በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ ሰባት

በቤተሰባችሁ ውስጥ ዓመፀኛ ልጅ አለን?

በቤተሰባችሁ ውስጥ ዓመፀኛ ልጅ አለን?

1, 2. (ሀ) ኢየሱስ የአይሁድ ሃይማኖታዊ መሪዎችን ከሃዲነት ጎላ አድርጎ ለመግለጽ የትኛውን ምሳሌ ተጠቅሟል? (ለ) በጉርምስና ዕድሜ ላይ የሚገኙ ልጆችን በተመለከተ ከኢየሱስ ምሳሌ ምን ነጥብ እንማራለን?

ኢየሱስ ከመሞቱ ከጥቂት ቀናት በፊት ለአንድ የአይሁድ ሃይማኖታዊ መሪዎች ቡድን አንድ የሚያመራምር ጥያቄ አቅርቦ ነበር። እንዲህ አላቸው:- “ምን ይመስላችኋል? አንድ ሰው ሁለት ልጆች ነበሩት፤ ወደ አንደኛው ቀርቦ:- ልጄ ሆይ፣ ዛሬ ሂድና በወይኔ አትክልት ሥራ አለው። እርሱም መልሶ:- አልወድም አለ፤ ኋላ ግን ተጸጸተና ሄደ። ወደ ሁለተኛውም ቀርቦ እንዲሁ አለው እርሱም መልሶ:- እሺ ጌታዬ አለ፤ ነገር ግን አልሄደም። ከሁለቱ የአባቱን ፈቃድ ያደረገ ማን ነው?” የአይሁድ መሪዎቹ “ፊተኛው” ብለው መለሱለት።​—⁠ማቴዎስ 21:​28-31

2 እዚህ ላይ ኢየሱስ የአይሁድ መሪዎች ታማኞች ሆነው አለመገኘታቸውን ጎላ አድርጎ መግለጹ ነበር። እንደ ሁለተኛው ልጅ ነበሩ፤ የአምላክን ፈቃድ ለመፈጸም ቃል ቢገቡም ቃላቸውን አልጠበቁም። ይሁን እንጂ የኢየሱስ ምሳሌ ስለ ቤተሰብ ሕይወት በነበረው ጥሩ ግንዛቤ ላይ የተመሠረተ መሆኑን ብዙ ወላጆች ይገነዘባሉ። ኢየሱስ እዚህ ላይ በጥሩ ሁኔታ እንደገለጸው ብዙውን ጊዜ ወጣቶች የሚያስቡትን ለማወቅም ሆነ የሚሠሩትን ለመተንበይ በጣም አስቸጋሪ ነው። አንድ ወጣት በጉርምስና ዕድሜው ብዙ ችግር ይፈጥር ይሆናል፤ በኋላ ግን አድጎ ኃላፊነት የሚሰማውና የተከበረ ዐዋቂ ሰው ይሆናል። በአፍላ የጉርምስና ዕድሜ ላይ ስለሚገኙ ልጆች ዓመፅ በምንነጋገርበት ጊዜ ይህን ነጥብ ማስታወስ ይኖርብናል።

ዓመፀኛ ሲባል ምን ማለት ነው?

3. ወላጆች ልጄ ዓመፀኛ ነው ብለው ለመደምደም መቸኮል የሌለባቸው ለምንድን ነው?

3 አልፎ አልፎ በወላጆቻቸው ላይ ስላመፁ በአፍላ የጉርምስና ዕድሜ ላይ የሚገኙ ልጆች ትሰሙ ይሆናል። እንዲያውም ጨርሶ ለወላጆቹ አልገዛ ያለ ጎረምሳ ያለበትን ቤተሰብ ታውቁ ይሆናል። ይሁን እንጂ አንድ ልጅ በእርግጥ ዓመፀኛ መሆን አለመሆኑን ማወቅ ሁልጊዜ ቀላል አይደለም። ከዚህም በላይ በአንድ ቤተሰብ ውስጥ ያሉ አንዳንዶቹ ልጆች ሥርዓታማ ሆነው ሳለ ሌሎቹ ለምን እንደሚያምፁ ለማወቅ ሊያስቸግር ይችላል። ወላጆች ከልጆቻቸው መካከል አንዱ የለየለት ዓመፀኛ የመሆን አዝማሚያ እንዳለው ከጠረጠሩ ምን ማድረግ ይኖርባቸዋል? ይህን ጥያቄ ለመመለስ በቅድሚያ ዓመፀኛ ሲባል ምን ማለት እንደሆነ እንመልከት።

4-6. (ሀ) ዓመፀኛ ሲባል ምን ማለት ነው? (ለ) ወላጆች በአፍላ የጉርምስና ዕድሜ ላይ የሚገኘው ልጃቸው አልፎ አልፎ የማይታዘዛቸው ከሆነ ምን ነገር ማስታወስ ይኖርባቸዋል?

