በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ይህን ያውቁ ኖሯል?

ይህን ያውቁ ኖሯል?

በጥንት ዘመን አንድ ሰው ልብሱን መቅደዱ ምን ትርጉም ነበረው?

በርካታ ሰዎች ልብሳቸውን እንደቀደዱ የሚገልጹ ታሪኮች በቅዱሳን መጻሕፍት ላይ ተመዝግበው ይገኛሉ። እንዲህ ያለው ድርጊት በዚህ ዘመን ላለ ሰው እንግዳ ነገር ቢመስልም በአይሁዶች ዘንድ ግን ሰዎች ተስፋ ሲቆርጡ፣ ሲያዝኑ፣ ውርደት ሲደርስባቸው፣ ሲቆጡ ወይም በለቅሶ ጊዜ የተሰማቸውን ጥልቅ ስሜት የሚገልጹበት መንገድ ነበር።

ለምሳሌ ያህል ሮቤል፣ ዮሴፍ ለባርነት እንደተሸጠ ሲሰማ እሱን ለማዳን የነበረው እቅድ በመክሸፉ ‘ልብሱን ቀዷል።’ የዮሴፍ አባት ያዕቆብም፣ ልጁ በአውሬ እንደተበላ ስላሰበ ‘ልብሱን ቀዶ’ ነበር። (ዘፍ. 37:18-35) ኢዮብ ልጆቹ በሙሉ እንደተገደሉ ሲነገረው ‘ልብሱን ቀዷል።’ (ኢዮብ 1:18-20) እስራኤላውያን በጦርነት ተሸንፈው ሁለቱ የዔሊ ልጆች በተገደሉና የቃል ኪዳኑ ታቦት በተማረከ ጊዜ አንድ መልእክተኛ ‘ልብሱን በመቅደድ’ ወሬውን ለሊቀ ካህናቱ ዔሊ ለመንገር ሄዶ ነበር። (1 ሳሙ. 4:12-17) ኢዮስያስ የሕጉ መጽሐፍ ሲነበብለት ሕዝቡ ምን ያህል እንደተሳሳቱ ስለተገነዘበ “ልብሱን ቀደደ።”—2 ነገ. 22:8-13

ኢየሱስ ለፍርድ በቀረበበት ጊዜ ሊቀ ካህናቱ ቀያፋ የኢየሱስን ንግግር አምላክን እንደ መስደብ አድርጎ ስለቆጠረው “ልብሱን ቀዶ” ነበር። (ማቴ. 26:59-66) በረቢዎች ሃይማኖታዊ ሕግ መሠረት መለኮታዊው ስም ሲሰደብ የሰማ ማንኛውም ሰው ልብሱን መቅደድ ነበረበት። ከኢየሩሳሌም ጥፋት በኋላ ስለነበረው ሁኔታ ግን አንድ ረቢ እንዲህ በማለት ተናግሯል፦ “በዚህ ዘመን መለኮታዊው ስም ሲሰደብ የሰማ ሰው ልብሱን መቅደድ አያስፈልገውም፤ አለበለዚያ ልብሶቹ ሁሉ የተቀዳደዱ ይሆናሉ።”

እርግጥ ነው፣ አንድ ሰው ሐዘኑ ከልብ እስካልሆነ ድረስ ልብሱን መቅደዱ በአምላክ ፊት ምንም ዋጋ የለውም። በመሆኑም ይሖዋ ለሕዝቡ ‘ልብሳቸውን ሳይሆን ልባቸውን እንዲቀድዱና ወደ እሱ እንዲመለሱ’ ነግሯቸው ነበር።—ኢዩ. 2:13