በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ስለ ወደፊቱ ጊዜ አስተማማኝ መመሪያ ማግኘት ይቻላል?

ስለ ወደፊቱ ጊዜ አስተማማኝ መመሪያ ማግኘት ይቻላል?

ቀደም ባሉት ርዕሶች ላይ እንደተመለከትነው ሰዎች በዕድል በማመን፣ ከፍተኛ ትምህርት በመከታተል፣ ሀብት በማሳደድ፣ ጥሩ ሰው ለመሆን በመጣርና እንዲህ የመሳሰሉ ነገሮችን በማድረግ የወደፊት ሕይወታቸውን አስተማማኝ ለማድረግ ይሞክራሉ። ሆኖም እነዚህን አማራጮች በመጠቀም የወደፊት ሕይወትን አስተማማኝ ለማድረግ መሞከር የተሳሳተ ካርታ ተጠቅሞ ያሰቡበት ቦታ ለመድረስ እንደመሞከር ነው። ይህ ሲባል ታዲያ ስለ ወደፊቱ ጊዜ አስተማማኝ መመሪያ ማግኘት አይቻልም ማለት ነው? በፍጹም!

ከሁሉ የተሻለ መመሪያ የምናገኘው ከማን ነው?

አብዛኛውን ጊዜ ውሳኔ ስናደርግ በዕድሜም ሆነ በተሞክሮ ከእኛ የሚበልጥን ሰው እናማክራለን። ከወደፊቱ ጊዜ ጋር በተያያዘም አስተማማኝ መመሪያ ሊሰጠን የሚችል አካል አለ፤ ይህ አካል በዕድሜም ሆነ በጥበብ ከእኛ በእጅጉ የላቀ ነው። እሱ የሰጠንን ምክር የምናገኘው ጥንታዊ በሆኑ ቅዱሳን መጻሕፍት ውስጥ ነው። እነዚህ መጻሕፍት መጻፍ የጀመሩት ከ3,500 ዓመታት ገደማ በፊት ነው፤ የመጻሕፍቱ ስብስብ መጽሐፍ ቅዱስ ተብሎ ይጠራል።

በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ እምነት መጣል የምትችለው ለምንድን ነው? ምክንያቱም መጽሐፍ ቅዱስን ያጻፈው በጽንፈ ዓለም ውስጥ በዕድሜም ሆነ በጥበብ ተወዳዳሪ የሌለው አካል ነው። “ከዘመናት በፊት የነበረ” እንዲሁም “ከዘላለም እስከ ዘላለም” የሚኖር እንደሆነ ተገልጿል። (ዳንኤል 7:9፤ መዝሙር 90:2) ‘ሰማያትን የፈጠረው፣ እውነተኛ የሆነው አምላክና ምድርን የሠራት’ እሱ ነው። (ኢሳይያስ 45:18) ስሙ ይሖዋ እንደሆነ ተናግሯል።—መዝሙር 83:18

መጽሐፍ ቅዱስ የሰው ዘር ሁሉ ፈጣሪ የሆነው አምላክ ያጻፈው መጽሐፍ ስለሆነ አንዱን ባሕል ወይም ዘር ከሌላው አያበላልጥም። በውስጡ የያዘው ምክር ዘመን የማይሽረው ሲሆን በሁሉም የዓለም ክፍሎች የሚኖሩ ሰዎችን ይጠቅማል። ከየትኛውም መጽሐፍ ይበልጥ በብዙ ቋንቋዎች የተተረጎመና በስፋት የተሰራጨ መጽሐፍ ነው። * ይህ ሲባል ደግሞ በየትኛውም የዓለም ክፍል የሚኖሩ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስን በቀላሉ መረዳትና በውስጡ ባለው ምክር ሕይወታቸውን መምራት ይችላሉ ማለት ነው። እነዚህ እውነታዎች መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚከተለው በማለት ከሚናገረው ሐሳብ ጋር ይስማማሉ፦

“አምላክ [አያዳላም]፤ ከዚህ ይልቅ ከየትኛውም ብሔር ቢሆን እሱን የሚፈራና ትክክል የሆነውን ነገር የሚያደርግ ሰው በእሱ ዘንድ ተቀባይነት አለው።”—የሐዋርያት ሥራ 10:34, 35

አንድ አፍቃሪ ወላጅ ለልጆቹ መመሪያ እንደሚሰጥ ሁሉ አፍቃሪ አባታችን ይሖዋም በቃሉ በመጽሐፍ ቅዱስ አማካኝነት መመሪያ ይሰጠናል። (2 ጢሞቴዎስ 3:16) ይህን መጽሐፍ ያጻፈው እኛን የሠራንና ለእኛ ከሁሉ የተሻለውን ነገር የሚያውቀው አምላክ ስለሆነ በቃሉ ላይ ሙሉ እምነት መጣል እንችላለን።

ታዲያ እንዲህ ያለውን ሕይወት ለማግኘት ምን ማድረግ ይጠበቅብሃል? እስቲ ቀጣዩን ርዕስ ተመልከት።

^ አን.6 የመጽሐፍ ቅዱስን ትርጉም ሥራና ስርጭት በተመለከተ ተጨማሪ መረጃ ለማግኘት www.pr418.com ላይ የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርቶች > ታሪክ እና መጽሐፍ ቅዱስ በሚለው ሥር ተመልከት።

^ አን.16 ተጨማሪ ማብራሪያ ለማግኘት በይሖዋ ምሥክሮች የተዘጋጀውን መጽሐፍ ቅዱስ የአምላክ ቃል ነው ወይስ የሰው? የተባለውን መጽሐፍ ምዕራፍ 9 ተመልከት። መጽሐፉ www.pr418.com ላይ ይገኛል። ላይብረሪ > መጻሕፍትና ብሮሹሮች በሚለው ሥር ተመልከት።