በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የአምላክን መንግሥት ለመደገፍ አሁኑኑ እርምጃ ውሰድ!

የአምላክን መንግሥት ለመደገፍ አሁኑኑ እርምጃ ውሰድ!

የምትኖርበት አካባቢ በከባድ አውሎ ነፋስ ሊመታ እንደሆነ አወቅህ እንበል። የመንግሥት አካላት “በአፋጣኝ አካባቢውን ለቃችሁ ውጡ!” የሚል አስቸኳይ የማስጠንቀቂያ መልእክት እያሰሙ ነው። በዚህ ጊዜ ምን ታደርጋለህ? አውሎ ነፋሱ ወደማይደርስበት ቦታ እንደምትሸሽ የታወቀ ነው።

ኢየሱስ “ታላቅ መከራ” ብሎ የጠራው ምሳሌያዊ አውሎ ነፋስ በቅርቡ ምድርን ይመታል። (ማቴዎስ 24:21) ወደ ሌላ አካባቢ በመሸሽ ከዚህ መከራ ልናመልጥ አንችልም። ሆኖም ራሳችንን ለመጠበቅ ማድረግ የምንችለው ነገር አለ። ይህ ምንድን ነው?

ኢየሱስ ክርስቶስ በተራራው ስብከቱ ላይ “ከሁሉ አስቀድማችሁ የአምላክን መንግሥትና ጽድቅ ፈልጉ” የሚል መመሪያ ሰጥቷል። (ማቴዎስ 6:33) ይህን ማድረግ የምንችለው እንዴት ነው?

ከሁሉ አስቀድመን የአምላክን መንግሥት መፈለግ። በሕይወታችን ውስጥ የአምላክን መንግሥት ከምንም ነገር በላይ ማስቀደም አለብን። (ማቴዎስ 6:25, 32, 33) ለአምላክ መንግሥት እንዲህ ያለ ትልቅ ቦታ ልንሰጥ የሚገባው ለምንድን ነው? ምክንያቱም በሰው ዘር ላይ እየደረሱ ያሉት ችግሮች በጣም ከባድ ስለሆኑ በሰዎች አቅም ሊፈቱ አይችሉም። ይህን ሊያደርግ የሚችለው የአምላክ መንግሥት ብቻ ነው።

ጽድቁን መፈለግ። በጽድቅ ላይ በተመሠረቱት የአምላክ ሕጎችና መመሪያዎች መሠረት ሕይወታችንን ለመምራት የቻልነውን ሁሉ ልናደርግ ይገባል። ለምን? ምክንያቱም ትክክልና ስህተት የሆነውን ነገር በራሳችን ለመወሰን ከሞከርን ውጤቱ አስከፊ ይሆናል። (ምሳሌ 16:25) በሌላ በኩል ግን በአምላክ መሥፈርቶች የምንመራ ከሆነ አምላክን የምናስደስት ከመሆኑም ሌላ ለራሳችን እንጠቀማለን።—ኢሳይያስ 48:17, 18

ከሁሉ አስቀድማችሁ የአምላክን መንግሥትና ጽድቅ መፈለጋችሁን ቀጥሉ። ኢየሱስ አንዳንዶች ብዙ ሀብት ማካበት አስተማማኝ ሕይወት ለመምራት እንደሚያስችል በማሰብ ትኩረታቸው ሊከፋፈል እንደሚችል አስጠንቅቋል። ሌሎች ደግሞ በኑሮ ጭንቀት ከመዋጣቸው የተነሳ የአምላክን መንግሥት ለመፈለግ ጊዜ ሊያጡ ይችላሉ።—ማቴዎስ 6:19-21, 25-32

ይሁንና ኢየሱስ የአምላክን መንግሥት የሚደግፉ ሰዎች በዛሬው ጊዜ ለኑሮ የሚያስፈልጋቸው ነገር እንደሚሟላላቸውና ወደፊት ደግሞ የተትረፈረፈ በረከት እንደሚያገኙ ቃል ገብቷል።—ማቴዎስ 6:33

በመጀመሪያው መቶ ዘመን ይኖሩ የነበሩት የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ከሁሉ አስቀድመው የአምላክን መንግሥትና ጽድቅ የፈለጉ ቢሆንም በሕይወት ዘመናቸው መከራና ሥቃይ ተወግዶ የማየት አጋጣሚ አላገኙም። ሆኖም የአምላክን መንግሥትና ጽድቅ ማስቀደማቸው ጥበቃ ሆኖላቸዋል። እንዴት?

የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት በአምላክ የጽድቅ መሥፈርቶች ይመሩ የነበረ ሲሆን ይህም የአምላክን ሕግ ችላ የሚሉ ሰዎች ከሚደርስባቸው መከራ እንዲያመልጡ ረድቷቸዋል። የአምላክ መንግሥት እንደሚመጣ ያላቸው ጠንካራ እምነት እጅግ ከባድ የሚባሉ ችግሮችን እንኳ በጽናት እንዲወጡ አስችሏቸዋል። በተጨማሪም አምላክ ሁኔታውን መወጣት እንዲችሉ “ከሰብዓዊ ኃይል በላይ [የሆነ] ኃይል” ሰጥቷቸዋል።—2 ቆሮንቶስ 4:7-9

አንተስ ከሁሉ አስቀድመህ የአምላክን መንግሥት ትፈልግ ይሆን?

በመጀመሪያው መቶ ዘመን የነበሩ ክርስቲያኖች ኢየሱስ ከሁሉ አስቀድመው የአምላክን መንግሥት እንዲፈልጉ የሰጣቸውን መመሪያ ታዘዋል። በዚያ ዘመን በነበረው ዓለም በሙሉ የአምላክን መንግሥት ምሥራች ሰብከዋል። (ቆላስይስ 1:23) በዛሬው ጊዜ እንዲህ እያደረጉ ያሉ ሰዎች አሉ?

አዎ! የይሖዋ ምሥክሮች የአምላክ መንግሥት አሁን ያለውን ሥርዓት ሊያጠፋ የቀረው ጊዜ አጭር እንደሆነ ይገነዘባሉ። በመሆኑም ኢየሱስ እንደሚከተለው በማለት የተናገረለትን ሥራ ዳር ለማድረስ የቻሉትን ሁሉ እያደረጉ ነው፦ “ይህ የመንግሥቱ ምሥራች ለብሔራት ሁሉ ምሥክር እንዲሆን በመላው ምድር ይሰበካል፤ ከዚያም መጨረሻው ይመጣል።”—ማቴዎስ 24:14

ለምሥራቹ ምን ምላሽ ትሰጥ ይሆን? በመጀመሪያው መቶ ዘመን፣ ቤርያ በተባለች የመቄዶንያ ከተማ ይኖሩ የነበሩትን ሰዎች ምሳሌ እንድትከተል እናበረታታሃለን። እነዚህ ሰዎች ሐዋርያው ጳውሎስ ስለ አምላክ መንግሥት የሚገልጸውን ምሥራች ሲነግራቸው መልእክቱን “በታላቅ ጉጉት” ተቀብለዋል። ከዚያም የሰሙት ነገር ትክክል መሆኑን ለማረጋገጥ ‘ቅዱሳን መጻሕፍትን በሚገባ ይመረምሩ’ የነበረ ከመሆኑም ሌላ የተማሩትን ነገር ተግባር ላይ ያውሉ ነበር።—የሐዋርያት ሥራ 17:11, 12

አንተም እንዲህ ማድረግ ትችላለህ። ከሁሉ አስቀድመህ የአምላክን መንግሥትና ጽድቅ መፈለግህ በዛሬው ጊዜ ጥበቃ ይሆንልሃል፤ ወደፊት ደግሞ ዘላቂ የሆነ ሰላምና ደህንነት ያስገኝልሃል።