በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

‘መንግሥቲቱ ቀርባለች’

‘መንግሥቲቱ ቀርባለች’

ምዕራፍ 8

‘መንግሥቲቱ ቀርባለች’

1. በማቴዎስ 3:1–10 ላይ የሚገኙት የዮሐንስ ቃላት ወቅታዊ የነበሩት ለምንድን ነው?

እስቲ “አለቃው መሲሕ” መጀመሪያ በመጣበት ጊዜ ምን ምን እንዳደረገ ይበልጥ ሰፋ ባለ መንገድ እንመርምር። “መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ” የሚል እንግዳ የሆነ አዋጅ በመጀመሪያ ከመጥምቁ ዮሐንስ አፍ ይሰማ ጀመር። (ማቴዎስ 3:2) የወደፊቱ ንጉሥ የሚገለጥበት ጊዜ ተቃርቦ ነበር። ‘ሰባኛው ሳምንት’ ይኸውም ለሕዝቡ ልዩ ሞገስ የሚዘረጋበት “ሳምንት” ቀርቦ ነበር። ስለዚህ አይሁዶች በእርግጥ በአምላካቸው በይሖዋ የጽድቅ ሕጎች ላይ ለሠሩት ኃጢአት ንስሐ የሚገቡበት ከፍተኛ ጊዜ ነበር። አሁን እስራኤል ወደ ፍርድ ቀን የምትገባበት ጊዜ ደርሷል። ስለዚህ ዮሐንስ ንግግሩን በመቀጠል ግብዝ ለነበሩት የሕዝቡ የሃይማኖት መሪዎች እንግዲህ:- “እናንተ የእፉኝት ልጆች፣ ከሚመጣው ቁጣ እንድትሸሹ ማን አመለከታችሁ? እንግዲህ ለንስሐ የሚገባ ፍሬ አድርጉ፤ አሁንስ ምሳር በዛፎች ሥር ተቀምጧል፤ እንግዲህ መልካም ፍሬ የማያደርግ ዛፍ ሁሉ ይቆረጣል ወደ እሳትም ይጣላል።” — ማቴዎስ 3:7, 8, 10

2. (ሀ) የኢየሱስ ጥምቀት የተለየ የነበረው እንዴት ነው? (ለ) ኢየሱስ ‘ሥራውን እንደ ጀመረ’ ከምን ጋር መታገል አስፈለገው?

2 ኢየሱስ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ በመምጣት አጥማቂው ዮሐንስ እንዲያጠምቀው የጠየቀው በዚህን ጊዜ ነበር። ኢየሱስ ኃጢአት እንደሌለበት ዮሐንስ ያውቅ ስለነበር በመጀመሪያ አላጠምቅህም አለው። ሆኖም የኢየሱስ ጥምቀት ለየት ያለ ነበር። አምላኩ በምድር ላይ እንዲሠራው ለሰጠው ልዩ ሥራ ራሱን ለይሖዋ ማቅረቡን የሚያመለክት ነበር። ስለዚህ ኢየሱስ በውኃ መጠመቁ ተገቢ ነበር።

“ሲጸልይም ሰማይ ተከፈተ፣ መንፈስ ቅዱስም በአካል መልክ እንደ ርግብ በእርሱ ላይ ወረደ፤ የምወድህ ልጄ አንተ ነህ፣ በአንተ ደስ ይለኛል የሚል ድምፅም ከሰማይ መጣ። ኢየሱስም ሊያስተምር ሲጀምር ዕድሜው ሠላሳ ዓመት ያህል ሆኖት ነበር።”

መሲሕና የተሾመ ንጉሥ በመሆኑ ወዲያው የጥንቱ እባብ ዲያብሎስና በግብዝነት አምላክን እናገለግላለን የሚሉት የአይሁድ የሃይማኖት መሪዎች እርሱን ማጥቃት ጀመሩ። — ሉቃስ 3:21–23

3. ኢየሱስ ፈተና ሲመጣበት የተከተለው መንገድ አዳምና ሔዋን ከተከተሉት መንገድ የሚለየው እንዴት ነው?

