በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ለአምላክ መንግሥት ምንጊዜም ታማኝ ሁኑ

ለአምላክ መንግሥት ምንጊዜም ታማኝ ሁኑ

“የዓለም ክፍል አይደሉም።”—ዮሐ. 17:16

መዝሙሮች፦ 63, 129

1, 2. (ሀ) ክርስቲያኖች ለአምላክ ታማኝ መሆን የሚያሳስባቸው ለምንድን ነው? ይህስ ከገለልተኝነት ጋር የሚያያዘው እንዴት ነው? (በመግቢያው ላይ ያለውን ሥዕል ተመልከት።) (ለ) ብዙ ሰዎች ለየትኞቹ ነገሮች ታማኝነት ያሳያሉ? ይሁንና ይህ ምን ሊያስከትል ይችላል?

ክርስቲያኖች በጦርነት ጊዜ ብቻ ሳይሆን መቼም ቢሆን ታማኝ የመሆናቸውና የገለልተኝነት አቋማቸውን የመጠበቃቸው ጉዳይ ያሳስባቸዋል። ለምን? ምክንያቱም ራሳቸውን ለይሖዋ የወሰኑ ሁሉ እሱን ሊወዱት፣ ታማኝ ሊሆኑለትና ሊታዘዙት ቃል ገብተዋል። (1 ዮሐ. 5:3) የምንኖረው የትም ይሁን የት እንዲሁም አስተዳደጋችን፣ ዜግነታችን ወይም ባሕላችን ምንም ይሁን ምን በአምላክ የጽድቅ መሥፈርቶች ለመመራት እንፈልጋለን። ለይሖዋና ለመንግሥቱ ያለንን ታማኝነት ለሌላ ለማንኛውም ነገር ካለን ፍቅር እናስበልጣለን። (ማቴ. 6:33) ክርስቲያኖች እንዲህ ዓይነት ታማኝነት ለማሳየት በዚህ ዓለም ላይ በሚፈጠር በየትኛውም ግጭት ወይም ውዝግብ ውስጥ ከመግባት መቆጠብ አለባቸው።—ኢሳ. 2:4፤ ዮሐንስ 17:11, 15, 16ን አንብብ።

2 የይሖዋ ምሥክር ያልሆኑ ሰዎች ለአገራቸው፣ ለዘራቸው ወይም ለባሕላቸው አልፎ ተርፎም ለብሔራዊ የስፖርት ቡድናቸው ልዩ ታማኝነት ማሳየት እንዳለባቸው ይሰማቸው ይሆናል። እንዲህ ያለው ታማኝነት የውድድርና የፉክክር መንፈስ እንዲኖር ይባስ ብሎም ደም መፋሰስና የጅምላ ጭፍጨፋ እንዲከሰት ምክንያት ሆኗል። እኛም የማኅበረሰቡ ክፍል እንደመሆናችን መጠን ሰዎች እነዚህን አለመግባባቶች ለመፍታት የሚወስዱት እርምጃ ጥሩም ሆነ መጥፎ፣ በራሳችን ወይም በቤተሰባችን ላይ ተጽዕኖ ማሳደሩ አይቀርም። አምላክ የሰው ልጆችን የፈጠረው የፍትሕ ስሜት እንዲኖራቸው አድርጎ በመሆኑ ሰብዓዊ መንግሥታት የሚያደርጓቸው ውሳኔዎች ፍትሐዊና ትክክል እንዳልሆኑ ሲሰማን ቅር እንሰኝ ይሆናል። (ዘፍ. 1:27፤ ዘዳ. 32:4) እንዲህ ዓይነት ሁኔታ ሲያጋጥመን ምን እናደርጋለን? በዓለም ላይ ባሉ ውዝግቦች ረገድ ሳናስበው ከአንዱ ወገን እንቆም እንዲሁም በቀላሉ ውዝግቡ ውስጥ እንገባ ይሆናል።

3, 4. (ሀ) ክርስቲያኖች በዓለም ላይ ውዝግቦች ሲነሱ ገለልተኛ የሚሆኑት ለምንድን ነው? (ለ) በዚህ ርዕስ ውስጥ ምን እንመረምራለን?

