በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 44

ሁሉም በዓላት አምላክን ያስደስታሉ?

ሁሉም በዓላት አምላክን ያስደስታሉ?

ይሖዋ በሕይወታችን ደስተኛ እንድንሆን ይፈልጋል፤ ደስታ ከሚሰጡን ነገሮች መካከል ደግሞ አንዳንድ ለየት ያሉ ቀኖችን ከወዳጅ ዘመዶቻችን ጋር አብረን ማሳለፍ ይገኝበታል። ይሁንና ሁሉም በዓላትና ዝግጅቶች አምላክን ያስደስታሉ? በዚህ ረገድ ለይሖዋ ያለንን ፍቅር ማሳየት የምንችለው እንዴት ነው?

1. አብዛኞቹ በዓላት ይሖዋን የሚያሳዝኑት ለምንድን ነው?

አብዛኞቹ በዓላት ከመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርቶች ጋር እንደሚጋጩ ወይም ከጣዖት አምልኮ እንደመጡ ስታውቅ ትገረም ይሆናል። እነዚህ በዓላት ከሐሰት ሃይማኖት ጋር ንክኪ ያላቸው ናቸው። ከመናፍስታዊ ድርጊቶች ጋር ግንኙነት ሊኖራቸው ወይም ‘ነፍስ አትሞትም’ በሚለው ትምህርት ላይ የተመሠረቱ ሊሆኑ ይችላሉ። አንዳንድ በዓላት ከአጉል እምነት ወይም በዕድል ከማመን የመነጩ ናቸው። (ኢሳይያስ 65:11) ይሖዋ አገልጋዮቹን “ራሳችሁን ለዩ . . . ርኩስ የሆነውንም ነገር አትንኩ” በማለት አስጠንቅቋቸዋል።—2 ቆሮንቶስ 6:17 a

2. ይሖዋ ለሰዎች ከልክ ያለፈ ክብር ለሚሰጡ በዓላት ምን አመለካከት አለው?

ይሖዋ ‘በሰዎች እንዳንታመን’ ያስጠነቅቀናል። (ኤርምያስ 17:5⁠ን አንብብ።) አንዳንድ በዓላት የሚከበሩት ገዢዎችን ወይም ወታደሮችን ለማክበር ነው። ሌሎች በዓላት ደግሞ ብሔራዊ ዓርማን ወይም የነፃነት ቀንን ለማሰብ ተብለው የሚከበሩ ናቸው። (1 ዮሐንስ 5:21) ፖለቲካዊ ወይም ማኅበራዊ ንቅናቄዎችን ለማስታወስ ተብለው የሚከበሩ በዓላትም አሉ። ይሖዋ በተለይ ከእሱ ዓላማ ጋር የሚጋጩ ሐሳቦችን ለሚያራምዱ ሰዎች ወይም ድርጅቶች ከልክ ያለፈ ክብር ስንሰጥ ምን የሚሰማው ይመስልሃል?

3. አንዳንድ በዓላት ተቀባይነት እንዳይኖራቸው የሚያደርጉት የትኞቹ ምግባሮች ናቸው?

መጽሐፍ ቅዱስ ‘ከልክ በላይ መጠጣትንና መረን የለቀቀ ድግስን’ ያወግዛል። (1 ጴጥሮስ 4:3) በአንዳንድ በዓላት ላይ ሰዎች ልቅ የሆነ ምግባር የሚያሳዩ ከመሆኑም ሌላ ሥነ ምግባር የጎደላቸው ነገሮችን ያደርጋሉ። ከይሖዋ ጋር ያለንን ወዳጅነት ይዘን መቀጠል ከፈለግን እንዲህ ካሉ ርኩስ ድርጊቶች መራቅ ይኖርብናል።

ጠለቅ ያለ ጥናት

በዓላትን ከማክበር ጋር በተያያዘ ጥሩ ውሳኔ በማድረግ ይሖዋን ማስደሰት የምትችለው እንዴት እንደሆነ እንመለከታለን።

4. ይሖዋን በማያስከብሩ በዓላት ከመካፈል ተቆጠብ

ኤፌሶን 5:10ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

  • አንድን በዓል ለማክበር ወይም ላለማክበር ስንወስን የትኛውን ነገር ማረጋገጥ ያስፈልገናል?

