በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

መንፈሳዊውን ገነት ይበልጥ አስውቡት

መንፈሳዊውን ገነት ይበልጥ አስውቡት

“እግሬ የሚያርፍበትንም ስፍራ አከብራለሁ።”—ኢሳ. 60:13

መዝሙሮች፦ 102, 75

1, 2. በዕብራይስጥ ቅዱሳን መጻሕፍት ላይ “የእግር ማሳረፊያ” የሚለው አገላለጽ ምንን ለማመልከት አገልግሏል?

ይሖዋ አምላክ “ሰማይ ዙፋኔ ነው፤ ምድር ደግሞ የእግሬ ማሳረፊያ ናት” ብሏል፤ እንዲህ ማለቱም የተገባ ነው። (ኢሳ. 66:1) ‘የእግሩን ማሳረፊያ’ አስመልክቶ ደግሞ “እግሬ የሚያርፍበትንም ስፍራ አከብራለሁ” ብሏል። (ኢሳ. 60:13) ይህን የሚያደርገው እንዴት ነው? ደግሞስ የምንኖረው አምላክ “የእግሬ ማሳረፊያ” ብሎ በጠራው ቦታ ከመሆኑ አንጻር ይህ ጥቅስ ለእኛ ምን ትርጉም አለው?

2 “የእግር ማሳረፊያ” የሚለው አገላለጽ ከምድርም በተጨማሪ እስራኤላውያን ይጠቀሙበት የነበረውን የጥንቱን ቤተ መቅደስ ለማመልከት በዕብራይስጥ ቅዱሳን መጻሕፍት ላይ በምሳሌያዊ መንገድ ተሠርቶበታል። (1 ዜና 28:2፤ መዝ. 132:7) በምድር ላይ የነበረው ይህ ቤተ መቅደስ የእውነተኛው አምልኮ ማዕከል ሆኖ አገልግሏል። በዚህ ምክንያት ይህ ቤተ መቅደስ በአምላክ ዓይን እጅግ ውብ ነበር፤ እንዲሁም ቤተ መቅደሱ መኖሩ በራሱ የይሖዋ እግር የሚያርፍበትን ቦታ ያስከብር ነበር።

3. ታላቁ የአምላክ መንፈሳዊ ቤተ መቅደስ ምንድን ነው? የተቋቋመውስ መቼ ነው?

3 በዛሬው ጊዜ የእውነተኛው አምልኮ ማዕከል በምድር ላይ የሚገኝ ቤተ መቅደስ መሆኑ ቀርቷል። ያም ቢሆን ከማንኛውም ሕንፃ ይበልጥ ይሖዋን የሚያስከብር መንፈሳዊ ቤተ መቅደስ አለ። ይህ ቤተ መቅደስ በኢየሱስ ክርስቶስ ክህነትና መሥዋዕት አማካኝነት ከአምላክ ጋር ለመታረቅ የሚያስችለውን ዝግጅት ያመለክታል። ቤተ መቅደሱ የተቋቋመው ኢየሱስ በ29 ዓ.ም. ሲጠመቅ ማለትም የይሖዋ ታላቅ ቤተ መቅደስ ሊቀ ካህናት ሆኖ ሲቀባ ነው።—ዕብ. 9:11, 12

4, 5. (ሀ) መዝሙር 99 የይሖዋ እውነተኛ አምላኪዎች ምን ልባዊ ፍላጎት እንዳላቸው ይገልጻል? (ለ) ራሳችንን ምን ብለን መጠየቅ ይኖርብናል?