3 ሰብዓዊውን ማኅበረሰብ የሚያስተዳድሩት መንግሥታት፣ ዜጎቻቸው በግጭቶች ውስጥ ከአንዱ ወገን እንዲቆሙ ለማድረግ ጫና ያሳድሩ ይሆናል። እውነተኛ ክርስቲያኖች ግን ከአንዱ ቡድን ጋር መወገን አይችሉም። በዚህ ዓለም ላይ በሚነሱ ፖለቲካዊ ውዝግቦች ውስጥ ጣልቃ አንገባም፤ የጦር መሣሪያም አንታጠቅም። (ማቴ. 26:52) እንዲሁም አንደኛውን የሰይጣን ዓለም ክፍል ከሌላው እንድናስበልጥ በሚደረግብን ግፊት አንሸነፍም። (2 ቆሮ. 2:11) የዓለም ክፍል ባለመሆናችን በዓለም ውዝግቦች ውስጥ ፈጽሞ አንገባም።ዮሐንስ 15:18, 19ን አንብብ።

4 ይሁንና ፍጹማን ባለመሆናችን አንዳንዶቻችን ቀድሞ የነበረንን መከፋፈል የሚፈጥር አመለካከት ለማስወገድ መታገል ያስፈልገን ይሆናል። (ኤር. 17:9፤ ኤፌ. 4:22-24) በመሆኑም እንዲህ ያሉ ዝንባሌዎችን ለማስወገድ የሚረዱንን አንዳንድ መሠረታዊ ሥርዓቶች በዚህ ርዕስ ላይ እንመረምራለን። በተጨማሪም ለአምላክ መንግሥት ታማኝ ለመሆን አእምሯችንንና ሕሊናችንን እንዴት ማሠልጠን እንደምንችል እንመለከታለን።

በዚህ ዓለም ጉዳዮች ከማንም ጋር የማንወግነው ለምንድን ነው?

5, 6. ኢየሱስ፣ በኖረበት አገር ውስጥ ከሚታየው ልዩነት ጋር በተያያዘ ምን አመለካከት ነበረው? ለምንስ?

5 አንድ ሁኔታ ሲያጋጥምህ ምን እርምጃ መውሰድ እንዳለብህ እርግጠኛ ካልሆንክ ‘ኢየሱስ ቢሆን ኖሮ ምን ያደርግ ነበር?’ ብለህ ራስህን መጠየቅህ ጠቃሚ ነው። ኢየሱስ የኖረበት አገር እንደ ይሁዳ፣ ገሊላና ሰማርያ ያሉ የተለያዩ ክልሎችን ያካተተ ነበር። በእነዚህ ክልሎች ውስጥ በሚኖሩት ሰዎች መካከል አለመግባባት እንደነበር የመጽሐፍ ቅዱስ ዘገባዎች በግልጽ ያሳያሉ። (ዮሐ. 4:9) በተጨማሪም በፈሪሳውያንና በሰዱቃውያን (ሥራ 23:6-9)፣ በሕዝቡና በቀረጥ ሰብሳቢዎች (ማቴ. 9:11) እንዲሁም በረቢዎች ትምህርት ቤት በተማሩና ባልተማሩ (ዮሐ. 7:49) መካከል መከፋፈል ነበር። በመጀመሪያው መቶ ዘመን እስራኤላውያንን የሚገዟቸው ሮማውያን ሲሆኑ ሕዝቡ የሮማውያንን አገዛዝ አምርሮ ይጠላ ነበር። ኢየሱስ ሃይማኖታዊ እውነትን ደግፎ የተናገረ ከመሆኑም ሌላ መዳን የሚጀምረው ከአይሁዳውያን መሆኑን ገልጿል፤ ያም ቢሆን ደቀ መዛሙርቱ በሕዝቡ መካከል ባለው ውዝግብ ውስጥ እንዲገቡ ፈጽሞ አላበረታታም። (ዮሐ. 4:22) ከዚህ ይልቅ ሰዎችን ሁሉ እንደ ባልንጀራቸው አድርገው እንዲወዱ አሳስቧቸዋል።—ሉቃስ 10:27

