በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 49

የቤተሰብህን ሕይወት አስደሳች ማድረግ የምትችለው እንዴት ነው?—ክፍል 1

የቤተሰብህን ሕይወት አስደሳች ማድረግ የምትችለው እንዴት ነው?—ክፍል 1

አዲስ ተጋቢዎች በሠርጋቸው ዕለት የሚሰማቸው ደስታ ለዘላለም እንደሚቀጥል ተስፋ ያደርጋሉ። ደግሞም ሊቀጥል ይችላል። የመጽሐፍ ቅዱስን ምክር ተግባራዊ ለማድረግ ከፍተኛ ጥረት የሚያደርጉ ብዙ ዓመታትን በትዳር ያሳለፉ ክርስቲያኖች ይህ ሊሆን እንደሚችል በገዛ ሕይወታቸው ተመልክተዋል።

1. መጽሐፍ ቅዱስ ለባሎች ምን ምክር ይሰጣል?

ይሖዋ ባሎችን የቤተሰብ ራስ አድርጎ ሾሟቸዋል። (ኤፌሶን 5:23⁠ን አንብብ።) ባሎች ቤተሰቡን የሚጠቅም ውሳኔ እንዲያደርጉ ይጠብቅባቸዋል። መጽሐፍ ቅዱስ ለባሎች “ሚስቶቻችሁን መውደዳችሁን ቀጥሉ” የሚል ምክር ይሰጣል። (ኤፌሶን 5:25) ይህ ምን ማለት ነው? አፍቃሪ የሆነ ባል በቤት ውስጥም ሆነ በሰዎች ፊት ለሚስቱ ደግነት ያሳያል። የሚስቱን ደህንነት ለመጠበቅ እንዲሁም አካላዊና ስሜታዊ ፍላጎቷን ለማሟላት የቻለውን ሁሉ ያደርጋል። (1 ጢሞቴዎስ 5:8) ከሁሉ በላይ ደግሞ የሚስቱን መንፈሳዊ ፍላጎት ለማሟላት ይጥራል። (ማቴዎስ 4:4) ለምሳሌ ያህል፣ ከሚስቱ ጋር ይጸልያል እንዲሁም መጽሐፍ ቅዱስ ያነብባል። አንድ ባል በፍቅር ተነሳስቶ ሚስቱን የሚንከባከብ ከሆነ ከይሖዋ ጋር ያለውን ወዳጅነት ጠብቆ ይኖራል።—1 ጴጥሮስ 3:7⁠ን አንብብ።

2. መጽሐፍ ቅዱስ ለሚስቶች ምን ምክር ይሰጣል?

የአምላክ ቃል “ሚስት ባሏን በጥልቅ ታክብር” ይላል። (ኤፌሶን 5:33) እንዲህ ማድረግ የምትችለው እንዴት ነው? ባለቤቷ ስላሉት ጥሩ ባሕርያት እንዲሁም እሷንም ሆነ ልጆቻቸውን ለመንከባከብ ስለሚያደርገው ጥረት ልታስብ ትችላለች። በተጨማሪም እሱ የሚያደርጋቸውን ውሳኔዎች በመደገፍ እንዲሁም እሱን ስታነጋግርም ሆነ ለሌሎች ስለ እሱ ስትናገር ደግነት የሚንጸባረቅባቸው ቃላት በመጠቀም ለባሏ አክብሮት እንዳላት ታሳያለች፤ ባለቤቷ ይሖዋን የማያመልክ ቢሆንም እንኳ እንዲህ ማድረጓ አስፈላጊ ነው።

3. ባልና ሚስት ትዳራቸውን ማጠናከር የሚችሉት እንዴት ነው?

መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ባለትዳሮች ሲናገር ‘ሁለቱ አንድ ሥጋ ይሆናሉ’ ይላል። (ማቴዎስ 19:5) በመሆኑም ባለትዳሮች ሊያራርቃቸው የሚችልን ማንኛውንም ነገር ሊያስወግዱ ይገባል። አዘውትረው ጊዜ ማሳለፍ እንዲሁም ሐሳባቸውንና ስሜታቸውን ግልጽ በሆነና ፍቅር በሚንጸባረቅበት መንገድ መነጋገር ይኖርባቸዋል። ከይሖዋ በቀር ማንም ሰው ወይም ምንም ነገር ከትዳር ጓደኛቸው እንዲበልጥባቸው መፍቀድ የለባቸውም። ከሌላ ከማንም ሰው ጋር ከልክ ያለፈ ቅርርብ እንዳይኖራቸው ልዩ ጥንቃቄ ያደርጋሉ።

ጠለቅ ያለ ጥናት

ትዳርን ለማጠናከር የሚረዱ የመጽሐፍ ቅዱስ ምክሮችን እንመለከታለን።

4. ባሎች—ሚስቶቻችሁን ውደዱ እንዲሁም ተንከባከቡ

መጽሐፍ ቅዱስ “ባሎች ሚስቶቻቸውን እንደ ገዛ አካላቸው አድርገው ሊወዷቸው ይገባል” ይላል። (ኤፌሶን 5:28, 29) ይህ ምን ማለት ነው? ቪዲዮውን ተመልከቱ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • አንድ ባል ሚስቱን እንደሚወድና እንደሚንከባከብ ማሳየት የሚችልባቸው አንዳንድ መንገዶች የትኞቹ ናቸው?

ቆላስይስ 3:12ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • ባሎች በትዳራቸው ውስጥ እነዚህን ባሕርያት ማሳየት የሚችሉት እንዴት ነው?