4 በአጭር አነጋገር ዓመፀኛ ማለት ሁልጊዜ ሆን ብሎ ትእዛዝ የሚጥስ ወይም የሚቃወም እንዲሁም ከእሱ በላይ ያለውን ሥልጣን የማያከብር ማለት ነው። “ስንፍና በሕፃን ልብ ታስሮአል።” (ምሳሌ 22:​15) ስለዚህ ሁሉም ልጆች በሆነ ወቅት ላይ የወላጅንም ሆነ ሌላን ሥልጣን መቃወማቸው አይቀርም። በተለይ ደግሞ በአካልና በስሜት በሚያድጉበት የጉርምስና ዕድሜ ላይ ይህን ሲያደርጉ ይታያሉ። በየትኛውም ሰው ሕይወት ውስጥ የሚከሰት ለውጥ ውጥረት ይፈጥራል፤ የጉርምስና ዕድሜ ደግሞ በለውጥ ሂደቶች የተሞላ ነው። በአፍላ የጉርምስና ዕድሜ ላይ የሚገኙት ልጆቻችሁ ከልጅነት ወደ ዐዋቂነት እየተሸጋገሩ ነው። ስለዚህ በጉርምስና ዕድሜ ወቅት አንዳንድ ወላጆችና ልጆች እርስ በርስ ለመጣጣም ይቸገራሉ። ብዙውን ጊዜ ወላጆች ሳያውቁት ይህን ሽግግር ለማዘግየት ይሞክራሉ፤ በአፍላ የጉርምስና ዕድሜ ላይ የሚገኙት ልጆች ደግሞ ሊያፋጥኑት ይፈልጋሉ።

5 ዓመፀኛ የሆነ በአፍላ የጉርምስና ዕድሜ ላይ የሚገኝ ልጅ የወላጆቹን መመሪያዎች ያቃልላል። ይሁን እንጂ አልፎ አልፎ አንዳንድ ትእዛዞችን መተላለፉ ዓመፀኛ ሊያሰኘው እንደማይችል መዘንጋት የለብንም። በተጨማሪም መንፈሳዊ ጉዳዮችን በተመለከተ አንዳንድ ልጆች መጀመሪያ ላይ ለመጽሐፍ ቅዱስ እውነት እምብዛም ፍላጎት ላይኖራቸው ይችላል። እንደዚያም ሆኖ ግን ዓመፀኞች ላይሆኑ ይችላሉ። ስለዚህ ልጄ ዓመፀኛ ነው ብላችሁ ለመደምደም አትቸኩሉ።

6 ሁሉም ልጆች የጉርምስና ዕድሜ ላይ ሲደርሱ በወላጆቻቸው ሥልጣን ላይ ያምፃሉ ማለት ነውን? በፍጹም፣ እንደዚያ ማለት አይደለም። እንዲያውም ማስረጃዎቹ እንደሚያሳዩት በጉርምስና ዕድሜያቸው በጣም ዓመፀኛ የሚሆኑት ወጣቶች ቁጥር አነስተኛ ነው። ይሁን እንጂ ሁልጊዜ ስለሚያምፅ ልበ ደንዳና ልጅ ምን ለማለት ይቻላል? ለእንዲህ ዓይነቱ ዓመፅ መንስኤ የሚሆነው ነገር ምን ሊሆን ይችላል?

የዓመፀኝነት መንስኤዎች

7. ሰይጣናዊው የዓለም መንፈስ አንድ ልጅ ዓመፀኛ እንዲሆን ተጽዕኖ ሊያሳድርበት የሚችለው እንዴት ነው?

7 ለዓመፀኝነት አንዱ ትልቅ መንስኤ ሰይጣናዊው የዓለም መንፈስ ነው። “ዓለምም በሞላው በክፉው” ተይዟል። (1 ዮሐንስ 5:​19) በሰይጣን ቁጥጥር ሥር ያለው ዓለም ክርስቲያኖች ሊቋቋሙት የሚገባ ጎጂ ባህል አዳብሯል። (ዮሐንስ 17:​15) በአሁኑ ጊዜ ከዚህ ባህል መካከል አብዛኛው ከቀድሞው ዘመን ይበልጥ የከፋ፣ በጣም አደገኛና መጥፎ ተጽዕኖ በሚያሳድሩ ነገሮች የተሞላ ነው። (2 ጢሞቴዎስ 3:​1-5, 13) ወላጆች ልጆቻቸውን የማያስተምሯቸው፣ የማያስጠነቅቋቸውና የማይጠብቋቸው ከሆነ ‘በማይታዘዙት ልጆች ላይ አሁን በሚሠራው መንፈስ’ በቀላሉ ሊሸነፉ ይችላሉ። (ኤፌሶን 2:​2) የእኩዮች ተጽዕኖም ከዚህ ጋር የተያያዘ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ “የሰነፎች ባልንጀራ ግን ክፉ መከራን ይቀበላል” ይላል። (ምሳሌ 13:​20) በዚህ ዓለም መንፈስ ከተሞሉ ሰዎች ጋር የሚወዳጅም ይህ መንፈስ ተጽዕኖ ሊያሳድርበት ይችላል። ወጣቶች አምላካዊ የሆኑ መሠረታዊ ሥርዓቶችን መታዘዝ ከሁሉ ለተሻለው የሕይወት መንገድ መሠረት መሆኑን እንዲገነዘቡ የማያቋርጥ እርዳታ ያስፈልጋቸዋል።​—⁠ኢሳይያስ 48:17, 18

8. አንድ ልጅ ዓመፀኛ እንዲሆን ሊገፋፉት የሚችሉ አንዳንድ ነገሮች ምንድን ናቸው?