6 ኢየሱስ አብዛኞቹ አይሁዳውያን ለሌሎች የነበራቸውን ዓይነት መሠረተ ቢስ ጥላቻ ያላሳየው ለምንድን ነው? ምክንያቱም እሱም ሆነ አባቱ በዚህ ዓለም ላይ በሚነሱ ግጭቶች ረገድ ማንንም አይደግፉም። ይሖዋ በልጁ በኢየሱስ በኩል የመጀመሪያዎቹን ወንድና ሴት ሲፈጥር ዓላማው መላዋን ምድር እንዲሞሉ ነበር። (ዘፍ. 1:27, 28) አምላክ ሰዎችን የፈጠራቸው የተለያዩ ዘሮችን ማስገኘት እንዲችሉ አድርጎ ነው። ይሖዋም ሆነ ኢየሱስ አንድን ዘር፣ ብሔር ወይም ቋንቋ ከሌላው አስበልጠው አይመለከቱም። (ሥራ 10:34, 35፤ ራእይ 7:9, 13, 14) እኛም የእነሱን ፍጹም ምሳሌ መከተል ይኖርብናል።—ማቴ. 5:43-48

7, 8. (ሀ) ክርስቲያኖች ወገን መያዝ የሚኖርባቸው ከየትኛው ጉዳይ ጋር በተያያዘ ነው? (ለ) ክርስቲያኖች ለማኅበራዊና ለፖለቲካዊ ችግሮች እልባት ከማስገኘት ጋር በተያያዘ ምን ማስታወስ ይኖርባቸዋል?

7 ከአንድ ጉዳይ ይኸውም የይሖዋን አጽናፈ ዓለማዊ ሉዓላዊነት ከመደገፍ ጋር በተያያዘ ግን ከአንደኛው ወገን ጎን መቆም ይኖርብናል። በዚህ ረገድ መጀመሪያ ውዝግብ የተፈጠረው ሰይጣን በኤደን የይሖዋን አገዛዝ በተገዳደረበት ወቅት ነው። ከዚያ ወዲህ ሁሉም ሰው፣ ‘አምላክ ነገሮችን የሚያከናውንበት መንገድ ከሰይጣን የላቀ ነው ወይስ የሰይጣን መንገድ ይሻላል?’ በሚለው ጉዳይ ረገድ አቋም መውሰድ አስፈልጎታል። በራስህ መንገድ ነገሮችን ከማከናወን ይልቅ ከይሖዋ ጎን በመቆም የእሱን ሕግጋትና መሥፈርቶች እየታዘዝክ እንደሆነ በሐቀኝነት መናገር ትችላለህ? በሰው ልጆች ላይ ለሚደርሱ መከራዎች ብቸኛው መፍትሔ የእሱ መንግሥት እንደሆነ ታምናለህ? ወይስ የሰው ዘር ራሱን ማስተዳደር እንደሚችል ይሰማሃል?—ዘፍ. 3:4, 5

8 ለእነዚህ ጥያቄዎች የምትሰጠው መልስ፣ ሰዎች አከራካሪ በሆኑ ጉዳዮች ረገድ አመለካከትህን ሲጠይቁህ ከምትሰጠው መልስ ጋር በቀጥታ የተቆራኘ ነው። ፖለቲከኞችና የለውጥ አራማጆች በሰዎች መካከል መከፋፈል ለሚፈጥሩ ጉዳዮች እልባት ለማስገኘት ሲጥሩ ቆይተዋል። ይህን የሚያደርጉት በቅን ልቦና ተነሳስተው ሊሆን ይችላል። ይሁንና ክርስቲያኖች፣ የሰው ልጆችን ችግሮች ሊያስወግድና እውነተኛ ፍትሕ ሊያሰፍን የሚችለው የአምላክ መንግሥት ብቻ እንደሆነ ያውቃሉ። በመሆኑም ነገሩን ለይሖዋ መተው ይኖርብናል። ደግሞስ እያንዳንዱ ክርስቲያን የተሻለ እንደሆነ የሚያስበውን የመፍትሔ ሐሳብ የሚያራምድ ቢሆን ብዙም ሳይቆይ በጉባኤዎቻችን ውስጥ መከፋፈል አይፈጠርም?