  • አንተ በምትኖርበት አካባቢ የትኞቹ በዓላት በስፋት ይከበራሉ?

  • እነዚህ በዓላት ይሖዋን የሚያስደስቱት ይመስልሃል?

ለምሳሌ ያህል፣ አምላክ የልደት በዓልን ስለማክበር ምን እንደሚሰማው አስበህ ታውቃለህ? የይሖዋ አገልጋዮች ልደታቸውን እንዳከበሩ የሚገልጽ አንድም ሐሳብ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አይገኝም፤ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ልደታቸውን እንዳከበሩ የተገለጹት ሁለት ሰዎች ሲሆኑ እነሱም ይሖዋን የማያገለግሉ ናቸው። ዘፍጥረት 40:20-22ን እና ማቴዎስ 14:6-10ን አንብቡ። ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

  • ሁለቱን የልደት በዓላት የሚያመሳስላቸው ምንድን ነው?

  • ከእነዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪኮች በመነሳት ይሖዋ ልደት ስለማክበር ምን የሚሰማው ይመስልሃል?

ያም ሆኖ እንዲህ ብለህ ልታስብ ትችላለህ፦ ‘የልደት በዓልን ወይም የመጽሐፍ ቅዱስ ድጋፍ የሌላቸውን ሌሎች በዓላት ማክበሬ በእርግጥ ለይሖዋ ያን ያህል ግድ ይሰጠዋል?’ ዘፀአት 32:1-8ን አንብቡ። ከዚያም ቪዲዮውን ተመልከቱና በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

  • በይሖዋ ዘንድ ተቀባይነት ያለውን ነገር መርምረን ማረጋገጥ ያለብን ለምንድን ነው?

  • እንዲህ ማድረግ የምንችለው እንዴት ነው?

አምላክን የማያስደስቱ በዓላትን ለመለየት የሚረዱ ጥያቄዎች

  • ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር በሚጋጭ ትምህርት ላይ የተመሠረተ ነው? ይህን ለማወቅ በበዓሉ አመጣጥ ላይ ምርምር አድርግ።

  • ለሰዎች፣ ለድርጅቶች ወይም ለብሔራዊ ዓርማዎች ከልክ ያለፈ ክብር የሚሰጥ ነው? ከማንም በላይ ክብር የምንሰጠው ለይሖዋ ነው፤ ደግሞም የዓለምን ችግሮች ሊፈታ የሚችለው እሱ ብቻ ነው።

  • በበዓሉ ወቅት የሚፈጸሙት ልማዶች ከመጽሐፍ ቅዱስ መሥፈርቶች ጋር የሚጋጩ ናቸው? በሥነ ምግባር ንጹሕ መሆን ያስፈልገናል።

5. የያዝከውን አቋም ሌሎች እንዲያከብሩልህ ማድረግ

ሌሎች ሰዎች ይሖዋን በማያስደስቱ በዓላት እንድትካፈል የሚያደርጉብህን ጫና መቋቋም ቀላል ላይሆን ይችላል። የያዝከውን አቋም በትዕግሥትና በዘዴ አስረዳቸው። እንዲህ ማድረግ የሚቻልበትን መንገድ ለማወቅ ቪዲዮውን ተመልከቱ

ማቴዎስ 7:12ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

  • በዚህ ጥቅስ መሠረት ከአንተ የተለየ እምነት ላላቸው ቤተሰቦችህ በዓል ማክበር እንደሌለባቸው ልትነግራቸው ይገባል?

  • አብረሃቸው በዓል ባታከብርም ቤተሰቦችህ እንደምትወዳቸው እንዲሰማቸው ምን ማድረግ ትችላለህ?

6. ይሖዋ ደስተኛ እንድንሆን ይፈልጋል

ይሖዋ ከወዳጅ ዘመዶቻችን ጋር ጥሩ ጊዜ እንድናሳልፍ ይፈልጋል። መክብብ 8:15ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • ይህ ጥቅስ ይሖዋ ደስተኛ እንድንሆን እንደሚፈልግ የሚያሳየው እንዴት ነው?