8 ለዓመፀኝነት መንስኤ ሊሆን የሚችለው ሌላው ነገር በቤት ውስጥ ያለው መንፈስ ነው። ለምሳሌ ያህል አንድ ወላጅ የአልኮል ሱሰኛ፣ አደንዛዥ ዕፆች የሚወስድ ወይም ደግሞ ጠበኛ ከሆነ በአፍላ የጉርምስና ዕድሜ ላይ የሚገኘው ልጅ ለሕይወት ያለው አመለካከት ሊዛባ ይችላል። በአንጻራዊ ሁኔታ ሲታይ ሰላማዊ በሆኑ ቤተሰቦች ውስጥ እንኳ አንድ ልጅ ወላጆቹ ምንም ትኩረት እንደማይሰጡት ሆኖ ከተሰማው ሊያምፅ ይችላል። ይሁን እንጂ በአፍላ የጉርምስና ዕድሜ ላይ የሚገኙ ልጆች የሚያምፁት በውጫዊ ተጽዕኖዎች የተነሳ ብቻ አይደለም። ወላጆች አምላካዊ የሆኑ መሠረታዊ ሥርዓቶችን በሥራ እያዋሉና በተቻለ መጠን በአካባቢያቸው ካለው ዓለም ተጽዕኖ ልጆቻቸውን ለመጠበቅ ጥረት እያደረጉም እንኳ አንዳንድ ልጆች የወላጆቻቸውን መመሪያዎች ወደ ጎን ገሸሽ ያደርጋሉ። ለምን? እንዲህ የሚያደርጉት በሌላው የችግሮቻችን መንስኤ ማለትም በሰብዓዊ አለፍጽምና ምክንያት ሊሆን ይችላል። ጳውሎስ እንዲህ ብሏል:- “ኃጢአት በአንድ ሰው [በአዳም] ወደ ዓለም ገባ በኃጢአትም ሞት፣ እንደዚሁም ሁሉ ኃጢአትን ስላደረጉ ሞት ለሰው ሁሉ ደረሰ።” (ሮሜ 5:​12) አዳም ራስ ወዳድ የሆነ ዓመፀኛ ነው፤ ለዘሮቹ ሁሉ መጥፎ ቅርስ አውርሶ አልፏል። አንዳንድ ወጣቶች ልክ እንደ ቀድሞ አባታቸው ማመፅን ይመርጣሉ።

ልል የነበረው ዔሊና በጣም ጥብቅ የነበረው ሮብዓም

9. አንድ ልጅ ዓመፀኛ እንዲሆን ሊያነሳሱት የሚችሉ ሁለት ተቃራኒ ነገሮች ምንድን ናቸው?

9 በአፍላ የጉርምስና ዕድሜ ላይ የሚገኙ ልጆች እንዲያምፁ የሚያደርጋቸው ሌላው ነገር ወላጆች ልጆችን በማሳደግ ረገድ ያላቸው ሚዛናዊ ያልሆነ አመለካከት ነው። (ቆላስይስ 3:​21) አንዳንድ በጣም ጠንቃቃ የሆኑ ወላጆች ልጆቻቸውን የማያፈናፍን ገደብ የሚያወጡ ከመሆኑም በላይ ጥብቅ የሆነ ተግሣጽ ይሰጧቸዋል። ሌሎቹ ደግሞ በጣም ልል ይሆኑና በጉርምስና ዕድሜ ላይ የሚገኙትን ተሞክሮ የሌላቸውን ልጆቻቸውን ሊጠብቋቸው የሚችሉ መመሪያዎችን ሳይሰጧቸው ይቀራሉ። ሁለቱንም ሚዛናዊ በሆነ መንገድ ጎን ለጎን ማስኬድ ሁልጊዜ ቀላል አይሆንም። በተጨማሪም የተለያዩ ልጆች የሚያስፈልጋቸው ክትትል የተለያየ ነው። አንደኛው ከሌላው የበለጠ ክትትል ሊያስፈልገው ይችላል። ያም ሆኖ ግን በጣም ጥብቅ መሆንም ሆነ በጣም ልል መሆን አደጋ እንደሚያስከትል የሚከተሉት ሁለት የመጽሐፍ ቅዱስ ምሳሌዎች በግልጽ ያሳያሉ።

10. ዔሊ ታማኝ ሊቀ ካህን የነበረ ሊሆን ቢችልም እንኳ ጥሩ ወላጅ ያልነበረው ለምንድን ነው?

10 የጥንቷ እስራኤል ሊቀ ካህናት የነበረው ዔሊ ልጆች ነበሩት። ለ40 ዓመታት ያህል ያገለገለ በመሆኑ የአምላክን ሕግ ጠንቅቆ ያውቅ እንደነበረ ምንም ጥርጥር የለውም። ዔሊ የዘወትር የክህነት ግዴታዎቹን በታማኝነት ይፈጽም እንደነበረ መገመት አያዳግትም፤ በተጨማሪም አፍኒንና ፊንሐስ የተባሉ ልጆቹን የአምላክን ሕግ በሚገባ አስተምሯቸው ሊሆን ይችላል። ይሁን እንጂ ዔሊ ልጆቹን መረን ለቅቋቸው ነበር። አፍኒንና ፊንሐስ ዋነኛ ካህናት ሆነው ያገለግሉ የነበረ ቢሆንም የራሳቸውን ምኞትና ርካሽ የሆነ የጾታ ፍላጎታቸውን ለማርካት ብቻ የሚሯሯጡ “ምናምንቴዎች” ነበሩ። ሆኖም ቅዱስ በሆነ ሥፍራ ጸያፍ የሆኑ ድርጊቶች በፈጸሙ ጊዜ ዔሊ ከካህንነት ቦታቸው ለማስወገድ ድፍረት አጥቶ ነበር። ከዚህ ይልቅ ተራ የሆነ ተግሣጽ ሰጣቸው። ዔሊ በዚህ ልል አቋሙ ከአምላክ ይበልጥ ልጆቹን አክብሯል። በዚህም የተነሣ ልጆቹ በይሖዋ ንጹሕ አምልኮ ላይ ሊያምፁና መላው የዔሊ ቤት መዓት ሊወርድበት ችሏል።​—⁠1 ሳሙኤል 2:​12-17, 22-25, 29፤ 3:​13, 14፤ 4:⁠11-22

11. ወላጆች ከዔሊ መጥፎ ምሳሌ ምን ሊማሩ ይችላሉ?