9. በመጀመሪያው መቶ ዘመን በቆሮንቶስ ጉባኤ ውስጥ ምን ችግር ተነስቶ ነበር? ሐዋርያው ጳውሎስ ምን የመፍትሔ ሐሳብ አቅርቧል?

9 በመጀመሪያው መቶ ዘመን የነበሩት ክርስቲያኖች በጉባኤው ውስጥ መከፋፈል የሚፈጥር አንድ ጉዳይ በተነሳበት ጊዜ ምን እንዳደረጉ እንመልከት። በቆሮንቶስ የሚገኙ አንዳንድ ክርስቲያኖች “‘እኔ የጳውሎስ ነኝ፣’ ‘እኔ ግን የአጵሎስ ነኝ፣’ ‘እኔ ደግሞ የኬፋ ነኝ፣’ ‘እኔ የክርስቶስ ነኝ’” ይሉ ነበር። መከፋፈል እንዲፈጠር መንስኤ የሆነው ምንም ይሁን ምን፣ ክፍፍል መፈጠሩ ሐዋርያው ጳውሎስን አስቆጥቶታል። “ታዲያ የክርስቶስ ጉባኤ ተከፋፍሏል ማለት ነው?” በማለት ጠየቀ። እንዲህ ያለውን ክፍፍል የሚፈጥር አመለካከት ለማስወገድ መፍትሔው ምንድን ነው? ጳውሎስ ለክርስቲያኖች የሚከተለውን ምክር ሰጥቷቸዋል፦ “እንግዲህ ወንድሞች፣ ሁላችሁም ንግግራችሁ አንድ እንዲሆንና በመካከላችሁ መከፋፈል እንዳይኖር፣ ከዚህ ይልቅ በአስተሳሰብም ሆነ በዓላማ ፍጹም አንድነት እንዲኖራችሁ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አጥብቄ አሳስባችኋለሁ።” ዛሬም ቢሆን በክርስቲያን ጉባኤ ውስጥ ምንም ዓይነት መከፋፈል ሊኖር አይገባም።—1 ቆሮ. 1:10-13፤ ሮም 16:17, 18ን አንብብ።

10. አንድ ክርስቲያን በዓለም ላይ ባሉ ውዝግቦች ረገድ ገለልተኛ መሆን እንዳለበት ሐዋርያው ጳውሎስ በምሳሌ ያስረዳው እንዴት ነው?

10 ጳውሎስ፣ ቅቡዓን ክርስቲያኖች በምድር ባሉ ነገሮች ላይ ከማተኮር ይልቅ ዜግነታቸው በሰማይ መሆኑን እንዲያስታውሱ አሳስቧቸዋል። (ፊልጵ. 3:17-20) * እነዚህ ክርስቲያኖች ክርስቶስን ተክተው የሚሠሩ አምባሳደሮች ናቸው። አምባሳደሮች ደግሞ በተመደቡባቸው አገራት ጉዳዮች ውስጥ ጣልቃ አይገቡም። ታማኝ መሆን ያለባቸው ለሌላ መንግሥት ነው። (2 ቆሮ. 5:20) ምድራዊ ተስፋ ያላቸው ክርስቲያኖችም የአምላክ መንግሥት ተገዢዎች በመሆናቸው በዚህ ዓለም ላይ ባሉ ውዝግቦች ረገድ ከማንም ወገን አለመቆማቸው ተገቢ ነው።

ለይሖዋ ታማኝ ለመሆን ራሳችሁን አሠልጥኑ

11, 12. (ሀ) አንድ ክርስቲያን ለአምላክ መንግሥት ታማኝ መሆን ፈታኝ እንዲሆንበት የሚያደርገው ምን ሊሆን ይችላል? (ለ) አንዲት ክርስቲያን ምን አጋጠማት? ምንስ አደረገች?