4 እኛም ለመንፈሳዊው ቤተ መቅደስ ያለንን አድናቆት መግለጽ ስለምንፈልግ የይሖዋን ስም በማሳወቅ እሱን እናወድሰዋለን፤ እንዲሁም በምሕረት ተነሳስቶ የቤዛ ዝግጅት ስላደረገልን ከፍ ከፍ እናደርገዋለን። በዛሬው ጊዜ ከስምንት ሚሊዮን የሚበልጡ እውነተኛ ክርስቲያኖች ይሖዋን እያከበሩት መሆኑ ምንኛ የሚያስደስት ነው! ምድርን ለቀው ወደ ሰማይ ከሄዱ በኋላ አምላክን እንደሚያወድሱ አድርገው በተሳሳተ መንገድ ከሚያስቡ አንዳንድ ሃይማኖተኛ ሰዎች በተቃራኒ ሁሉም የይሖዋ ምሥክሮች በአሁኑ ወቅት እዚሁ ምድር ላይ አምላክን የማመስገንን አስፈላጊነት ተገንዝበዋል።

5 እንዲህ በማድረግ በመዝሙር 99:1-3, 5 ላይ የተገለጹትን የይሖዋን ታማኝ አገልጋዮች ምሳሌ እንከተላለን። (ጥቅሱን አንብብ።) ይህ መዝሙር እንደሚጠቁመው ሙሴ፣ አሮንና ሳሙኤል በዘመናቸው የነበረውን የእውነተኛ አምልኮ ዝግጅት ሙሉ በሙሉ ደግፈዋል። (መዝ. 99:6, 7) በዛሬው ጊዜም በምድር ያሉት የኢየሱስ ቅቡዓን ወንድሞች በሰማይ ከእሱ ጋር ካህናት ሆነው ለማገልገል ከመሄዳቸው በፊት በመንፈሳዊው ቤተ መቅደስ ምድራዊ አደባባይ በታማኝነት እያገለገሉ ነው። በሚሊዮን የሚቆጠሩት “ሌሎች በጎች” በታማኝነት ይደግፏቸዋል። (ዮሐ. 10:16) ቅቡዓንና ሌሎች በጎች ያላቸው ተስፋ የተለያየ ቢሆንም የአምላክ የእግር ማሳረፊያ በሆነችው በምድር ላይ ሁለቱም ቡድኖች ይሖዋን በአንድነት እያመለኩ ነው። ይሁንና ‘ይሖዋ ለንጹሕ አምልኮ ያደረገውን ዝግጅት በተሟላ ሁኔታ እየደገፍኩ ነው?’ ብለን ራሳችንን መጠየቃችን የተገባ ነው።

በአምላክ መንፈሳዊ ቤተ መቅደስ የሚያገለግሉት እነማን ናቸው?

6, 7. የጥንቶቹ ክርስቲያኖች ምን ችግር አጋጠማቸው? ከበርካታ ዘመናት በኋላስ ምን አስፈለገ?

6 የክርስቲያን ጉባኤ ከተቋቋመ መቶ ዓመት እንኳ ሳይሞላው፣ አስቀድሞ እንደተነገረው ክህደት መስፋፋት ጀመረ። (ሥራ 20:28-30፤ 2 ተሰ. 2:3, 4) ከዚያ በኋላ አምላክን በመንፈሳዊ ቤተ መቅደሱ በትክክል እያገለገሉ ያሉትን ሰዎች ማንነት መለየት አስቸጋሪ እየሆነ ሄደ። ይሖዋ፣ በተሾመው ንጉሡ በኢየሱስ ክርስቶስ አማካኝነት ነገሮች ግልጽ እንዲሆኑ ያደረገው ከዘመናት በኋላ ነው።

7 የይሖዋን ሞገስ ያገኙትና በመንፈሳዊው ቤተ መቅደሱ እያገለገሉ ያሉት እነማን እንደሆኑ በ1919 በግልጽ ታወቀ። እነዚህ ክርስቲያኖች ለአምላክ የሚያቀርቡት አገልግሎት በእሱ ዘንድ ይበልጥ ተቀባይነት እንዲኖረው በመንፈሳዊ ሁኔታ ነጽተዋል። (ኢሳ. 4:2, 3፤ ሚል. 3:1-4) ሐዋርያው ጳውሎስ ከበርካታ ዘመናት በፊት የተመለከተው ራእይ በዚህ ጊዜ በተወሰነ መንገድ ፍጻሜ ማግኘት ጀመረ።

