) የሥነ ምግባር መሥፈርቶች እያሽቆለቆሉ ይሄዳሉ። በእነዚህ አስቸጋሪ ጊዜያት የኢየሱስ ተከታዮች የአምላክን መንግሥት ምሥራች ለሁሉም ብሔራት ይሰብካሉ።​—ማቴዎስ 24:3, 7, 8ን እና 2 ጢሞቴዎስ 3:1-5ን አንብብ።

4. የሰው ልጆች የወደፊት ዕጣ ምንድን ነው?

ሁሉን ቻይ የሆነው አምላክ ታማኝ ለሆኑ የሰው ልጆች በረከቶችን አዘጋጅቶላቸዋል። መሲሑ ኢየሱስ ክርስቶስ እና ከእሱ ጋር ተባባሪ ገዢዎች እንዲሆኑ የተመረጡት ሰዎች ከሰማይ ሆነው ምድርን ያስተዳድራሉ። ይህ መንግሥት ለአንድ ሺህ ዓመት ይገዛል። ሙታን የሚነሱ ሲሆን የዘላለም ሕይወት የማግኘት አጋጣሚ ይሰጣቸዋል። ከዚህም በላይ የአምላክ መንግሥት በዚያን ጊዜ የሚኖሩትን ሁሉ ከበሽታቸው ይፈውሳቸዋል። ሕመምና ሞት ጨርሶ ይወገዳል።​—ራእይ 5:10ን፣ 20:6, 12⁠ን እና ራእይ 21:4, 5ን አንብብ።

ተጨማሪ ማብራሪያ ለማግኘት ትክክለኛው የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ምንድን ነው? የተባለውን መጽሐፍ ከገጽ 23-25 እና ከገጽ 197-201 ተመልከት።