ይሖዋ ሕዝቦቹ ደስታ የሚሰጧቸውን ነገሮች እንዲያደርጉና ከሌሎች ጋር ጥሩ ጊዜ እንዲያሳልፉ ይፈልጋል። በብሔራት አቀፍ ስብሰባዎቻችን ላይ ይህ በግልጽ የሚታየው እንዴት ነው? ቪዲዮውን ተመልከቱ

ገላትያ 6:10ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

  • ለሌሎች ‘መልካም ለማድረግ’ የግድ በዓላትን ማክበር ያስፈልገናል?

  • ይበልጥ ደስተኛ የምትሆነው በበዓል ቀን ላይ ግዴታ ሆኖብህ ስጦታ ስትሰጥ ነው ወይስ በራስህ ተነሳስተህ የፈለግክበት ጊዜ ላይ ስትሰጥ?

  • ብዙ የይሖዋ ምሥክሮች አልፎ አልፎ ለልጆቻቸው ለየት ያሉ ዝግጅቶችን ያደርጋሉ፤ አንዳንድ ጊዜም ያልጠበቋቸውን ስጦታዎች በመስጠት ያስደስቷቸዋል። ልጆች ካሉህ ለልጆችህ ልታደርጋቸው የምትችላቸው አንዳንድ ለየት ያሉ ነገሮች ምንድን ናቸው?

አንዳንዶች እንዲህ ይላሉ፦ “የበዓሉ አመጣጥ ሊያሳስበን አይገባም። ዋናው ነገር ከወዳጅ ዘመዶቻችን ጋር ጥሩ ጊዜ ማሳለፍ መቻላችን ነው።”

  • አንተ ምን ትላለህ?

ማጠቃለያ

ይሖዋ ከወዳጅ ዘመዶቻችን ጋር ጥሩ ጊዜ እንድናሳልፍ ይፈልጋል። ሆኖም እሱን የማያስደስቱ በዓላትን እንድናከብር አይፈልግም።

ክለሳ

  • አንድ በዓል ይሖዋን የሚያስደስት መሆን አለመሆኑን ለማወቅ የትኞቹን ጥያቄዎች ልንጠይቅ እንችላለን?

  • ቤተሰቦቻችንና ወዳጆቻችን ከበዓላት ጋር በተያያዘ ያደረግነውን ውሳኔ እንዲረዱልን ማድረግ የምንችለው እንዴት ነው?

  • ይሖዋ ደስተኛ እንድንሆንና ጥሩ ጊዜ እንድናሳልፍ ይፈልጋል ብለህ እንድታምን የሚያደርግህ ምንድን ነው?

ግብ

ምርምር አድርግ

ክርስቲያኖች ከማያከብሯቸው በዓላት መካከል አንዳንዶቹ የትኞቹ ናቸው?

“የይሖዋ ምሥክሮች አንዳንድ በዓላትን የማያከብሩት ለምንድን ነው?” (ድረ ገጻችን ላይ የወጣ ርዕስ)

የልደት በዓልን ማክበር አምላክን አያስደስትም እንድንል የሚያደርጉንን አራት ምክንያቶች ተመልከት።

“የይሖዋ ምሥክሮች ልደት የማያከብሩት ለምንድን ነው?” (ድረ ገጻችን ላይ የወጣ ርዕስ)

ይሖዋን የሚወዱ ልጆች፣ በበዓላት ወቅት እሱን ማስደሰት የሚችሉት እንዴት እንደሆነ ተመልከት።

ይሖዋ በጣም ይወድሃል (11:35)

በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ክርስቲያኖች የገና በዓልን ላለማክበር መርጠዋል። ስላደረጉት ውሳኔ ምን ይሰማቸዋል?

“የተሻለ ነገር አግኝተዋል” (መጠበቂያ ግንብ ታኅሣሥ 1, 2012)

a በዙሪያህ ያሉ ሰዎች በዓል በሚያከብሩበት ጊዜ ምን ማድረግ እንዳለብህ ለማወቅ ተጨማሪ ሐሳብ 5⁠ን ተመልከት።