5. ሚስቶች—ባሎቻችሁን ውደዱ እንዲሁም አክብሩ

መጽሐፍ ቅዱስ አንዲት ሚስት ባሏ ይሖዋን የሚያመልክ ሆነም አልሆነ ልታከብረው እንደሚገባ ይናገራል። አንደኛ ጴጥሮስ 3:1, 2ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

  • ባልሽ ይሖዋን የማያገለግል ከሆነ ይሖዋን ማገልገል እንዲጀምር እንደምትፈልጊ ግልጽ ነው። ታዲያ ይህን ለማድረግ የሚረዳሽ ውጤታማ የሆነው ዘዴ የትኛው ነው? ነጋ ጠባ ለእሱ መስበክ ወይስ ጥሩ ምግባርና አክብሮት ማሳየት? ለምን?

አንድ ባልና ሚስት በጋራ ጥሩ ውሳኔ ላይ ሊደርሱ ይችላሉ። አንዳንድ ጊዜ ግን ሚስቶች በባሎቻቸው ሐሳብ አይስማሙ ይሆናል። እንዲህ ያለ ሁኔታ ሲያጋጥም ሚስቶች በእርጋታና በአክብሮት ሐሳባቸውን መግለጽ ይችላሉ፤ ሆኖም ይሖዋ ለቤተሰቡ የተሻለው ምን እንደሆነ የመወሰን ኃላፊነት የሰጠው ለባሎች እንደሆነ ማስታወስ ይኖርባቸዋል። በመሆኑም የባሎቻቸውን ውሳኔ ለመደገፍ የቻሉትን ሁሉ ሊያደርጉ ይገባል። እንዲህ ማድረጋቸው በቤታቸው ውስጥ ደስታ እንዲሰፍን ይረዳል። አንደኛ ጴጥሮስ 3:3-5ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • አንዲት ሚስት ለባሏ አክብሮት ስታሳይ ይሖዋ ምን ይሰማዋል?

6. በትዳራችሁ ውስጥ የሚያጋጥማችሁን ችግር መፍታት ትችላላችሁ

ፍጹም የሆነ ትዳር የለም። በመሆኑም ባለትዳሮች የሚያጋጥሟቸውን ችግሮች ለመፍታት ተባብረው መሥራት ይኖርባቸዋል። ቪዲዮውን ተመልከቱ ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

  • በቪዲዮው ላይ የታዩት ባልና ሚስት እየተራራቁ እንደመጡ የሚያሳዩ አንዳንድ ምልክቶች የትኞቹ ናቸው?

  • ትዳራቸውን ለማጠናከር ምን እርምጃዎች ወሰዱ?

አንደኛ ቆሮንቶስ 10:24ን እና ቆላስይስ 3:13ን አንብቡ። እያንዳንዱን ጥቅስ ካነበባችሁ በኋላ በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

  • በዚህ ጥቅስ ላይ የሚገኘውን ምክር ተግባራዊ ማድረግ ትዳርን ለማጠናከር የሚረዳው እንዴት ነው?

መጽሐፍ ቅዱስ አንዳችን ሌላውን ማክበር እንዳለብን ይናገራል። ሌሎችን ማክበር ደግነት ማሳየትንም ይጨምራል። ሮም 12:10ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

  • ባሎችም ሆኑ ሚስቶች የትዳር ጓደኛቸው ቀድሞ አክብሮት እስኪያሳያቸው መጠበቅ ይኖርባቸዋል? እንዲህ ብለህ የመለስከው ለምንድን ነው?

አንዳንዶች እንዲህ ይላሉ፦ “እኔና ባለቤቴ የቀድሞውን ያህል አንቀራረብም።”

  • መጽሐፍ ቅዱስ በዚህ ረገድ እንደሚረዳቸው ልታስረዳቸው የምትችለው እንዴት ነው?

ማጠቃለያ

አንድ ባልና ሚስት እርስ በርስ የሚዋደዱ፣ የሚከባበሩና የመጽሐፍ ቅዱስን ምክር ተግባራዊ የሚያደርጉ ከሆነ ደስተኛ መሆን ይችላሉ።

ክለሳ

  • ባሎች ትዳራቸው አስደሳች እንዲሆን ማድረግ የሚችሉት እንዴት ነው?

  • ሚስቶች ትዳራቸው አስደሳች እንዲሆን ማድረግ የሚችሉት እንዴት ነው?

  • ባለትዳር ከሆንክ ትዳርህን ለማጠናከር የሚረዳህ የትኛው የመጽሐፍ ቅዱስ ምክር ነው?

ግብ

ምርምር አድርግ

የቤተሰባችሁን ሕይወት አስደሳች ለማድረግ የሚረዷችሁ የትኞቹ ጠቃሚ ምክሮች ናቸው?

ደስተኛ ቤተሰብ ሊኖርህ ይችላል! (ብሮሹር)

ይህ የሙዚቃ ቪዲዮ በትዳር ውስጥ የአምላክን ምክር ተግባራዊ ማድረግ ምን ጥቅም እንደሚያስገኝ ያሳያል።

ተዋደን እንኑር (4:26)

ባል የቤተሰብ ራስ እንዲሆን የተሰጠውን ኃላፊነት ማክበር ምን ነገሮችን ይጨምራል?

“እናንት ሴቶች፣ ለራስነት ሥልጣን መገዛት ያለባችሁ ለምንድን ነው?” (መጠበቂያ ግንብ ግንቦት 15, 2010)

አንድ ባልና ሚስት፣ እስከ ፍቺ ያደረሷቸውን ከባድ ችግሮች መፍታት የቻሉት እንዴት ነው?

በአምላክ እርዳታ ትዳራችንን መልሰን ገነባን (5:14)