11 በብዙ የዓለም ክፍሎች ያሉ ማኅበረሰቦች እርስ በርስ የተሳሰሩ ናቸው። እንዲሁም የጋራ የሆነ ታሪክ፣ ባሕልና ቋንቋ አላቸው፤ በዚህም በጣም ይኮራሉ። እንዲህ ባሉ ማኅበረሰቦች ውስጥ ክርስቲያኖች ከገለልተኝነት ጋር የተያያዘ ጉዳይ ሲነሳ ተገቢውን ምላሽ ለመስጠት አእምሯቸውንና ሕሊናቸውን ማሠልጠን ይኖርባቸዋል። ይህን ማድረግ የሚችሉት እንዴት ነው?

12 በቀድሞዋ ዩጎዝላቪያ ክልል ውስጥ የምትኖረውን ሚሪዬታን * እንደ ምሳሌ እንውሰድ። ያደገችው ሰርቦችን በሚጠላ ማኅበረሰብ ውስጥ ነው። ይሖዋ የማያዳላ አምላክ እንደሆነና በዘር ልዩነት ምክንያት ለሚፈጠሩ ችግሮች ተጠያቂው ሰይጣን መሆኑን ስታውቅ ብሔራዊ ስሜትን ከውስጧ ለማጥፋት ትግል ማድረግ ጀመረች። በአካባቢዋ ከዘር ጋር የተያያዘ ግጭት ሲቀሰቀስ ግን ቀደም ሲል ለሰርቦች የነበራት ጥላቻ ማገርሸት ጀመረ፤ በመሆኑም ለሰርቦች መስበክ ከበዳት። ይሁንና እንዲህ ያለው ተገቢ ያልሆነ ስሜት በራሱ እንደሚጠፋ በማሰብ እጇን አጣጥፋ አልተቀመጠችም። ይሖዋ ይህንን ችግሯን ለመወጣት ብቻ ሳይሆን አገልግሎቷን ለማስፋትና ለአቅኚነት ብቃቱን ለማሟላት እንዲረዳት በጸሎት ለመነችው። ሚሪዬታ እንዲህ ብላለች፦ “ከሁሉ በላይ የረዳኝ በአገልግሎቱ ላይ ትኩረት ማድረጌ ነው። በአገልግሎት ላይ የይሖዋን ፍቅር ለማንጸባረቅ እጥራለሁ፤ ይህም አሉታዊ ስሜትን ለማስወገድ ረድቶኛል።”

13. (ሀ) አንዲት የይሖዋ ምሥክር እንድትከፋ ያደረጋት ሁኔታ ምንድን ነው? ይሁንና ምን አደረገች? (ለ) ቶይላ ካጋጠማት ነገር ምን እንማራለን?

13 የቶይላን ምሳሌ ደግሞ እንመልከት። ከሜክሲኮ የመጣችው ቶይላ፣ በአውሮፓ ውስጥ የሚገኝ አንድ ጉባኤ አባል ናት። ከላቲን አሜሪካ አገራት የመጡ አንዳንድ የጉባኤው አባላት የእሷን አገርና ባሕል አልፎ ተርፎም የአገሯን ሙዚቃ በተመለከተ ቅር የሚያሰኝና ዝቅ የሚያደርግ ሐሳብ ሲሰጡ ሰማች። አንተ ብትሆን ኖሮ ምን ታደርግ ነበር? ቶይላ ይህን ስትሰማ መከፋቷ አያስገርምም። ሆኖም ቶይላ በልቧ ውስጥ የሚፈጠሩ አሉታዊ ስሜቶችን ለማስወገድ እንዲረዳት ይሖዋን ጠየቀች፤ ይህም የሚያስመሰግናት ነው። እኛም አንዳንድ ወንድሞችና እህቶች ተመሳሳይ ስሜት እንደሚያስቸግራቸው ማስታወስ ይኖርብናል። የሌሎችን አገር ወይም ባሕል ዝቅ የሚያደርግ ነገር በመናገር ወይም በማድረግ በወንድሞቻችንም ሆነ በሌሎች ዘንድ መከፋፈል መፍጠር አንፈልግም፤ በሌላ በኩል ደግሞ ሌሎች እንዲህ ዓይነት ነገር ሲናገሩ ብንሰማም ቅር መሰኘት አይኖርብንም።—ሮም 14:19፤ 2 ቆሮ. 6:3

14. ክርስቲያኖች በታማኝነት ረገድ ለሚነሱ ጥያቄዎች መልስ ለመስጠት አእምሯቸውንና ሕሊናቸውን ማሠልጠን የሚችሉት እንዴት ነው?