11 እነዚህ ነገሮች ሲፈጸሙ የዔሊ ልጆች ዐዋቂዎች ነበሩ፤ ቢሆንም ይህ ታሪክ ተግሣጽ አለመስጠት የሚያስከትለውን አደጋ ጎላ አድርጎ ያሳያል። (ከምሳሌ 29:​21 ጋር አወዳድሩ።) አንዳንድ ወላጆች ልጆቻቸውን ያፈቀሩ እየመሰላቸው ስድ ይለቋቸዋል፤ ከዚህም የተነሳ ግልጽ፣ ቋሚና ምክንያታዊ መመሪያዎችን ሳያወጡና ሳያስፈጽሙ ሊቀሩ ይችላሉ። አምላካዊ የሆኑ መሠረታዊ ሥርዓቶች በሚጣሱበት ጊዜ እንኳ ሳይቀር ፍቅራዊ ተግሣጽ ሳይሰጡ ይቀራሉ። ስድ ለቀው ስለሚያሳድጓቸው ልጆቻቸው የወላጅንም ሆነ ሌላ ዓይነት ሥልጣንን ከቁብ የማይቆጥሩ ሊሆኑ ይችላሉ።​—⁠ከ⁠መክብብ 8:​11 ጋር አወዳድሩ።

12. ሮብዓም በሥልጣን አጠቃቀም ረገድ ምን ስህተት ፈጽሟል?

12 ሮብዓም ደግሞ በተቃራኒው ሥልጣንን አላግባብ በመጠቀም ረገድ እንደ ምሳሌ የሚጠቀስ ሰው ነው። ሮብዓም አንድ በነበረው የእስራኤል መንግሥት ላይ የነገሠ የመጨረሻው ንጉሥ ሲሆን ጥሩ ንጉሥ አልነበረም። ቀደም ሲል አባቱ ማለትም ሰሎሞን በአገሩ ሰዎች ላይ ከባድ ቀንበር በመጣሉ ሕዝቡ በጣም ተከፍቶ ነበር። ታዲያ ሮብዓም ራራላቸውን? በፍጹም። የሕዝቡ ተወካዮች ቀንበሩን እንዲያላላላቸው በጠየቁት ጊዜ በዕድሜ የሚበልጡት አማካሪዎቹ የሰጡትን በሳል ምክር ወደ ጎን ትቶ በሕዝቡ ላይ የተጣለው ቀንበር ይበልጥ እንዲጠብቅ ትእዛዝ አስተላለፈ። ይህ ዕብሪቱ አሥሩ የሰሜን ነገዶች እንዲያምፁና መንግሥቱ ለሁለት እንዲከፈል አድርጓል።​—⁠1 ነገሥት 12:​1-21፤ 2 ዜና መዋዕል 10:​19

13. ወላጆች ሮብዓም የፈጸመውን ስህተት ላለመድገም ምን ማድረግ ይችላሉ?

13 ወላጆች ስለ ሮብዓም ከሚናገረው የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ አንዳንድ ጠቃሚ ትምህርቶችን መቅሰም ይችላሉ። በጸሎት ‘ይሖዋን መፈለግና’ ልጆቻቸውን ለማሳደግ የሚጠቀሙባቸውን ዘዴዎች በመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶች አማካኝነት መመርመር ይኖርባቸዋል። (መዝሙር 105:​4) መክብብ 7:​7 “ግፍ ጠቢቡን ያሳብደዋል” ሲል ይገልጻል። በሚገባ የታሰበባቸው ገደቦች በጉርምስና ዕድሜ ላይ የሚገኙ ልጆች ከጉዳት ተጠብቀው እንዲያድጉ ይረዷቸዋል። ሆኖም ልጆች አግባብነት ያለው በራስ የመመካትና በራስ የመተማመን መንፈስ እንዳያዳብሩ የሚያደርግ በጣም ጥብቅ የሆነና የማያፈናፍን ሁኔታ መፈጠር የለበትም። ወላጆች መጠነኛ ነፃነትንና በግልጽ የተቀመጡ የማይለዋወጡ ገደቦችን ሚዛናዊ በሆነ መንገድ ጎን ለጎን ለማስኬድ በሚጥሩበት ጊዜ በአፍላ የጉርምስና ዕድሜ ላይ የሚገኙ አብዛኞቹ ልጆች ለማመፅ የሚጋበዙበት ሁኔታ አይኖርም።

መሠረታዊ የሆኑ ነገሮችን ማሟላት ዓመፅን ሊያስቀር ይችላል

ልጆች በአፍላ የጉርምስና ዕድሜያቸው ወቅት የሚያጋጥሟቸውን ችግሮች መቋቋም እንዲችሉ ወላጆቻቸው የሚረዷቸው ከሆነ የተረጋጋ መንፈስ ይዘው ያድጋሉ

14, 15. ወላጆች የልጃቸውን ዕድገት እንዴት መመልከት ይኖርባቸዋል?