3 “ኢየሱስም መንፈስ ቅዱስ ሞልቶበት ከዮርዳኖስ ተመለሰ፣ በመንፈስም ወደ ምድረ በዳ ተመርቶ አርባ ቀን በዲያብሎስ ተፈተነ።” (ሉቃስ 4:1, 2) ኢየሱስ ጊዜው ሲደርስ ዲያብሎስንና የእርሱን ክፉ “ዘር” የሚቀጠቅጥ አምላክ ይመጣል ሲል የተናገረለት “ዘር” መሆኑን ሰይጣን አውቋል። ሰይጣን ኢየሱስን የአምላክን ትእዛዝ እንዲያፈርስ በማድረግ የይሖዋን ዓላማ ሊያጨናግፍ ይችል ይሆንን? ኢየሱስ ለ40 ቀናት ምንም ምግብ አልበላም ነበር። ስለዚህ ዲያብሎስ የተራበውን ኢየሱስን በዚያ ደረቅ ምድረ በዳ የሚገኙ ጥቂት ድንጋዮችን ወደ ዳቦ እንዲቀይር ሐሳብ አቀረበለት። ኢየሱስ አሁን ተአምር የመሥራት ኃይል አለው፤ ይሁን እንጂ እንዲህ በማለት የይሖዋን ሕግ ጠቀሰ:-

“ሰው በእግዚአብሔር ቃል ሁሉ እንጂ በእንጀራ ብቻ አይኖርም ተብሎ ተጽፎአል።” (ማቴዎስ 4:1–4፤ ዘዳግም 8:3)

ለሕይወት አስፈላጊ የሆኑ የተትረፈረፉ ምግቦች በዙሪያቸው እያሉላቸው የተከለከለውን ፍሬ በመብላት የአምላክን ትእዛዝ ካፈረሱት ከሔዋንና ከባልዋ ከአዳም ምንኛ የተለየ አቋም ወሰደ!

4. ኢየሱስ ሁለተኛውን ፈተና ከተቋቋመበት መንገድ ምን ትምህርት ልናገኝ እንችላለን?

4 የኢየሱስ ትሕትናና በአባቱ ላይ ያለው ሙሉ ትምክህት የሚቀጥለውን ፈተና በተቋቋመበት መንገድ ታይቷል። ኢየሱስ የአምላክ ልጅ እንደመሆኑ ራሱን ትልቅ እንደሆነና ልዩ ክብር እንደሚገባው አድርጎ እንዲያስብ ለማድረግ ሰይጣን ሞክሮ ነበር። አዎን፣ ጉዳት እንዳይደርስበት የአምላክ መላእክት ከታች እንደሚቀልቡት እርግጠኛ ሆኖ ራሱን ከመቅደስ ጫፍ ወደ ታች በመወርወር አላስፈላጊ ሙከራ እንዲያደርግ ሐሳብ አቀረበለት። ሆኖም ኢየሱስ እንደገና የይሖዋን ሕግ በመጥቀስና እንደሚከተለው በማለት እንደዚህ ያለውን የሞኝነት ሐሳብ ሳይቀበለው ቀረ:-

“እግዚአብሔር አምላክህን አትፈታተነው ተብሎ ደግሞ ተጽፎአል።” (ማቴዎስ 4:5–7፤ ዘዳግም 6:16)

እስከዚህ ዘመን ድረስ ያሉትን የአምላክ አገልጋዮች ነን የሚሉትን ሁሉ የሚጠቅም ትምህርት እዚህ ላይ አለ:- ይኸውም ማንም ሰው በይሖዋ ፊት ባለው አቋም ተመክቶ ምንም ነገር አያድርግ የሚል ነው። በአምላክ ልንባረክ የምንችለው ባለፈው ጊዜ በሰጠነው አገልግሎት ወይም አሁን ባለን ሥልጣን መሠረት ሳይሆን በትሕትና ለዝግጅቶቹና ለትእዛዞቹ ጥልቅ አክብሮት እያሳየን እርሱን መታዘዛችንን በመቀጠል ነው። — ፊልጵስዩስ 2:5–7

5. (ሀ) ሦስተኛው ፈተና ያተኮረው በምን ከፍተኛ ጉዳይ ላይ ነበር? (ለ) ኢየሱስ መልስ ሲሰጥ እንደገና በአምላክ ሕግ የተጠቀመው እንዴት ነው? (ሐ) ይህስ ዛሬ ለእኛ ግሩም ምሳሌ የሚሆነው እንዴት ነው?

