በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የመጀመሪያውን ፍቅርህን መልሰህ አቀጣጥል!

የመጀመሪያውን ፍቅርህን መልሰህ አቀጣጥል!

ምዕራፍ 7

የመጀመሪያውን ፍቅርህን መልሰህ አቀጣጥል!

ኤፌሶን

1. የመጀመሪያው የኢየሱስ መልእክት የተላከው ለየትኛው ጉባኤ ነበር? የበላይ ተመልካቾቹንስ ያሳሰበው ስለ ምን ነገር ነው?

ኢየሱስ በመጀመሪያ መልእክቱን የላከው በዘመኑ ሞቅ ያለች የወደብ ከተማ በነበረችውና በታናሽቱ እስያ በጳጥሞስ ደሴት አጠገብ በምትገኘው የኤፌሶን ከተማ ለነበረው ጉባኤ ነው። ዮሐንስን እንዲህ ሲል አዘዘው:- “በኤፌሶን ወዳለው ወደ ቤተ ክርስቲያን መልአክ እንዲህ ብለህ ጻፍ:- በቀኝ እጁ ሰባቱን ከዋክብት የያዘው በሰባቱም የወርቅ መቅረዞች መካከል የሚሄደው እንዲህ ይላል:-” (ራእይ 2:1) ኢየሱስ በሌሎቹ ስድስት መልእክቶች እንዳደረገው እዚህም ላይ የሥልጣን ደረጃውን የሚያሳይ መግለጫ ሰጠ። ሁሉም ሽማግሌዎች በራሱ የበላይ ተቆጣጣሪነት ሥር እንደሚገኙና እርሱም ጉባኤዎችን ሁሉ እንደሚመረምር ለኤፌሶን የበላይ ተመልካቾች አስገነዘባቸው። እስካለንበት ዘመን ድረስ ሽማግሌዎችን በመቆጣጠርና ከጉባኤው ጋር የሚተባበሩትን ሁሉ እረኛ ሆኖ በደግነት በመጠበቅ በራስነት ሥልጣኑ ሲሠራ ቆይቶአል። ጊዜያት እያለፉ በሄዱ መጠን ብርሃኑ በበለጠ ድምቀት እንዲበራ ለማስቻል የጉባኤዎችን አደረጃጀት ማስተካከል አስፈልጎታል። አዎ፣ በአምላክ በጎች ላይ የተሾመው ዋነኛ እረኛ ኢየሱስ ነው።—ማቴዎስ 11:28-30፤ 1 ጴጥሮስ 5:2-4

2. (ሀ) ኢየሱስ የኤፌሶንን ጉባኤ ያመሰገነው ስለ ምን ጥሩ ነገሮች ነው? (ለ) የኤፌሶን ሽማግሌዎች የትኛውን የሐዋርያው ጳውሎስን ምክር ፈጽመው እንደነበረ ግልጽ ነው?

2 ከዚህ በኋላ ኢየሱስ ለሁሉም ምሳሌ ተወላቸው። ከሰባቱ መልእክቶቹ በሁለቱ ላይ ግን ሞቅ ያለ የምሥጋና ቃል በማሰማት መልእክቱን ይከፍታል። ለኤፌሶን ክርስቲያኖች የሚከተለውን መልእክት ላከላቸው:- “ሥራህንና ድካምህን ትዕግሥትህንም አውቃለሁ፤ ክፉዎችንም ልትታገሥ እንዳትችል፣ እንዲሁም ሳይሆኑ፣ ሐዋርያት ነን የሚሉትን መርምረህ ሐሰተኞች ሆነው እንዳገኘሃቸው አውቃለሁ። ታግሰህማል፣ ስለ ስሜም ብለህ ጸንተህ አልደከምህም።” (ራእይ 2:2, 3) ከዓመታት በፊት ጳውሎስ የኤፌሶንን ሽማግሌዎች እንደ “ጨካኝ ተኩላዎች” ያሉ ከሃዲዎች ተነስተው መንጋውን እንደሚበጠብጡና ሽማግሌዎቹም የጳውሎስን የትጋት ምሳሌ በመከተል ነቅተው መጠበቅ እንደሚኖርባቸው አስጠንቅቆአቸው ነበር። (ሥራ 20:29, 31) አሁን ደግሞ ኢየሱስ ስለ ድካማቸውና ስለ ጽናታቸው እንዲሁም ሳይሰለቹ ስለመትጋታቸው ስላመሰገናቸው ይህንን የጳውሎስን ምክር ሠርተውበታል ማለት ነው።

3. (ሀ) “ሐሰተኛ ሐዋርያት” በዘመናችን ታማኞችን ለማሳት የሞከሩት እንዴት ነበር? (ለ) ጴጥሮስ ስለ ከሃዲዎች ምን ማስጠንቀቂያ ሰጥቶ ነበር?