14 ምንም እንኳ ወላጆች ሕፃን የነበሩ ልጆቻቸው በአካላዊ ሁኔታ ወደ ጉልምስና እያደጉ ሲሄዱ ማየታቸው የሚያስደስታቸው ቢሆንም በጉርምስና ዕድሜያቸው በእነሱ መመካት ትተው በራሳቸው መተማመን ሲጀምሩ ግራ ሊጋቡ ይችላሉ። በዚህ የሽግግር ወቅት ላይ በአፍላ የጉርምስና ዕድሜ ላይ የሚገኘው ልጃችሁ አልፎ አልፎ ግትር አቋም ቢይዝ ወይም ለመተባበር ፈቃደኛ ባይሆን ልትደነቁ አይገባም። የክርስቲያን ወላጆች ግብ ልጃቸውን የጎለመሰ፣ የተረጋጋ መንፈስ ያለውና ኃላፊነት የሚሰማው ክርስቲያን አድርጎ ማሳደግ እንደሆነ መዘንጋት የለባችሁም።​—⁠ከ⁠1 ቆሮንቶስ 13:​11 እና ከ⁠ኤፌሶን 4:​13, 14 ጋር አወዳድሩ።

15 ወላጆች ምንም እንኳ ከባድ ሊሆንባቸው ቢችልም በጉርምስና ዕድሜ ላይ የሚገኘው ልጃቸው የበለጠ ነፃነት እንዲሰጡት የሚያቀርብላቸውን ጥያቄ ውድቅ የማድረግ ልማድ ሊኖራቸው አይገባም። አንድ ልጅ ጤናማ በሆነ መንገድ ራሱን ሆኖ ማደግ አለበት። እንዲያውም በአፍላ የጉርምስና ዕድሜ ላይ የሚገኙ አንዳንድ ልጆች በአንፃራዊ ሁኔታ ለጋ በሆነ ዕድሜያቸውም እንኳ በሳል አመለካከት ማዳበር ይጀምራሉ። ለምሳሌ ያህል መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ወጣቱ ንጉሥ ኢዮስያስ ሲናገር “ገና ብላቴና ሳለ [15 ዓመት ገደማ ሲሆነው] የአባቱን የዳዊትን አምላክ ይፈልግ ጀመር” ይላል። ይህ ለየት ያለ ወጣት ኃላፊነት የሚሰማው ግለሰብ እንደነበረ ግልጽ ነው።​—⁠2 ዜና መዋዕል 34:​1-3

16. ልጆች የበለጠ ኃላፊነት ሲሰጣቸው ምን ነገር መገንዘብ ይኖርባቸዋል?

16 ይሁን እንጂ ነፃነት ተጠያቂነት ያስከትላል። ስለዚህ ወደ ጉልምስና በመሸጋገር ላይ ያለው ልጃችሁ አንዳንድ የሚወስዳቸው ውሳኔዎችና የሚያደርጋቸው ነገሮች የሚያስከትሉትን ውጤቶች እንዲቀምስ አድርጉት። “ሰው የሚዘራውን ሁሉ ያንኑ ደግሞ ያጭዳል” የሚለው መሠረታዊ ሥርዓት በአፍላ የጉርምስና ዕድሜ ላይ ለሚገኙ ልጆችም ሆነ ለዐዋቂዎች ይሠራል። (ገላትያ 6:​7) ልጆች ለዘላለም በእናንተ ጥላ ሥር ሊኖሩ አይችሉም። ይሁን እንጂ ልጃችሁ ፈጽሞ ተቀባይነት የሌለው ነገር ለመፈጸም ቢነሳስ? ኃላፊነት ያለባችሁ እንደመሆናችሁ መጠን መከልከል ይኖርባችኋል። በተጨማሪም ለምን እንደከለከላችሁት ልታስረዱት የምትችሉ ቢሆንም ቃላችሁን ምንም ነገር ሊለውጠው አይገባም። (ከማቴዎስ 5:​37 ጋር አወዳድሩ።) ሆኖም ‘የለዘበች መልስ ቁጣን የምትመልስ’ በመሆኑ ‘አይሆንም’ ብላችሁ ስትከለክሉት አነጋገራችሁ የለዘበና ምክንያታዊነት የሚንፀባረቅበት እንዲሆን ጥረት አድርጉ።​—⁠ምሳሌ 15:​1

17. አንድ ወላጅ በአፍላ የጉርምስና ዕድሜ ላይ ለሚገኝ ልጅ ሊያሟላቸው የሚገቡ አንዳንድ አስፈላጊ ነገሮች ምንድን ናቸው?

17 ምንም እንኳ ወጣቶች ከሚሰጧቸው ገደቦችና መመሪያዎች ጋር የማይስማሙባቸው ጊዜያት ቢኖሩም ቋሚ በሆነ ተግሣጽ ተገቢውን ጥበቃ ማግኘት አለባቸው። አንድ ወላጅ ደስ ባለው ጊዜ ሁሉ መመሪያዎችን የሚለዋውጥ ከሆነ ልጆቹን ሊያበሳጫቸው ይችላል። ከዚህም በላይ በአፍላ የጉርምስና ዕድሜ ላይ የሚገኙ ወጣቶች ቁርጥ ያለ እርምጃ የመውሰድ፣ የዓይናፋርነት ወይም ደግሞ በራስ የመተማመን መንፈስ የማጣት ችግርን መቋቋም የሚችሉበት ማበረታቻና እርዳታ እንደ አስፈላጊነቱ የሚሰጣቸው ከሆነ የተረጋጋና የማይለዋወጥ መንፈስ ይዘው ሊያድጉ ይችላሉ። በተጨማሪም በአፍላ የጉርምስና ዕድሜ ላይ የሚገኙ ልጆች ወላጆቻቸው እምነት ሲጥሉባቸው ይደሰታሉ።​—⁠ከ⁠ኢሳይያስ 35:​3, 4፤ ከ⁠ሉቃስ 16:​10 እና 19:​17 ጋር አወዳድሩ።

18. በአፍላ የጉርምስና ዕድሜ ላይ የሚገኙ ልጆችን በተመለከተ ምን አበረታች እውነታዎች አሉ?