5 አሁን ደግሞ የመጨረሻውና ከፍተኛው ፈተና ሊመጣ ነው! ሰይጣን ከፍተኛ ጥያቄ በሆነው የመንግሥቱ ጥያቄ ረገድ ኢየሱስን ሊያሰናክለው ቢችል እንዴት ደስ ባለው! “ደግሞ ዲያብሎስ እጅግ ረጅም ወደ ሆነ ተራራ ወሰደው፣ የዓለምን መንግሥታት ሁሉ ክብራቸውን አሳይቶ:- ወድቀህ ብትሰግድልኝ ይህን ሁሉ እሰጥሃለሁ አለው።” ኢየሱስ ለብዙ መቶ ዘመናት ይሖዋ የወሰነውን ጊዜ መጠበቅ ሳያስፈልገው ያንኑ ዕለት በቀላሉ አቋሙን በማላላት ብቻ መላውን የሰው ዘር ዓለም ለመቆጣጠር እንደሚችል ሰይጣን ተከራከረው። ይሁን እንጂ ኢየሱስ እንደገና የይሖዋን ሕግ በመጥቀስ የሚከተለውን መልስ ሰጠ:-

“ሂድ አንተ ሰይጣን ለጌታ ለአምላክህ ስገድ እርሱንም ብቻ አምልክ ተብሎ ተጽፎአልና አለው።” (ማቴዎስ 4:8–10፤ ዘዳግም 6:13)

እዚህም ላይ በዛሬው ጊዜ ይሖዋን ለሚያመልኩት ሁሉ ኢየሱስ እንደገና እንዴት ያለ ግሩም ምሳሌ ተወላቸው! ጉዞው የቱንም ያህል ረጅም ቢመስል ለይሖዋ ቅዱስ አገልግሎት የሚያቀርቡ ሁሉ በሕይወታቸው ውስጥ ለአምላክ መንግሥት አንደኛ ቦታ መስጠታቸውን በምንም መንገድ ማቆም የለባቸውም። በፍቅረ ነዋይ በተጠመደው የሰይጣን ዓለም ውስጥ የራሳቸውን ትንንሽ “መንግሥታት” ለማቋቋም ፈጽሞ አይሞክሩ!

‘የዚህ ዓለም ክፍል አይደሉም’

6. (ሀ) በዚህ ጊዜ መንግሥቲቱ ቀርባ የነበረችው በምን መንገድ ነው? (ለ) 1 ጴጥሮስ 2:21⁠ን በሥራ ላይ ለማዋል ክርስቲያኖች የትኛውን የኢየሱስ ምሳሌ መከተል ይኖርባቸዋል?

6 ኢየሱስ የዲያብሎስን አሳሳች ፈተናዎች ካሸነፈ በኋላ ቀጥሎ የሆነው ነገር ምንድን ነው? የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገብ እንዲህ ሲል ይነግረናል:-

“ኢየሱስ:- መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ እያለ ይሰብክ ጀመር።”

መንግሥቲቱ ቀርባ የነበረው በምን መንገድ ነው? ንጉሡዋ እንዲሆን የተቀባው ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ በሰዎቹ መካከል በመገኘት ‘ያስተምርና የመንግሥቱን ምሥራች ይሰብክ ስለነበረ’ ነው። በሚሄድበት ቦታ ሁሉ እጅግ ብዙ ሕዝብ ይከተሉት ነበር። (ማቴዎስ 4:17, 23–25) ኢየሱስ ትምህርቱን የተቀበሉት ሰዎች ‘ልክ እርሱ የዓለም ክፍል እንዳልሆነ እነርሱም የዓለም ክፍል መሆን እንደማይገባቸው’ በጣም ግልጽ በሆነ መንገድ ተናግሮ ነበር። ከዓለም እንዲሁም ከዓመፅና ከብልግና መንገዶቹ መራቅ አለባቸው። ዛሬም ኢየሱስን መከተል የሚፈልጉ ሁሉ እንደዚሁ ማድረግ አለባቸው። — ዮሐንስ 17:14, 16፤ 1 ጴጥሮስ 2:21፤ በተጨማሪም ማቴዎስ 5:27, 28፤ 26:52 ተመልከት።

7. ኢየሱስ በዮሐንስ 8:44 ላይ የተናገረውን መሠረት በማድረግ በዛሬው ጊዜ የሃይማኖት መሪዎች የሚያስተምሯቸውን ትምህርቶች ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር እያስተያየን መመርመራችን በጣም አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው?