3 በጌታ ቀንም “ደቀ መዛሙርትን ወደ ኋላቸው ይስቡ ዘንድ ጠማማ ነገርን የሚናገሩ ሰዎች” “ሐሰተኛ ሐዋርያት” ተነስተዋል። (2 ቆሮንቶስ 11:13፤ ሥራ 20:30፤ ራእይ 1:10) እነዚህ ከሃዲዎች እርስ በርሳቸው የሚጋጩት የተለያዩ ኑፋቄያዊ ሃይማኖቶች በሙሉ የየራሳቸው የሆነ ጥሩ ነገር አላቸው ይላሉ። አምላክ ድርጅት እንዳለው አያምኑም። ኢየሱስ በ1914 ንጉሣዊ ሥልጣን መቀበሉን ይክዳሉ። በ⁠2 ጴጥሮስ 3:3, 4 ላይ የሚገኘውን ትንቢት ፈጽመዋል። “በመጨረሻው ዘመን እንደራሳቸው ምኞት የሚመላለሱ ዘባቾች በመዘበት እንዲመጡ ይህን በፊት እወቁ፤ እነርሱም:- ‘የመምጣቱ የተስፋ ቃል ወዴት ነው? አባቶች ከሞቱባት ጊዜ ከፍጥረት መጀመሪያ ይዞ ሁሉ እንዳለ ይኖራልና’ ይላሉ።”

4. (ሀ) የዘባቾች ኩራትና ዓመፀኛነት የተጋለጠው እንዴት ነበር? (ለ) ዛሬ ክርስቲያኖች እንደ ኤፌሶን ክርስቲያኖች መሆናቸውን የሚያሳዩት በሐሰተኛ ተቃዋሚዎች ላይ ምን ዓይነት እርምጃ በመውሰድ ነው?

4 እነዚህ ዘባቾች እምነትን ለሕዝብ የማስታወቅን ጉዳይ አይቀበሉም። (ሮሜ 10:10) የሕዝበ ክርስትናን ቀሳውስት ድጋፍና የጋዜጦችንና የቴሌቪዥን ጣቢያዎችን እርዳታ በመጠየቅ ስለቀድሞ ባልንጀሮቻቸው የሐሰት ዜና አሰራጭተዋል። ታማኝ የሆኑ ሁሉ የእነዚህ አሳቾች ንግግርና ምግባር እውነተኝነት የሌለበት መሆኑን ለመገንዘብ ብዙ ጊዜ አልፈጀባቸውም። የዛሬዎቹ ክርስቲያኖች ልክ እንደ ኤፌሶን ክርስቲያኖች እነዚህን ‘ክፉ ሰዎች ለመታገስ ስለማይችሉ’ አስወግደዋቸዋል። *

5. (ሀ) የኤፌሶን ክርስቲያኖች ምን ድካም እንደነበራቸው ኢየሱስ ተናገረ? (ለ) የኤፌሶን ክርስቲያኖች የትኛውን ቃል ማስታወስ ይገባቸው ነበር?