18 ብዙውን ጊዜ በቤተሰብ ውስጥ ሰላም፣ የተረጋጋ መንፈስና ፍቅር ሲኖር ልጆች በጥሩ ሁኔታ ያድጋሉ፤ ይህ ደግሞ ወላጆችን ሊያጽናናቸው ይችላል። (ኤፌሶን 4:​31, 32፤ ያዕቆብ 3:​17, 18) እንዲያውም ብዙ ወጣቶች የአልኮል ሱሰኛ፣ ጠብ ወይም ደግሞ ሌሎች ጎጂ ተጽዕኖዎች ባሉባቸው ቤተሰቦች መካከል ቢያድጉም እንኳ እንዲህ ዓይነቱን መጥፎ ተጽዕኖ ተቋቁመው ጥሩ ሰው መሆን ችለዋል። ስለዚህ ወጣት ልጆቻችሁ የተረጋጋ መንፈስ እንዲያድርባቸው እንዲሁም እንደምትወዷቸውና ልዩ ትኩረት እንደምትሰጧቸው እንዲሰማቸው ማድረግ ይኖርባችኋል፤ እንዲህ ካደረጋችሁ ምክንያታዊ ገደቦችና ከቅዱሳን ጽሑፎች መሠረታዊ ሥርዓቶች ጋር የሚስማማ ተግሳጽ ብትሰጧቸውም እንኳ ወደፊት የምትኮሩባቸው ዓይነት ሰዎች ሆነው ማደጋቸው አይቀርም።​—⁠ከምሳሌ 27:​11 ጋር አወዳድሩ።

ልጆች ችግር ውስጥ ሲገቡ

19. ወላጆች ልጃቸውን ሊሄድበት በሚገባው መንገድ ማሠልጠን ያለባቸው ቢሆንም ልጁ ምን ኃላፊነት አለበት?

19 ጥሩ ወላጅ መሆን ወሳኝ ነው። ምሳሌ 22:​6 “ልጅን በሚሄድበት መንገድ ምራው፣ በሸመገለም ጊዜ ከእርሱ ፈቀቅ አይልም” ይላል። ይሁን እንጂ ጥሩ ወላጆች እያሏቸው ከባድ ችግሮች ስላሉባቸው ልጆችስ ምን ለማለት ይቻላል? እንዲህ ዓይነት ሁኔታ ሊያጋጥም ይችላልን? አዎ፣ ሊያጋጥም ይችላል። ይህ የምሳሌ ጥቅስ ልጅ ወላጆቹን ‘የመስማትና’ የመታዘዝ ኃላፊነት እንዳለበት ጎላ አድርገው ከሚገልጹት ሌሎች ጥቅሶች አንጻር መታየት አለበት። (ምሳሌ 1:​8) በቤተሰቡ መካከል ስምምነት እንዲኖር ከተፈለገ የቅዱሳን ጽሑፎችን መሠረታዊ ሥርዓቶች ሥራ ላይ በማዋል ረገድ ወላጆችም ሆኑ ልጆች መተባበር አለባቸው። ወላጆችና ልጆች ተባብረው የማይሠሩ ከሆነ ችግሮች ይፈጠራሉ።

20. ልጆች ባለማወቅ ስህተት ሲሠሩ ወላጆቻቸው ምን ቢያደርጉ የተሻለ ይሆናል?

20 ወላጆች በአፍላ የጉርምስና ዕድሜ ላይ የሚገኝ ልጃቸው ሲሳሳትና ችግር ውስጥ ሲገባ ምን ማድረግ ይኖርባቸዋል? ልጁ ይበልጥ እርዳታ የሚያስፈልገው በዚህ ጊዜ ነው። ወላጆች ልጃቸው ተሞክሮ የሚጎድለው መሆኑን ካስታወሱ ከሚገባው በላይ ከመቆጣት ሊቆጠቡ ይችላሉ። ጳውሎስ በጉባኤው ውስጥ የነበሩ የጎለመሱ ሰዎችን እንዲህ ሲል መክሯቸዋል:- “ሰው በማናቸውም በደል ስንኳ ቢገኝ፣ መንፈሳውያን የሆናችሁ እናንተ እንደዚህ ያለውን ሰው በየውሃት መንፈስ አቅኑት።” (ገላትያ 6:​1) ወላጆችም ልጃቸው ባለማወቅ ስህተት በሚፈጽምበት ጊዜ ይህንኑ ሥርዓት መከተል ይችላሉ። ልጁ የሠራው ነገር ስህተት የሆነው ለምን እንደሆነና ስህተቱን ዳግመኛ ላለመፈጸም ምን ማድረግ እንደሚችል በሚያስረዱበት ጊዜ የሚጠሉት የፈጸመውን ስህተት እንጂ እሱን እንዳልሆነ ግልጽ ማድረግ አለባቸው።​—⁠ከይሁዳ 22, 23 ጋር አወዳድሩ።

21. ወላጆች ልጆቻቸው ከባድ ኃጢአት በሚፈጽሙበት ጊዜ የክርስቲያን ጉባኤን ምሳሌ በመከተል ምን ማድረግ ይኖርባቸዋል?

