በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የአንባቢያን ጥያቄዎች

የአንባቢያን ጥያቄዎች

ምሳሌ 24:16 “ጻድቅ ሰባት ጊዜ ቢወድቅ እንኳ መልሶ ይነሳልና፤ ክፉ ሰው ግን በሚደርስበት መከራ ይሰናከላል” ይላል። ይህ ጥቅስ አንድ ሰው በተደጋጋሚ በኃጢአት ቢወድቅም አምላክ ይቅር እንደሚለው የሚጠቁም ነው?

ይህ ጥቅስ የሚናገረው ስለዚህ ጉዳይ አይደለም። ከዚህ ይልቅ “ጻድቅ . . . ቢወድቅ” ሲል መከራ ወይም ችግር በተደጋጋሚ ቢያጋጥመው እንደማለት ሲሆን “ይነሳል” የሚለው ደግሞ መከራውን እንደሚወጣው የሚያሳይ ነው።

በጥቅሱ ዙሪያ ያለውን ሐሳብ ተመልከት፦ “በጻድቁ ቤት ላይ በክፋት አትሸምቅ፤ ማረፊያ ቦታውንም አታፍርስበት። ጻድቅ ሰባት ጊዜ ቢወድቅ እንኳ መልሶ ይነሳልና፤ ክፉ ሰው ግን በሚደርስበት መከራ ይሰናከላል። ጠላትህ ሲወድቅ ሐሴት አታድርግ፤ ሲሰናከልም ልብህ ደስ አይበለው።”—ምሳሌ 24:15-17

አንዳንዶች በቁጥር 16 ላይ ያለው ሐሳብ፣ በኃጢአት ቢወድቅም ንስሐ ገብቶ ስለሚመለስ ሰው የሚናገር እንደሆነ ይገልጻሉ። ሁለት እንግሊዛውያን ቀሳውስት፣ ‘ጥንትም ሆነ ዛሬ ያሉ ሰባኪዎች ይህን ጥቅስ በዚህ መንገድ ብዙ ጊዜ እንደተጠቀሙበት’ ጽፈዋል። ቀሳውስቱ እንዲህ ያለው አመለካከት ምን ትርጉም እንዳለው ሲገልጹ እንዲህ ብለዋል፦ “አንድ ጥሩ ሰው . . . በከባድ ኃጢአት ቢወድቅም ለአምላክ ያለውን ፍቅር አያጣም፤ በመሆኑም ኃጢአት በሠራ ቁጥር ንስሐ በመግባት ከወደቀበት ይነሳል።” ከኃጢአት ዝንባሌው ጋር መታገል የማይፈልግ ሰው እንዲህ ያለው አመለካከት ሊማርከው ይችላል። እንዲህ ያለው ሰው በተደጋጋሚ ኃጢአት ቢሠራም አምላክ ምንጊዜም ይቅር እንደሚለው ያስብ ይሆናል።

ይሁንና የቁጥር 16 ትርጉም ይህ አይደለም።

በቁጥር 16 እና 17 ላይ “ቢወድቅ” እና “ሲወድቅ” ተብሎ የተተረጎመው የዕብራይስጥ ቃል በተለያዩ መንገዶች ሊሠራበት ይችላል። ቃሉ፣ ቃል በቃል መውደቅን ሊያመለክት ይችላል፤ ለምሳሌ ‘በሬ መንገድ ላይ ወደቀ፣’ ‘አንድ ሰው ከጣሪያ ላይ ወደቀ’ ወይም ‘ጠጠር ወደ ምድር ወደቀ’ ሊባል ይችላል። (ዘዳ. 22:4, 8፤ አሞጽ 9:9) ይህ ቃል ምሳሌያዊ በሆነ መንገድም ሊሠራበት ይችላል፤ ለምሳሌ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ “ይሖዋ በሰው መንገድ ደስ ሲሰኝ፣ አካሄዱን ይመራለታል። ቢወድቅም እንኳ አይዘረርም፤ ይሖዋ እጁን ይዞ ይደግፈዋልና።”—መዝ. 37:23, 24፤ ምሳሌ 11:5፤ 13:17

ይሁን እንጂ ፕሮፌሰር ኤድዋርድ ሄይስ ፕለምትረ እንደተናገሩት “[“መውደቅ”] ተብሎ የተተረጎመው የዕብራይስጥ ቃል በኃጢአት መውደቅን ለማመልከት ጨርሶ ተሠርቶበት አያውቅም።” አንድ ሌላ ምሁር ቁጥር 16⁠ን በሚከተለው መንገድ ጠቅለል አድርገው አስቀምጠውታል፦ “የአምላክን ሕዝቦች መበደል፣ ከንቱና ጥቅም የሌለው ነገር ነው፤ ምክንያቱም መልሰው መነሳታቸው አይቀርም። ክፉዎች ግን ወድቀው ይቀራሉ!”

ከዚህ አንጻር ምሳሌ 24:16 ‘መውደቅ’ ሲል የሚያመለክተው፣ አንድ ሰው በኃጢአት መውደቁን ሳይሆን ከባድ ችግሮች ወይም መከራዎች በተደጋጋሚ የደረሱበት መሆኑን ነው። በዚህ ክፉ ሥርዓት ውስጥ ጻድቅ ሰው፣ የጤና እክል ወይም ሌሎች ችግሮች ሊያጋጥሙት ይችላሉ። አልፎ ተርፎም መንግሥት ከባድ ስደት ሊያደርስበት ይችላል። ሆኖም አምላክ እንደሚደግፈውና ችግሩን ለመቋቋም ብሎም ለመወጣት እንደሚረዳው መተማመን ይችላል። አንተስ የአምላክ አገልጋዮች፣ የኋላ ኋላ ነገሮች መልካም እንደሚሆኑላቸው ብዙ ጊዜ አልተመለከትክም? ይህ የሆነው ለምንድን ነው? መጽሐፍ ቅዱስ ምክንያቱን ሲነግረን “ይሖዋ ሊወድቁ የተቃረቡትን ሁሉ ይደግፋል፤ ያጎነበሱትንም ሁሉ ቀና ያደርጋል” ይላል።—መዝ. 41:1-3፤ 145:14-19

“ጻድቅ” ሰው፣ ሌሎች መከራ እየደረሰባቸው መሆኑ አያስደስተውም። ከዚህ ይልቅ “እውነተኛውን አምላክ የሚፈሩ ሰዎች አምላክን በመፍራታቸው የኋላ ኋላ መልካም እንደሚሆንላቸው” በማወቁ ይጽናናል።—መክ. 8:11-13፤ ኢዮብ 31:3-6፤ መዝ. 27:5, 6