7 የሐሰት አምልኮን በተመለከተ ኢየሱስ በጊዜው ለነበሩት የሃይማኖት መሪዎች እንዲህ ብሎ ነገራቸው:- “እናንተ ከአባታችሁ ከዲያብሎስ ናችሁ የአባታችሁንም ምኞት ልታደርጉ ትወዳላችሁ። እርሱ ከመጀመሪያ ነፍሰ ገዳይ ነበረ፤ እውነትም በእርሱ ስለ ሌለ በእውነት አልቆመም። ሐሰትን ሲናገር ከራሱ ይናገራል፣ ሐሰተኛ የሐሰትም አባት ነውና።” (ዮሐንስ 8:44) በዚያን ጊዜ ተራዎቹ ሰዎች ራሳቸውን በአይሁድ ሃይማኖት ውስጥ ሰርጸው ከነበሩት የሐሰት ልማዶች (በኋላ በታልሙድ ውስጥ የተጨመሩ) ራሳቸውን ነፃ ማድረጋቸው በጣም አስፈላጊ ነበር። ዛሬም ቢሆን ልክ እንደነዚህ አይሁዶች ሕይወታቸውን በሙሉ ከቅድመ አያቶቻቸው ሲተላለፍ በመጣ ሃይማኖት ውስጥ ያኖሩ ሰዎች የሃይማኖት መሪዎቻቸው ተራ የሆነ የሰው ወግ ለማስተማር ሲሉ የአምላክን ቃል ‘ወደ ጎን’ አድርገው እንደሆነና እንዳልሆነ ለማወቅ መመርመራቸው በጣም አስፈላጊ ነው። — ማርቆስ 7:9–13

8, 9. (ሀ) ኢየሱስ ‘መንግሥቱ የዚህ ዓለም ክፍል እንዳልሆነች’ የተናገረው ለምንድን ነው? (ለ) ታዲያ እውነተኛ ክርስቲያኖች ለምን ስደት ይደርስባቸዋል? (ሐ) ድፍረት ሊኖራቸው የሚገባውስ ለምንድን ነው?

8 ኢየሱስ ለሞት ፍርድ በቀረበ ጊዜ በወቅቱ የነበሩትን የፖለቲካ መሪዎች በተመለከተ እንዲህ ሲል ተናግሮ ነበር:-

“መንግሥቴ ከዚህ ዓለም አይደለችም፤ መንግሥቴስ ከዚህ ዓለም ብትሆን፣ ወደ አይሁድ እንዳልሰጥ ሎሌዎቼ ይዋጉልኝ ነበር። አሁን ግን መንግሥቴ ከዚህ ዓለም አይደ ለችም።”

የኢየሱስ መንግሥት ምንጩ ከሰማይ ነው። ይህ መንግሥት ሥልጣኑን የሚያገኘው ከሰይጣን ሳይሆን ሉዓላዊ ገዥ ከሆነው ከይሖዋ አምላክ ነው። በዚህም ምክንያት ሰይጣን በምድራዊ ዘሩ ተጠቅሞ ኢየሱስንና ተከታዮቹን አሳዷል። — ዮሐንስ 18:36

9 ስለዚህ ኢየሱስ ለእውነተኛ ተከታዮቹ እንዲህ አላቸው:- “እርስ በርሳችሁ እንድትዋደዱ ይህን አዛችኋለሁ። ዓለም ቢጠላችሁ ከእናንተ በፊት እኔን እንደጠላኝ እወቁ። ከዓለምስ ብትሆኑ ዓለም የራሱ የሆነውን ይወድ ነበር፤ ነገር ግን እኔ ከዓለም መረጥኋችሁ እንጂ ከዓለም ስለ አይደላችሁ ስለዚህ ዓለም ይጠላችኋል።” (ዮሐንስ 15:17–19) ይሖዋን የሚያመልኩ ሰዎች ምግባረ ብልሹ ከሆነው ፖለቲካና በአሁኑ ጊዜ ተስፋፍቶ ከሚገኘው አመጽ ገለል ስለሚሉ እስከ አሁኑ ዘመን ድረስ መራራ ጥላቻና ስደት ይደርስባቸዋል። ይሁን እንጂ ዓለምን የሚያሸንፉ ሁሉ ከፍተኛ ሽልማት ይጠብቃቸዋል። ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ “በዓለም ሳላችሁ መከራ አለባችሁ፤ ነገር ግን አይዞአችሁ፤ እኔ ዓለምን አሸንፌዋለሁ” የሚል ማረጋገጫ ሰጥቷቸዋል። — ዮሐንስ 16:33

ንጉሣዊ ብቃቶች

10, 11. (ሀ) የዓለም መሪዎች መለኮታዊ የመግዛት መብት ተቀብለው እንደማይገዙ የሚያሳየው ምንድን ነው? (ለ) ከዚህ በተቃራኒ ኢየሱስ ለንግሥና ብቁ መሆኑን ያሳየው እንዴት ነው?

