በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ይህን ያውቁ ኖሯል?

ይህን ያውቁ ኖሯል?

ይህን ያውቁ ኖሯል?

ኢየሱስ “ሁለት ኪሎ ሜትር አብረኸው ሂድ” ሲል ምን ማለቱ ነበር?

ኢየሱስ ዝነኛ በሆነው የተራራ ስብከቱ ላይ “አንድ ባለሥልጣን አንድ ኪሎ ሜትር እንድትሄድ ቢያስገድድህ ሁለት ኪሎ ሜትር አብረኸው ሂድ” በማለት ተናግሮ ነበር። (ማቴዎስ 5:41) የኢየሱስ አድማጮች፣ ይህን ሐሳብ ሕዝቡ ከሚሰጠው የግዳጅ አገልግሎት ጋር አያይዘውት መሆን አለበት፤ የመንግሥት ባለሥልጣናት ወይም የሮም ወታደሮች ሕዝቡ አንድ ዓይነት አገልግሎት እንዲሰጡ ማስገደድ ይችል ነበር።

በመጀመሪያው መቶ ዘመን ዓ.ም. እስራኤላውያን በሮማውያን አገዛዝ ሥር ነበሩ። ሮማውያኑ ሰዎችንም ሆነ እንስሳትን አንድ ዓይነት አገልግሎት እንዲሰጡ ከማስገደድ ወደኋላ አይሉም፤ እንዲሁም መንግሥታዊ ሥራዎችን ሲያከናውኑ አስፈላጊ እንደሆነ የተሰማቸውን ማንኛውንም ነገር ነጥቀው ከመውሰድ አይመለሱም። ለምሳሌ የሮም ወታደሮች፣ የቀሬና ተወላጅ የሆነው ስምዖን የኢየሱስን የመከራ እንጨት የሚሰቀልበት ቦታ ድረስ ተሸክሞ እንዲያደርስ አስገድደውት ነበር። (ማቴዎስ 27:32) እንዲህ ያሉ የግዳጅ አገልግሎቶች ሕዝቡን የሚጨቁኑ በመሆናቸው አይሁዳውያኑ በእነዚህ ሥራዎች ከመማረርም አልፈው አጥብቀው ይጠሏቸው ነበር።

ሕዝቡ አንድን ሸክም ተሸክመው ምን ያህል ርቀት መሄድ ይጠበቅባቸው እንደነበር አናውቅም። ይሁንና ከሚጠበቅባቸው ርቀት በላይ ተጨማሪ መንገድ ለመጓዝ ፈቃደኞች ይሆናሉ ብሎ ማሰብ የማይመስል ነገር ነው። በመሆኑም ኢየሱስ ለአድማጮቹ ሁለት ኪሎ ሜትር እንዲሄዱ ሲነግራቸው በሥልጣን ላይ ያሉ ሰዎች የሚጠይቋቸው አገልግሎቶች ከአምላክ ሕግ ጋር የሚጋጩ እስካልሆኑ ድረስ የተጠየቁትን ሳያማርሩ እንዲያከናውኑ እያሳሰባቸው ነበር።​—ማርቆስ 12:17

በወንጌል ዘገባዎች ውስጥ የተጠቀሰው ሐና ማን ነው?

ሐና (ሐናነስን) በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ‘የካህናት አለቃ’ ተብሎ የተገለጸ ሲሆን ኢየሱስ ችሎት ፊት በቀረበበት ወቅት በዚህ ቦታ ላይ ያገለግል ነበር። (ሉቃስ 3:2፤ ዮሐንስ 18:13፤ የሐዋርያት ሥራ 4:6) ሐና የእስራኤል ሊቀ ካህናት የነበረው የቀያፋ አማት ነው፤ እሱ ራሱም ቢሆን ከ6 ወይም 7 ዓ.ም. አንስቶ ሮማዊው አገረ ገዥ ቫሌርዩስ ግራቱስ ከሥልጣኑ እስካወረደው እስከ 15 ዓ.ም. ገደማ ድረስ ሊቀ ካህናት ሆኖ አገልግሏል። ሐና፣ ከሊቀ ካህንነቱ ቢወርድም በእስራኤል ውስጥ ከፍተኛ ሥልጣን ነበረው። ከሐና ልጆች መካከል አምስቱ እንዲሁም የልጁ ባል ሊቀ ካህናት ሆነው አገልግለዋል።

እስራኤል ራሷን የቻለች ብሔር በነበረችበት ጊዜ፣ ሊቀ ካህናቱ እስከ ሕይወቱ ፍጻሜ ድረስ በዚህ ኃላፊነት ይቀጥል ነበር። (ዘኍልቍ 35:25) ብሔሩ በሮም ቁጥጥር ሥር ከወደቀ በኋላ ግን ሊቀ ካህናቱ በዚህ ኃላፊነት የሚቀጥለው በሮም ባለሥልጣናትና በሮማውያን ነገሥታት በጎ ፈቃድ ሆነ፤ እነዚህ ባለሥልጣናት በተመቻቸው ጊዜ ሊቀ ካህናቱን ማውረድ ይችሉ ነበር። የሶርያ አገረ ገዥ የነበረው ቄሬኔዎስ በ6 ወይም 7 ዓ.ም. ጆዛር የተባለውን ሊቀ ካህናት ከኃላፊነቱ አውርዶ ሐናን እንደሾመ የታሪክ ምሑር የሆነው ፍላቭየስ ጆሴፈስ ዘግቧል። እነዚህ አረማዊ ገዢዎች የሚሾሙትን ሊቀ ካህናት የሚመርጡት ከካህናቱ መካከል የነበረ ይመስላል።

የሐና ቤተሰብ አባላት የናጠጡ ሀብታሞችና በጣም ስግብግቦች ነበሩ። እነዚህ ሰዎች ሀብታም ሊሆኑ የቻሉት በቤተ መቅደሱ ውስጥ ለሚቀርቡ መሥዋዕቶች የሚያስፈልጉትን እንደ ርግቦች፣ በጎች፣ ዘይትና ወይን ያሉትን ሸቀጦች ንግድ ብቻቸውን ተቆጣጥረው ስለነበረ ሳይሆን አይቀርም። የሐና ልጅ የሆነው ሐናነስ (ሐናንያ) “የወጣላቸው አጭበርባሪዎች የሆኑ አገልጋዮች” እንደነበሩት ጆሴፈስ የጻፈ ሲሆን “እነዚህ አገልጋዮች የካህናቱን አሥራት በጉልበት ይወስዳሉ፤ እንዲሁም ለመስጠት ፈቃደኛ ያልሆኑትን ካህናት ከመደብደብ ወደኋላ አይሉም” በማለት ዘግቧል።