21 ልጁ የፈጸመው ጥፋት በጣም ከባድ ከሆነስ? እንዲህ ዓይነት ሁኔታ በሚፈጠርበት ጊዜ ልጁ ልዩ እርዳታና ጥበብ የተሞላበት አመራር ያስፈልገዋል። አንድ የጉባኤ አባል ከባድ ኃጢአት በሚፈጽምበት ጊዜ ንስሐ መግባትና የሽማግሌዎችን እርዳታ መጠየቅ ይኖርበታል። (ያዕቆብ 5:​14-16) ንስሐ ከገባ በኋላ ሽማግሌዎቹ ወደ ቀድሞ መንፈሳዊ አቋሙ እንዲመለስ ይረዱታል። በቤተሰብ ውስጥ ደግሞ ወላጆች ምንም እንኳ በጉዳዩ ላይ ከሽማግሌዎች ጋር መወያየት ሊያስፈልጋቸው ቢችልም ጥፋት የሠራውን በአፍላ የጉርምስና ዕድሜ ላይ የሚገኝ ልጅ የመርዳት ኃላፊነት አለባቸው። ልጃቸው የፈጸመውን ከባድ ኃጢአት ከሽማግሌዎች አካል ለመደበቅ መሞከር የለባቸውም።

22. ወላጆች ልጃቸው ከባድ ስህተት ከፈጸመ የይሖዋን ምሳሌ በመከተል ምን ዓይነት አመለካከት ለመያዝ ይጥራሉ?

22 የራሳችን ልጆች የፈጸሙትን ከባድ ችግር ለማስተካከል የምናደርገው ጥረት እልህ አስጨራሽ ነው። ወላጆች በጣም ከመበሳጨታቸው የተነሳ እንዲህ ዓይነቱን አስቸጋሪ ልጅ በቁጣ ለማስፈራራት ሊነሳሱ ይችላሉ፤ ይሁን እንጂ እንዲህ ማድረጉ ልጁን ከማስመረር በቀር የሚፈይደው ነገር ላይኖር ይችላል። የዚህ ወጣት የወደፊት ሕይወት በዚህ ወሳኝ ወቅት በምታደርጉለት ነገር ላይ የተመካ ሊሆን እንደሚችል አስታውሱ። በተጨማሪም ይሖዋ ሕዝቡ ከትክክለኛው ጎዳና ርቀው በነበረበት ጊዜ ንስሐ እስከገቡ ድረስ ይቅር ሊላቸው ዝግጁ እንደነበረ አትዘንጉ። ይሖዋ የተናገራቸውን የሚከተሉትን ፍቅራዊ ቃላት ተመልከቱ:- “ኑና እንዋቀስ ይላል እግዚአብሔር፤ ኃጢአታችሁ እንደ አለላ ብትሆን እንደ አመዳይ ትነጻለች፤ እንደ ደምም ብትቀላ እንደ ባዘቶ ትጠራለች።” (ኢሳይያስ 1:​18) ለወላጆች እንዴት ያለ ግሩም ምሳሌ ነው!

23. ወላጆች ከልጃቸው መካከል አንዱ ከባድ ኃጢአት በሚፈጽምበት ጊዜ ምን ማድረግ አለባቸው? ምን ማድረግስ የለባቸውም?

23 ስለዚህ ልጁ አካሄዱን እንዲያስተካክል ለማበረታታት ጥረት አድርጉ። ተሞክሮ ካላቸው ወላጆችና ከሽማግሌዎች ጥሩ ምክር ለማግኘት ጣሩ። (ምሳሌ 11:​14) ስሜታዊ የሆነ እርምጃ እንዳትወስዱና ልጃችሁ ዳግመኛ እናንተን ለመቅረብ እንዲቸገር የሚያደርግ ነገር እንዳትናገሩ ወይም እንዳታደርጉ ጥንቃቄ አድርጉ። በቁጣ መገንፈልና ከሚገባው በላይ መናደድ የለባችሁም። (ቆላስይስ 3:​8) ቶሎ ተስፋ አትቁረጡ። (1 ቆሮንቶስ 13:​4, 7) ክፋትን መጥላት ያለባችሁ ቢሆንም ምንም የማትራሩና በልጃችሁ የምትመረሩ መሆን የለባችሁም። ከሁሉ በላይ ደግሞ ወላጆች ጥሩ ምሳሌ ለመሆንና በአምላክ ላይ ያላቸውን እምነት አጠንክረው ለመያዝ መጣር ይኖርባቸዋል።

የለየለትን ዓመፀኛ ልጅ እንዴት መያዝ እንደሚገባ

24. አንዳንድ ጊዜ በክርስቲያን ቤተሰብ ውስጥ ምን አሳዛኝ ሁኔታ ይፈጠራል? አንድ ወላጅ ለእንዲህ ዓይነቱ ሁኔታ ምን ምላሽ መስጠት አለበት?

24 አንድ ወጣት ክርስቲያናዊ እሴቶችን ሙሉ በሙሉ ወደ ጎን ገሸሽ በማድረግ እሺ ብሎ የማይመለስ የለየለት ዓመፀኛ ሊሆን የሚችልበት አጋጣሚ ይኖራል። በዚህ ጊዜ ትኩረታችሁን በተቀሩት ልጆች ላይ በማሳረፍ የቤተሰብ ሕይወታቸው በጥሩ ሁኔታ እንዲቀጥል ማድረግ ወይም እንደገና መገንባት ይኖርባችኋል። ሌሎቹን ልጆች ችላ ብላችሁ ኃይላችሁንና ችሎታችሁን በሙሉ ለዓመፀኛው ልጅ ብቻ እንዳታውሉ መጠንቀቅ አለባችሁ። ችግሩን ከተቀሩት የቤተሰባችሁ አባላት ለመደበቅ ከመሞከር ይልቅ ጉዳዩን ተገቢ እስከሚሆንበት ደረጃ ድረስ በመግለጽ በሚያጽናና መንገድ አወያዩአቸው።​—⁠ከምሳሌ 20:​18 ጋር አወዳድሩ።

25. (ሀ) ወላጆች ልጃቸው የለየለት ዓመፀኛ በሚሆንበት ጊዜ የክርስቲያን ጉባኤን አሠራር በመከተል ምን ሊያደርጉ ይችላሉ? (ለ) ወላጆች ከልጃቸው መካከል አንዱ ዓመፀኛ ቢሆን ምን ነገር ማስታወስ ይኖርባቸዋል?