10 ዓለምን የሚያስተዳድር መሪ ምን ብቃቶች ማሟላት አለበት ትላለህ? በታሪክ መድረክ ላይ የታዩት አብዛኞቹ መሪዎች “ኃይለኞች”፣ ዕብሪተኞች፣ በትዕቢት የተነፉ ነበሩ። አብዛኛውን ጊዜም ከተራው ሕዝብ ፍላጎት ይልቅ የራሳቸውን ዝና የሚያስቀድሙ ሆነው ተገኝተዋል። አንዳንዶች ነገሥታት ታላላቅ ግዛቶችን አቋቁመናል በማለት በትምክህት ተናግረዋል፤ ውሎ አድሮ ግን ግዙፍ የነበሩት ግዛቶቻቸው ፈራርሰዋል። ይህም “እግዚአብሔር ቤትን ካልሠራ፣ ሠራተኞች በከንቱ ይደክማሉ” በማለት ንጉሥ ሰለሞን የተናገረው ቃል እውነት መሆኑን የሚያረጋግጥ ነው። (መዝሙር 127:1) እነዚህ “ነገሥታት” መለኮታዊ የመግዛት መብት ተቀብለው እንደማይገዙ በተግባራቸው አሳይተዋል። ሉዓላዊነታቸው ከይሖዋ አምላክ የተገኘ አልነበረም።

11 አምላክ የሾመው ንጉሥ ኢየሱስ ክርስቶስ ግን “ለእውነት፣ ለትሕትናና ለጽድቅ” ሲል ከጠላቶቹ ጋር ለመዋጋት እንደሚጋልብ በትንቢት ተነግሯል። ስለ እርሱ እንዲህ የሚል ተጽፎ እናገኛለን:- “ጽድቅን ወደድህ ዓመፃንም ጠላህ፤ ስለዚህ ከባልንጀሮችህ (ማለትም ከእርሱ በፊት ከነበሩት በዳዊት መሥመር ከተነሡት ነገሥታት) ይልቅ እግዚአብሔር አምላክህ የደስታን ዘይት ቀባህ።” (መዝሙር 45:4, 7) የይሖዋን ቅዱስ ስም ለሚያረክስና የአምላክን የጽድቅ ሥርዓቶች ለሚጥስ ለማንኛውም ነገር ባለው ጥላቻ ምክንያት ሰማያዊው ንጉሥ የተወሰነለት ጊዜ ሲደርስ የጽድቅ አገዛዝ እንዲመጣ ዝግጅት ለማድረግ ይህችን ምድር ከማንኛውም ዓይነት ክፋት ያጸዳታል። ኢየሱስ እንደዚህ ያለ መሪ ለመሆን ብቃቱን አሳይቷልን? በሚገባ አሳይቷል!

12. ኢየሱስ ቅዱስ አገልግሎት በማቅረብ በኩል ምን ምሳሌ ትቶልናል?

12 ኢየሱስ ፍጹም ሰው በነበረበት ጊዜ ለአምላክና ለጎረቤት ፍቅር በማሳየት በኩል ጥሩ አርአያ ሆኗል። ለይሖዋ የተወሰነው የአምላክ ሕዝብ ማለትም የእስራኤል ሕዝብ አባል እንደመሆኑ ኢየሱስ ሁለቱን ታላላቅ ትእዛዛት በማክበር ጥሩ ምሳሌ ትቷል። እንዲህ አለ:- “ከትእዛዛቱ ሁሉ ፊተኛይቱ:- እስራኤል ሆይ፣ ስማ፤ እግዚአብሔር አምላካችን አንድ እግዚአብሔር ነው፣ አንተም በፍጹም ልብህ በፍጹምም ነፍስህ በፍጹምም አሳብህ በፍጹምም ኃይልህ እግዚአብሔር አምላክህን ውደድ የምትል ናት። ፊተኛይቱ ትእዛዝ ይህች ናት። ሁለተኛይቱም:- ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ የምትል እርስዋን የምትመስል ይህች ናት።” (ማርቆስ 12:29–31፤ ዘዳግም 6:4, 5) ኢየሱስ ጉልበቱን ምንም ሳይቆጥብ ይሖዋን አገልግሏል፤ ባልንጀሮቹ የሆኑትንም አይሁዶች አስተምሯል። እነዚህ ሰዎች የበለጠ እንዲያስተምራቸው ፈልገው እንዲቆይላቸው በጠየቁት ጊዜ እንዲህ አላቸው:-