5 አሁን ግን ኢየሱስ ከሰባቱ ጉባኤዎች ለአምስቱ እንዳደረገው አንድ ከባድ ችግር እንዳለባቸው ጠቆማቸው። ለኤፌሶን ሰዎች እንዲህ አላቸው:- “ዳሩ ግን የምነቅፍብህ ነገር አለኝ፣ የቀደመውን ፍቅርህን ትተሃልና።” (ራእይ 2:4) ጳውሎስ ከ35 ዓመታት በፊት ‘አምላክ እኛን ስለወደደበት ታላቅ ፍቅር’ በመናገር “እንግዲህ እንደተወደዱ ልጆች እግዚአብሔርን የምትከተሉ [“የምትመስሉ፣” NW] ሁኑ። ክርስቶስም ደግሞ እንደወደዳችሁ . . . በፍቅር ተመላለሱ” ሲል መክሮአቸው ስለነበረ በዚህ ረገድ ጉድለት ማሳየት አልነበረባቸውም። (ኤፌሶን 2:4፤ 5:1, 2) ከዚህም በላይ የሚከተለው የኢየሱስ ቃል በማይፋቅ ሁኔታ በልባቸው ላይ መጻፍ ነበረበት። “እግዚአብሔር [“ይሖዋ፣” NW] አምላካችን አንድ እግዚአብሔር [“ይሖዋ፣” NW] ነው። አንተም በፍጹም ልብህ፣ በፍጹምም ነፍስህ፣ በፍጹምም አሳብህ፣ በፍጹምም ኃይልህ እግዚአብሔር [“ይሖዋ፣” NW] አምላክህን ውደድ።” (ማርቆስ 12:29-31) የኤፌሶን ክርስቲያኖች ይህ የመጀመሪያ ፍቅራቸው ጠፍቶባቸው ነበር።

6. (ሀ) በጉባኤው ውስጥ የቆየንም ሆንን አዳዲሶች ከምን ዓይነት አደጋና ዝንባሌ መጠንቀቅ ይኖርብናል? (ለ) ለአምላክ ያለን ፍቅር ምን እንድናደርግ ሊገፋፋን ይገባል?

6 በጉባኤው ውስጥ የቆየንም ሆንን አዳዲሶች፣ ለይሖዋ የነበረን የመጀመሪያ ፍቅር እንዳይጠፋብን መጠንቀቅ ይኖርብናል። የመጀመሪያ ፍቅራችን ሊጠፋ የሚችለው እንዴት ነው? በሥጋዊ ሥራችን ልንተሳሰር እንችላለን። በሕይወታችን ውስጥ ትልቁን ቦታ ብዙ ገንዘብ ለማካበት ወይም ደስታ ለማሳደድ ልንሰጥ እንችላለን። ይህን ስናደርግ መንፈሳዊ አስተሳሰብ ያለን ሰዎች መሆናችን ቀርቶ ሥጋዊ አስተሳሰብ ያለን እንሆናለን። (ሮሜ 8:5-8፤ 1 ጢሞቴዎስ 4:8፤ 6:9, 10) ለይሖዋ ያለን ፍቅር እንዲህ ያለውን ዝንባሌ እንድናስተካክልና ለራሳችን ‘በሰማይ የሚሆን መዝገብ ለማከማቸት’ ‘ከሁሉ አስቀድመን የእግዚአብሔርን ጽድቅና መንግሥት እንድንፈልግ’ ሊገፋፋን ይገባል።—ማቴዎስ 6:19-21, 31-33

7. (ሀ) ለይሖዋ የምናቀርበው አገልግሎት በምን ስሜት ተገፋፍተን የምንፈጽመው መሆን ይኖርበታል? (ለ) ዮሐንስ ስለ ፍቅር ምን ተናግሮ ነበር?

7 ለይሖዋ የምንሰጠው አገልግሎት ሁልጊዜ ለእርሱ ባለን ጥልቅ ፍቅር ተገፋፍተን የምናቀርበው ይሁን። ይሖዋና ክርስቶስ ላደረጉልን ነገሮች የጋለ አድናቆት ይኑረን። ዮሐንስ ራሱ ቆየት ብሎ እንደጻፈው “እግዚአብሔር እርሱ ራሱ እንደ ወደደን ስለ ኃጢአታችንም ማስተሰሪያ ይሆን ዘንድ ልጁን እንደ ላከ እንጂ እኛ እግዚአብሔርን እንደ ወደድነው አይደለም።” ዮሐንስ በመቀጠል “እግዚአብሔር ፍቅር ነው፣ በፍቅርም የሚኖር በእግዚአብሔር ይኖራል፣ እግዚአብሔርም በእርሱ ይኖራል” ይለናል። ለይሖዋ፣ ለጌታ ኢየሱስ ክርስቶስና ሕያው ለሆነው የአምላክ ቃል ያለን ፍቅር አይቀዝቅዝ። ይህንንም ፍቅራችንን የምናሳየው ለአምላክ በምናቀርበው የቅንዓት አገልግሎት ብቻ ሳይሆን “እግዚአብሔርንም የሚወድ ወንድሙን ደግሞ እንዲወድ ይህች ትዕዛዝ ከእርሱ አለችን” የሚለውን ቃል በመታዘዝ ጭምር ነው።—1 ዮሐንስ 4:10, 16, 21፤ ዕብራውያን 4:12፤ በተጨማሪም 1 ጴጥሮስ 4:8፤ ቆላስይስ 3:10-14፤ ኤፌሶን 4:15ን ተመልከት።