8, 9. ጳውሎስ በራእይ የተመለከተውን “ገነት” ሦስት ገጽታዎች አብራራ።

8 ጳውሎስ የተመለከተው ራእይ በ2 ቆሮንቶስ 12:1-4 ላይ ተመዝግቦ ይገኛል። (ጥቅሱን አንብብ።) ጳውሎስ የተመለከተውን ተአምራዊ ራእይ፣ የተገለጠ መልእክት በማለትም ገልጾታል። የተመለከተው ነገር በእሱ ዘመን የነበረ ሳይሆን ወደፊት የሚፈጸም ነው። ጳውሎስ “ወደ ሦስተኛው ሰማይ [ሲነጠቅ]” የተመለከተው “ገነት” ምንድን ነው? ቃል በቃል በምድር ላይ፣ በመንፈሳዊ ሁኔታ እንዲሁም በሰማይ የሚኖረውን ገነት ያመለክታል፤ ወደፊት ሦስቱም ነገሮች በአንድ ወቅት ላይ ይኖራሉ። እንዲህ የምንለው ለምንድን ነው? ምክንያቱም “ገነት” የሚለው ቃል ወደፊት በምድር ላይ ቃል በቃል የሚኖረውን ገነት ሊጠቁም ይችላል። (ሉቃስ 23:43) ከዚህም ሌላ በአዲሱ ዓለም ውስጥ በተሟላ ሁኔታ የሚኖረውን መንፈሳዊ ገነትም ሊያመለክት ይችላል። በተጨማሪም ‘የአምላክን ገነት’ ይኸውም ይሖዋ በሚኖርበት በሰማይ የመሆንን አስደናቂ መብት ሊያመለክት ይችላል።—ራእይ 2:7

9 ይሁንና ጳውሎስ “በአንደበት ሊገለጹ የማይችሉና ሰው እንዲናገራቸው ያልተፈቀዱ ቃላት [እንደሰማ]” የገለጸው ለምንድን ነው? ጳውሎስ ይህን የተናገረው በዚህ ራእይ ላይ የተመለከታቸውን አስደናቂ ነገሮች በዝርዝር የሚያብራራበት ጊዜ ስላልደረሰ ነው። ዛሬ ግን የአምላክ ሕዝቦች ስላገኟቸው በረከቶች መናገር ተፈቅዷል።

10. “መንፈሳዊ ገነት” እና “መንፈሳዊ ቤተ መቅደስ” የሚሉት አገላለጾች ተመሳሳይ ነገር አያመለክቱም የምንለው ለምንድን ነው?

10 “መንፈሳዊ ገነት” የሚለው ሐሳብ ከምንጠቀምባቸው ቲኦክራሲያዊ አገላለጾች አንዱ ሆኗል። ይህ አገላለጽ ከአምላክና ከወንድሞቻችን ጋር ሰላማዊ ግንኙነት እንዲኖረን የሚያደርገውን ልዩ የሆነና በመንፈሳዊ የበለጸገ ሁኔታ ያመለክታል። እርግጥ ነው፣ “መንፈሳዊ ገነት” እና “መንፈሳዊ ቤተ መቅደስ” የሚሉት ሐሳቦች አንድ እንደሆኑ አድርገን ልንደመድም አይገባም። መንፈሳዊ ቤተ መቅደስ የሚባለው አምላክ ከእውነተኛው አምልኮ ጋር በተያያዘ ያደረገው ዝግጅት ነው። በሌላ በኩል ደግሞ መንፈሳዊው ገነት አምላክ ሞገሱን የሚያሳያቸውን እንዲሁም በመንፈሳዊው ቤተ መቅደሱ እሱን የሚያገለግሉትን ሰዎች በግልጽ ለመለየት ይረዳል።—ሚል. 3:18

11. ከመንፈሳዊው ገነት ጋር በተያያዘ በዛሬው ጊዜ ምን መብት አለን?