“ስለዚህ ተልኬአለሁና ለሌሎቹ ከተማዎች ደግሞ የእግዚአብሔርን መንግሥት ወንጌል እሰብክ ዘንድ ይገባኛል።” (ሉቃስ 4:43)

ኢየሱስ ቅዱስ አገልግሎት ሲያቀርብ ብርቱ ሠራተኛ መሆኑን አሳይቷል፤ ይህም እውነተኛ ክርስቲያኖች በሙሉ ሊከተሉት የሚገባ ጥሩ ምሳሌ ነው። — ከዮሐንስ 5:17 ጋር አወዳድር።

13, 14. (ሀ) ኢየሱስ ሰዎችን እንዴት ይመለከት ነበር? (ለ) ለስብከት ወደየቦታው ይሄድ የነበረው ለምንድን ነው? ሌሎችንስ ለምን ላከ? (ሐ) በመንግሥቱ ግዛት ሥር የሰው ልጆች ምን ዓይነት አመራር እንደሚኖር ሊጠብቁ ይችላሉ?

13 ኢየሱስ አፍቃሪና ርኅሩኅ መሆኑን አሳይቷል። ሃይማኖታዊ ጨቋኞች በሕዝቡ ላይ ከጫኑት ከባድ ሸክም ተገላግለው ለማየት ከልቡ ይመኝ ነበር። ስለዚህም ስለ መንግሥቱ ነገራቸው፤ ደቀ መዛሙርቱንም እንዲህ በማለት ላካቸው:-

“ሄዳችሁም:- መንግሥተ ሰማያት ቀርባለች ብላችሁ ስበኩ።” — ማቴዎስ 9:35 እስከ 10:7

14 ይህ እጩ ንጉሥ ለሕዝቡ እንዲህ በማለት ግብዣ አቀረበ:- “እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ፣ ወደ እኔ ኑ፣ እኔም አሳርፋችኋለሁ። ቀንበሬን በላያችሁ ተሸከሙ ከእኔም ተማሩ፣ እኔ የዋህ በልቤም ትሑት ነኝና፣ ለነፍሳችሁም ዕረፍት ታገኛላችሁ፤ ቀንበሬ ልዝብ ሸክሜም ቀሊል ነውና።” (ማቴዎስ 11:28–30) ኢየሱስ የአምላክ ሰማያዊ ንጉሥ በመሆን በሁሉም የሰው ዘር ላይ በሚገዛበት ጊዜ ይህን የመሰለ ርኅራኄ ያሳያል። በምድር ላይ በነበረበት ጊዜ እንዳደረገውም በመንግሥቱ አብረውት የሚገዙት ሰዎች በእርግጥ የሚያስፈልጋቸውን እፎይታና የደግነት አመራር ለመስጠት እንዲደራጁ ያደርጋል። በኢየሱስ መንግሥታዊ አገዛዝ ሥር በምድር ላይ የሚኖሩ ሁሉ ለነፍሳቸው ዕረፍትን እንደሚያገኙ የተረጋገጠ ነው።

እንከን የሌለው አቋም አሳይቷል

15. ኢየሱስ ሰይጣን ላነሣው ግድድር የተሟላ መልስ የሰጠው እንዴት ነው?