14 አስተዳደግህ አሊያም የምትኖርበት አካባቢ ለአገርህ ወይም ለብሔርህ የተለየ ታማኝነት እንዲያድርብህ አድርጎሃል? እንዲህ ዓይነቱ ስሜት አሁንም በውስጥህ አለ? ክርስቲያኖች፣ ብሔራዊ ስሜት ለሌሎች ያላቸውን አመለካከት እንዲያዛባው መፍቀድ አይኖርባቸውም። ይሁንና ከአንተ የተለየ ዜግነት፣ ባሕል፣ ቋንቋ ወይም ዘር ላላቸው ሰዎች አሉታዊ አመለካከት እንዳለህ ብትገነዘብ ምን ማድረግ ያስፈልግሃል? ይሖዋ፣ ስለ ብሔራዊ ስሜትና ስለ ጭፍን ጥላቻ ያለውን አመለካከት ቆም ብለህ ማሰብህ ጠቃሚ ነው። እነዚህ ነገሮች በግል ጥናት ወይም በቤተሰብ አምልኮ ወቅት ምርምር ልታደርግባቸው የሚገቡ ጉዳዮች ናቸው። በተጨማሪም ይሖዋ በእነዚህ ጉዳዮች ረገድ የእሱ ዓይነት አመለካከት ለማዳበር እንዲረዳህ በጸሎት ለምነው።ሮም 12:2ን አንብብ።

ለይሖዋ ታማኝ ለመሆን ከፈለግን ዛቻ ቢሰነዘርብንም መጽናት ይኖርብናል (አንቀጽ 15, 16ን ተመልከት)

15, 16. (ሀ) ለአምላክ ታማኝ ለመሆን ጥረት ስናደርግ ሌሎች ምን ምላሽ እንደሚሰጡ መጠበቅ ይኖርብናል? (ለ) ወላጆች፣ ልጆቻቸው ክርስቲያናዊ ታማኝነታቸውን እንዲጠብቁ ሊረዷቸው የሚችሉት እንዴት ነው?

15 ይዋል ይደር እንጂ ሁሉም የይሖዋ አገልጋዮች በሕሊናቸው ምክንያት በአካባቢያቸው ካሉ ሰዎች ለምሳሌ ከሥራ ባልደረቦቻቸው፣ አብረዋቸው ከሚማሩ ሰዎች፣ ከጎረቤቶቻቸው፣ ከዘመዶቻቸው ወይም ከሌሎች የተለየ አቋም መያዝ የሚያስፈልጋቸው ሁኔታ መፈጠሩ አይቀርም። (1 ጴጥ. 2:19) በዚህ ጊዜ መለየታችን የግድ ነው! ዓለም በአቋማችን የተነሳ ቢጠላን መገረም አይኖርብንም፤ ምክንያቱም ኢየሱስ ይህ እንደሚሆን አስጠንቅቆናል። አብዛኞቹ ተቃዋሚዎች ከክርስቲያናዊ ገለልተኝነት ጋር የተያያዙት ጉዳዮች ምን ያህል ትልቅ ቦታ እንዳላቸው አይገነዘቡም። እኛ ግን ትልቅ ቦታ የምንሰጠው ጉዳይ ነው።