11 ከ1919 ጀምሮ ይሖዋ ፍጽምና የጎደላቸው ሰዎች በምድር ላይ ያለውን መንፈሳዊ ገነት በማልማት፣ በማጠናከርና በማስፋፋት ከእሱ ጋር አብረው እንዲሠሩ መፍቀዱን ማወቃችን ምንኛ የሚያስደስት ነው! በዚህ አስደናቂ ሥራ የበኩልህን ድርሻ እያበረከትክ እንዳለ ይሰማሃል? እንዲሁም የይሖዋን ‘የእግር ማሳረፊያ’ በማስከበር ረገድ ከእሱ ጋር አብረህ መሥራትህን ለመቀጠል ትነሳሳለህ?

የይሖዋ ድርጅት ይበልጥ እየተዋበ ነው

12. የኢሳይያስ 60:17ን ፍጻሜ በተመለከተ ሁላችንም ስለ ምን ነገር እርግጠኞች ነን? (በመግቢያው ላይ ያለውን ፎቶግራፍ ተመልከት።)

12 ከይሖዋ ድርጅት ምድራዊ ክፍል ጋር በተያያዘ አስደናቂ የሆነ ለውጥ እንደሚኖር በኢሳይያስ 60:17 ላይ አስቀድሞ ተነግሯል። (ጥቅሱን አንብብ።) ወጣቶች ወይም በእውነት ቤት ብዙ ያልቆዩ ክርስቲያኖች ስለ እነዚህ ለውጦች አንብበው አሊያም ሌሎች ሲናገሩ ሰምተው ሊሆን ይችላል። ይህን ለውጥ በዓይናቸው የተመለከቱ ወንድሞችና እህቶችማ እንዴት ያለ ትልቅ መብት አግኝተዋል! ይሖዋ በሾመው ንጉሡ አማካኝነት ለድርጅቱ ትምህርትና አመራር እየሰጠ መሆኑን እርግጠኞች መሆናቸው የሚገርም አይደለም። በአምላክ መተማመናቸው የተገባ እንደሆነ ያውቃሉ፤ ሁላችንም ብንሆን እንዲህ ያለ የመተማመን ስሜት አለን። እነዚህ ወንድሞች ከልብ በመነጨ ስሜት ሐሳባቸውን ሲገልጹ መስማት እምነትህን ያጠናክረዋል፤ እንዲሁም በይሖዋ ይበልጥ እንድትታመን ያደርግሃል።

13. በመዝሙር 48:12-14 መሠረት ምን ኃላፊነት ተጥሎብናል?

13 በእውነት ቤት የቆየንበት ጊዜ ምንም ያህል ቢሆን ለሌሎች ስለ ይሖዋ ድርጅት ማውራት ይኖርብናል። በዚህ ክፉ፣ ምግባረ ብልሹና ፍቅር የጎደለው ዓለም ውስጥ መንፈሳዊ ገነት መኖር መቻሉ በእርግጥም በዘመናችን የተፈጸመ ተአምር ነው! የይሖዋን ድርጅት ወይም ‘የጽዮንን’ አስደናቂ ነገሮች እንዲሁም የመንፈሳዊውን ገነት እውነት “ለመጪዎቹ ትውልዶች” በደስታ ልናስተላልፍ ይገባል።መዝሙር 48:12-14ን አንብብ።

14, 15. በ1970ዎቹ ዓመታት የትኞቹ ድርጅታዊ ማስተካከያዎች ተደርገዋል? ማስተካከያዎቹስ ምን ጥቅም አስገኝተዋል?