15 ከሁሉም በላይ የወደፊቱ የሰው ዘር ንጉሥ ጭካኔ በተሞላበት መንገድ በመከራ እንጨት ላይ እስከሚሞት ድረስ ለሰማያዊ አባቱ ምንም እንከን የማይወጣለት አቋምና ታዛዥነት አሳይቷል። የሚገደልበት ሰዓት እየቀረበ ሲመጣ ኢየሱስ “አባት ሆይ፣ ስምህን አክብረው” በማለት ወደ ይሖዋ ጸልዮ ነበር። የይሖዋም ድምፅ ከሰማይ:- “አከበርሁት ደግሞም አከብረዋለሁ” በማለት መልስ ሰጠ። ኢየሱስ የአባቱን ስም በመቀደስ ሰይጣን ላቀረበው ግድድር የተሟላ መልስ ሰጠ። በዚህም አንድ ፍጹም የሆነ ሰው ጠላት ያመጣበትን ማንኛውንም ፈተና ተቋቁሞ ለአምላክ የታመነ ሆኖ መመላለስ እንደሚችል አሳይቷል። በዚህም ምክንያት ኢየሱስ እንዲህ ለማለት ችሏል:- “አሁን የዚህ ዓለም ፍርድ ደርሶአል፤ አሁን የዚህ ዓለም ገዥ (ሰይጣን) ወደ ውጭ ይጣላል” ይኸውም ውሸታም መሆኑ ሙሉ በሙሉ ተረጋግጦ ይዋረዳል ማለት ነው። የአይሁድ ሃይማኖታዊ መሪዎች ‘የእባቡ ዘር’ በመሆን የአምላክ ሴት መሰል ድርጅት ባፈራው “ዘር” ላይ የሚያሠቃይ ‘የሰኮና’ ቁስል ያደርሱበታል፤ ይሁን እንጂ አምላክ ውድ ልጁን ወደ መንፈሳዊ ሕይወት ከሞት ያስነሣዋል። — ዘፍጥረት 3:15፤ ዮሐንስ 12:27–31

16, 17. (ሀ) በወደፊቱ የምድር ንጉሥ ላይ ጠንካራ ትምክህት ሊኖረን የሚችለው ለምንድን ነው? (ለ) ገነት የሆነች ምድር ስለመምጣትዋ የተሰጠው ተስፋ ተጨባጭ መሆኑን ቅዱሳን ጽሑፎች የሚያሳዩት እንዴት ነው? (ሐ) ፊተኛው አኗኗርህ ለዚያ ተስፋ ለመብቃት ከመጣጣር ሊያግድህ ይገባልን?

16 ኢየሱስ ለጽድቅ ያሳየው ፍቅር፣ ለዓመፃ የነበረው ጥላቻ፣ ለሰው ዘር ያደረበት ኃይለኛ ፍቅር ከሁሉም በላይ ደግሞ የይሖዋ ስም እንዲከበር የአባቱን ፈቃድ ለማድረግ የማያወላውል ታዛዥነት ማሳየቱ፣ እነዚህ ሁሉ ጠባዮች ይህ ታማኝ ልጅ የወደፊቱ የምድር ንጉሥ ለመሆን ብቃት ያለው መሆኑን ያረጋግጣሉ። ይህን ለመሰለ ንጉሥ ደስተኛ ተገዥ በመሆን ወደ ዘላለም ሕይወት መግባት አትፈልግምን?

17 እስከ አሁን ድረስ አኗኗርህ የቱንም ያህል ጥሩ ወይም መጥፎ ቢሆን ክብር በተላበሰች ምድር ላይ የዘላለም ሕይወት ለማግኘት ትችላለህ። ሌላው ቀርቶ ከኢየሱስ ጋር የተሰቀለው ንስሐ የገባ ሌባም እንደዚህ ያለውን ትንሣኤ እንደሚያገኝ ተስፋ ተሰጥቶታል! ኢየሱስን “በመንግሥትህ በመጣህ ጊዜ አስበኝ” ባለው ጊዜ ኢየሱስ “ዛሬ እውነት እልሃለሁ፤ ከእኔ ጋር በገነት ትሆናለህ አለው።” (ሉቃስ 23:42, 43 አዓት) በቅርቡ ገነትን በተጨባጭ እናያታለን። ታዲያ አንተም ለመንግሥቲቱና ለበረከቶቿ መምጣት ራስህን እያዘጋጀህ ነውን?

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 77 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

በምድር ላይ ከኖሩት ሁሉ የሚበልጥ ታላቅ ሰው

እጩ ንጉሥ በመሆን እስከ ሞት ድረስ ከንጹሕ አቋም ፍንክች እንደማይል አረጋገጠ። በፈሰሰው ደሙም የሰውን ልጆች ከኃጢአትና ከሞት ዋጃቸው