16 ለይሖዋ ታማኝ ለመሆን ከፈለግን ዛቻ ቢሰነዘርብንም መጽናት ይኖርብናል። (ዳን. 3:16-18) የሰው ፍርሃት በሁሉም ዕድሜ ባሉ ሰዎች ላይ ተጽዕኖ የሚያሳድር ቢሆንም በተለይ ታዳጊዎች ከሌሎች የተለዩ መሆን ይከብዳቸው ይሆናል። ልጆቻችሁ ለባንዲራ ሰላምታ ከመስጠት ወይም ከብሔራዊ በዓላት ጋር በተያያዘ አቋማቸውን የሚፈትን ሁኔታ እያጋጠማቸው ከሆነ እርዳታ ልታደርጉላቸው ይገባል። ልጆቻችሁ ጉዳዩ ምን ያህል ትልቅ ቦታ የሚሰጠው እንደሆነ እንዲገነዘቡ በቤተሰብ አምልኳችሁ ወቅት ለመርዳት ጥረት አድርጉ፤ ይህም የሚያጋጥማቸውን ፈተና በድፍረት ለመወጣት ያስችላቸዋል። የሚያምኑበትን ነገር በግልጽና አክብሮት በሚንጸባረቅበት መንገድ እንዲናገሩ እርዷቸው። (ሮም 1:16) ለልጆቻችሁ ተጨማሪ ድጋፍ ለመስጠት ደግሞ አስፈላጊ ከሆነ ከመምህሮቻቸው ጋር ስለ እነዚህ ጉዳዮች ተነጋገሩ።

ይሖዋ የፈጠራቸውን ሰዎች ሁሉ አክብሩ!

17. የትኛው አመለካከት ሊኖረን አይገባም? ለምንስ?

17 ያደግንበትን አገር፣ ባሕሉን፣ ቋንቋውን እንዲሁም ምግቡን በተወሰነ መጠን ብንወደው የሚያስገርም አይደለም። ይሁንና “የእኔ ከሁሉም ይበልጣል” የሚል ዓይነት አመለካከት ፈጽሞ ሊኖረን አይገባም። ይሖዋ እኛን ለማስደሰት ሲል እያንዳንዱን ነገር የፈጠረው ብዙ ዓይነቶች እንዲኖሩት አድርጎ ነው። (መዝ. 104:24፤ ራእይ 4:11) ታዲያ አንዱ ነገር ከሌላው የላቀ እንደሆነ ለማሰብ ምን ምክንያት አለን?

18. የይሖዋን አመለካከት ማዳበር በረከት የሚያስገኘው እንዴት ነው?

18 አምላክ ሁሉም ዓይነት ሰዎች የእውነትን ትክክለኛ እውቀት እንዲያገኙና ለዘላለም መኖር እንዲችሉ ይፈልጋል። (ዮሐ. 3:16፤ 1 ጢሞ. 2:3, 4) ተቀባይነት ያላቸው የተለያዩ አመለካከቶችን ለማስተናገድ አእምሯችንን ክፍት ማድረጋችን ሕይወታችንን አስደሳች የሚያደርገው ከመሆኑም ሌላ ክርስቲያናዊ አንድነታችንን ለመጠበቅ ያስችለናል። ለይሖዋ ያለንን ታማኝነት ጠብቀን ለመኖር በዓለም ላይ ባሉ ውዝግቦች ውስጥ ከመግባት መቆጠብ ይኖርብናል። በወገንተኝነት ላይ የተመሠረተ ታማኝነት በእኛ መካከል ሊኖር አይገባም። በሰይጣን ዓለም ውስጥ ከነገሠው የሚከፋፍል እንዲሁም ኩራትና ፉክክር የሚንጸባረቅበት አመለካከት ይሖዋ ስለገላገለን ምንኛ አመስጋኞች ነን! እንግዲያው መዝሙራዊው እንደሚከተለው በማለት የገለጸው ዓይነት ሰላማዊ አመለካከት ለማዳበር ቁርጥ ውሳኔ እናድርግ፦ “እነሆ፣ ወንድሞች በአንድነት አብረው ቢኖሩ ምንኛ መልካም ነው! ምንኛስ ደስ ያሰኛል!”—መዝ. 133:1

^ አን.10 ፊልጵስዩስ በሮም አገዛዝ ሥር ነበረች። በዚያ የሚገኘው ጉባኤ አንዳንድ አባላት የሮም ዜግነት የነበራቸው ይመስላል፤ ይህ ደግሞ ሌሎች ወንድሞቻቸው የሌሏቸውን አንዳንድ መብቶች ሊያስገኝላቸው ይችላል።

^ አን.12 አንዳንዶቹ ስሞች ተቀይረዋል።