25 ሐዋርያው ዮሐንስ በጉባኤው መካከል የነበረን ለመስተካከል ያልቻለ አንድ ዓመፀኛ ሰው በተመለከተ ሲናገር “በቤታችሁ አትቀበሉት ሰላምም አትበሉት” ብሎ ነበር። (2 ዮሐንስ 10) ወላጆችም ልጃቸው ለአካለ መጠን የደረሰና የለየለት ዓመፀኛ ከሆነ እንዲህ ዓይነት አቋም መውሰዱን አስፈላጊ ሆኖ ሊያገኙት ይችላሉ። እንዲህ ዓይነት አቋም መውሰድ አስቸጋሪና ከባድ ቢሆንም የተቀረውን ቤተሰብ ለመጠበቅ ሲባል አንዳንድ ጊዜ እንዲህ ማድረጉ የግድ አስፈላጊ ነው። ቤተሰባችሁ የእናንተ ጥበቃና የበላይ አመራር ያስፈልገዋል። ስለዚህ ዘወትር በግልጽ የተቀመጡና ምክንያታዊ የሆኑ የሥነ ምግባር ገደቦችን መጠቀም ይኖርባችኋል። ከሌሎቹ ልጆች ጋር ጥሩ የሐሳብ ልውውጥ ይኑራችሁ። በትምህርት ቤትና በጉባኤ ያላቸውን እንቅስቃሴና ተሳትፎ ተከታተሉ። በተጨማሪም ዓመፀኛው ልጅ የሚያደርጋቸውን ነገሮች የምትቃወሙ ቢሆንም ልጁን እንደማትጠሉት እንዲገነዘቡ አድርጉ። ልጁን ሳይሆን መጥፎ ድርጊቱን አውግዙ። የያዕቆብ ሁለት ወንዶች ልጆች በፈጸሙት የጭካኔ ተግባር ቤተሰቡ በአካባቢው ማኅበረሰብ እንዲገለል ባደረጉ ጊዜ ያዕቆብ የረገመው ልጆቹን ሳይሆን ያደረባቸውን ኃይለኛ ቁጣ ነበር።​—⁠ዘፍጥረት 34:​1-31፤ 49:​5-7

26. ልጆቻቸውን በጥሩ ሁኔታ ለማሳደግ ከፍተኛ ጥረት የሚያደርጉ ወላጆች ከልጆቻቸው አንዱ ዓመፀኛ ቢሆን በምን ሊጽናኑ ይችላሉ?

26 በቤተሰባችሁ ውስጥ ለተከሰተው ነገር የተጠያቂነት ስሜት ያድርባችሁ ይሆናል። ይሁን እንጂ የይሖዋን ምክር በመከተል ማድረግ የምትችሉትንና አቅማችሁ የፈቀደውን ሁሉ ካደረጋችሁ ራሳችሁን የምትወቅሱበት ምንም ምክንያት አይኖርም። ማንም ሰው ፍጹም ወላጅ ሊሆን አይችልም፤ ሆኖም እናንተ ጥሩ ወላጅ ለመሆን ከፍተኛ ጥረት አድርጋችኋል። ስለዚህ በዚህ ልትጽናኑ ይገባችኋል። (ከ⁠ሥራ 20:​26 ጋር አወዳድሩ።) በቤተሰብ ውስጥ የለየለት ዓመፀኛ መፈጠሩ በጣም የሚያሳዝን ቢሆንም ልጃችሁ እንዲህ ከሆነባችሁ አምላክ ችግራችሁን እንደሚረዳና በሙሉ ነፍሳቸው ለእሱ ያደሩ አገልጋዮቹን ፈጽሞ እንደማይተዋቸው እርግጠኞች ሁኑ። (መዝሙር 27:​10) ቤተሰባችሁ የቀሩት ልጆች ሰላምና መንፈሳዊ ጥበቃ የሚያገኙበት ቦታ እንዲሆን ለማድረግ ቁርጥ ውሳኔ አድርጉ።

27. ልጃቸው ዓመፀኛ የሆነባቸው ወላጆች የአባካኙን ልጅ ምሳሌ በማስታወስ ሁልጊዜ ምን ተስፋ ሊያደርጉ ይችላሉ?

27 ከዚህም በተጨማሪ ፈጽሞ ተስፋ መቁረጥ የለባችሁም። ቀደም ሲል ልጃችሁን በጥሩ ሁኔታ ለማሠልጠን ያደረጋችሁት ጥረት ውሎ አድሮ የባዘነውን ልጅ ልብ ሊነካውና ወደ አእምሮው እንዲመለስ ሊያደርገው ይችላል። (መክብብ 11:​6) በርከት ያሉ ክርስቲያን ቤተሰቦች የእናንተ ዓይነት ሁኔታ አጋጥሟቸዋል፤ ከእነዚህም መካከል አንዳንዶቹ አስቸጋሪ የነበሩት ልጆቻቸው በኢየሱስ ምሳሌ ላይ ከተጠቀሰው አባካኝ ልጅ ጋር በሚመሳሰል ሁኔታ ሊመለሱላቸው ችለዋል። (ሉቃስ 15:​11-32) የእናንተም ልጅ እንደዚሁ ሊስተካከል ይችል ይሆናል።