14 በመካከላችን ያሉ አንዳንድ አረጋውያን ባለፉት ዓመታት ለይሖዋ ድርጅት ምድራዊ ክፍል ውበት የጨመሩ ድርጅታዊ ማስተካከያዎች ሲደረጉ ተመልክተዋል። ጉባኤዎች በሽማግሌዎች አካል ሳይሆን በአንድ የጉባኤ አገልጋይ፣ አገሮች ደግሞ በቅርንጫፍ ኮሚቴ ሳይሆን በአንድ የበላይ ተመልካች ይመሩ እንደነበር ያስታውሳሉ፤ በተጨማሪም መመሪያ የሚተላለፈው በግልጽ በሚታወቀው የይሖዋ ምሥክሮች የበላይ አካል አማካኝነት ሳይሆን በመጠበቂያ ግንብ ማኅበር ፕሬዚዳንት በኩል እንደነበረም ትዝ ይላቸው ይሆናል። ሥራውን በኃላፊነት የሚመሩት ለአምላክ ያደሩ ወንድሞች፣ ከሌሎች ታማኝ ወንድሞች እገዛ ያገኙ የነበረ ቢሆንም በጉባኤዎች፣ በቅርንጫፍ ቢሮዎችና በዋናው መሥሪያ ቤት ውስጥ ውሳኔ የሚያስተላልፉት ብቻቸውን ነበር። በ1970ዎቹ የተደረጉት ማስተካከያዎች የበላይ ተመልካችነት ኃላፊነትን የሚይዘው አንድ ግለሰብ መሆኑ ቀርቶ የሽማግሌዎች አካል እንዲሆን መንገድ ከፍተዋል።

15 እነዚህ ማስተካከያዎች ያስገኙት ጥቅም አለ? እንዴታ! ይህም የሚጠበቅ ነው። ለምን? ምክንያቱም ማስተካከያዎቹ በቅዱሳን መጻሕፍት ውስጥ የሚገኘውን አሠራር በተመለከተ ባገኘነው ተጨማሪ እውቀት ላይ የተመሠረቱ ናቸው። አንድ ግለሰብ ብቻ የመወሰን ኃላፊነት ከሚኖረው ይልቅ ይሖዋ “ስጦታ አድርጎ” የሰጠን “ሰዎች” ሁሉ ያላቸው መልካም ችሎታ አንድ ላይ መቀናጀቱ ድርጅቱ እንዲጠቀም አድርጓል።—ኤፌ. 4:8፤ ምሳሌ 24:6

ይሖዋ በሁሉም ቦታ ለሚኖሩ ሰዎች በጣም የሚያስፈልጋቸውን መመሪያ እየሰጠ ነው (አንቀጽ 16, 17ን ተመልከት)

16, 17. በቅርቡ ከተደረጉት ማስተካከያዎች መካከል አንተን በግልህ ያስደሰተህ የትኛው ነው? ለምንስ?

16 በቅርብ ጊዜ የተደረጉ ማስተካከያዎችን ደግሞ እንመልከት፤ ከምናሰራጫቸው ጽሑፎች መልክና ይዘት እንዲሁም ከምናሰራጭበት ዘዴ ጋር በተያያዘ የተደረጉትን ለውጦች እንደ ምሳሌ መውሰድ እንችላለን። ተግባራዊ ነጥቦችን የያዙ እንዲሁም ማራኪ በሆነ መንገድ የቀረቡ ጽሑፎችን በአገልግሎት ላይ ማበርከት ምንኛ አስደሳች ነው! ከዚህም ሌላ እውነትን ለማሰራጨት jw.org እንደተባለው ድረ ገጽ ያሉትን ዘመናዊ የቴክኖሎጂ ውጤቶች ስንጠቀም ይሖዋ በየትኛውም ቦታ ያሉ ሰዎች በጣም የሚያስፈልጋቸውን ሆኖም ብዙዎቹ ያላገኙትን መመሪያ ለመስጠት ፍላጎት እንዳለው እናሳያለን።

17 ሌላው ሳይጠቀስ የማይታለፍ ነገር ደግሞ የቤተሰብ አምልኮ ወይም የግል ጥናት ለማድረግ ሰፋ ያለ ጊዜ እንድናገኝ ሲባል የተደረገው ጥበብ የታከለበት ማስተካከያ ነው። ከትላልቅ ስብሰባዎች ጋር በተያያዘ የተደረጉትን ለውጦችም እናደንቃለን። ስብሰባዎቹ ከዓመት ወደ ዓመት እየተሻሻሉ እንደመጡ ብዙውን ጊዜ እንናገራለን። በተጨማሪም ባሉን በርካታ ቲኦክራሲያዊ ትምህርት ቤቶች አማካኝነት የሚሰጠው ሥልጠና መጨመሩ ያስደስተናል። በእነዚህ ማስተካከያዎች ሁሉ ላይ የይሖዋ እጅ እንዳለበት በግልጽ መመልከት ይቻላል። ይሖዋ፣ ድርጅቱም ሆነ በአሁኑ ጊዜም እንኳ ያለን መንፈሳዊ ገነት ከጊዜ ወደ ጊዜ ይበልጥ እየተዋበ እንዲሄድ አድርጓል!

ለመንፈሳዊው ገነት ውበት የምታበረክተው አስተዋጽኦ

18, 19. ለመንፈሳዊው ገነት ውበት አስተዋጽኦ የምናደርገው እንዴት ነው?

18 ይሖዋ ለመንፈሳዊ ገነታችን ውበት አስተዋጽኦ እንድናበረክት የፈቀደልን መሆኑ ትልቅ መብት ነው። የመንግሥቱን ምሥራች በቅንዓት በመስበክና ተጨማሪ ደቀ መዛሙርት በማፍራት መንፈሳዊውን ገነት ይበልጥ እናስውበዋለን። አንድ ሰው ራሱን ወስኖ ክርስቲያን እንዲሆን በረዳን ቁጥር የመንፈሳዊው ገነት ወሰን እንዲሰፋ እያደረግን ነው ሊባል ይችላል።—ኢሳ. 26:15፤ 54:2

19 ክርስቲያናዊ ባሕርያችንን በየጊዜው በማሻሻልም መንፈሳዊው ገነት ይበልጥ ማራኪ እንዲሆን ማድረግ እንችላለን። በዚህ መንገድ መንፈሳዊው ገነት ለሚመለከቱት ሰዎች ይበልጥ ውብ እንዲሆን እናደርጋለን። አብዛኛውን ጊዜ ሰዎች መጀመሪያ ወደ ድርጅቱ እንዲሳቡ እንዲሁም ወደ አምላክና ወደ ክርስቶስ እንዲቀርቡ የሚያነሳሳቸው ከመጽሐፍ ቅዱስ እውቀት ይበልጥ የእኛ ንጹሕና ሰላማዊ ምግባር ነው።

የመንፈሳዊውን ገነት ወሰን በማስፋቱ ሥራ መካፈል ትችላለህ (አንቀጽ 18, 19ን ተመልከት)

20. ከምሳሌ 14:35 ጋር በሚስማማ መንገድ ምኞታችን ምን ሊሆን ይገባል?

20 ይሖዋና ኢየሱስ በዛሬው ጊዜ ያለንን ውብ መንፈሳዊ ገነት ሲመለከቱ ምንኛ ይደሰቱ ይሆን! በአሁኑ ጊዜ መንፈሳዊ ገነታችንን ይበልጥ ከማስዋብ የምናገኘው ደስታ ወደፊት ምድርን ቃል በቃል ወደ ገነትነት ስንለውጥ ለምናገኘው እርካታ ቅምሻ ነው። በምሳሌ 14:35 ላይ የሚገኘውን “ንጉሥ አስተውሎ በሚሠራ አገልጋይ ደስ ይሰኛል” የሚለውን ሐሳብ እናስታውስ። እንግዲያው መንፈሳዊውን ገነት ለማስዋብ በምናደርገው ጥረት ምንጊዜም አስተውለን እንሥራ!