“የቀደመውንም ሥራህን አድርግ”

8. ኢየሱስ የኤፌሶን ክርስቲያኖች ምን ማድረግ እንደሚኖርባቸው ተናገረ?

8 የኤፌሶን ክርስቲያኖች ተስፋቸውን ለማጣት ካልፈለጉ የቀድሞ ፍቅራቸውን መልሰው ማቀጣጠል ነበረባቸው። በዚህም ምክንያት ኢየሱስ እንዲህ አላቸው:- “እንግዲህ ከወዴት እንደ ወደቅህ አስብ ንስሐም ግባ የቀደመውንም ሥራህን አድርግ፤ አለዚያ እመጣብሃለሁ፣ ንስሐም ባትገባ መቅረዝህን ከስፍራው እወስዳለሁ።” (ራእይ 2:5) በኤፌሶን ጉባኤ የነበሩት ክርስቲያኖች ይህን ቃል የተቀበሉት እንዴት ነበር? እንዴት እንደተቀበሉት አናውቅም። ንስሐ ገብተው ለይሖዋ የነበራቸውን ፍቅር መልሰው ለማቀጣጠል ችለው እንደነበረ ተስፋ እናደርጋለን። ይህን ባያደርጉ ግን መብራታቸው ጠፍቶ መቅረዛቸውም ከቦታው ይወገዳል። የእውነትን ብርሃን የማብራት መብታቸውን ያጣሉ።

9. (ሀ) ኢየሱስ የኤፌሶን ክርስቲያኖችን የሚያበረታቱ ምን ቃላት ተናገረ? (ለ) ከዮሐንስ ዘመን በኋላ የነበሩት ጉባኤዎች ኢየሱስ ለኤፌሶን ጉባኤ የሰጠውን ምክር ሳይፈጽሙ የቀሩት እንዴት ነበር?

9 ይሁን እንጂ ኢየሱስ ገና ለኤፌሶን ክርስቲያኖች የሚናገረው የሚያበረታታ ቃል ነበረው። እንዲህም አለ:- “ነገር ግን ይህ አለህ፣ እኔ ደግሞ የምጠላውን የኒቆላውያንን ሥራ ጠልተሃልና።” (ራእይ 2:6) ሌላው ቢቀር ኢየሱስ ይጠላ የነበረውን ኑፋቄያዊ ክፍፍል ይጠሉ ነበር። ይሁን እንጂ ዘመናት እያለፉ በሄዱ መጠን ብዙ ጉባኤዎች ይህን የኢየሱስ ቃል ችላ ማለት ጀመሩ። ለይሖዋ፣ ለእውነትና እርስ በርሳቸው የነበራቸው ፍቅር እየጎደለ በመሄዱ ወደ መንፈሳዊ ጨለማ ዘቀጡ። እርስ በርሳቸው በሚጣሉ እጅግ ብዙ ኑፋቄዎች ተከፋፈሉ። ለይሖዋ ፍቅር ያልነበራቸው “ክርስቲያን” የመጽሐፍ ቅዱስ ገልባጮች የአምላክን ስም ከግሪክኛ የመጽሐፍ ቅዱስ ቅጂዎች ፈጽመው አጠፉ። በተጨማሪም ፍቅር የጎደላቸው መሆናቸው በክርስትና ስም እንደ ሲኦል እሳት፣ እንደ መንጽሔና እንደ ሥላሴ የመሰሉትን ባቢሎናዊና ግሪካዊ መሠረተ ትምህርቶች እስከ ማስተማር አደረሳቸው። ለአምላክና ለእውነት ፍቅር ስለሌላቸው ክርስቲያን ነን ከሚሉት መካከል አብዛኞቹ የአምላክን መንግሥት ምሥራች መስበካቸውን አቆሙ። የራሱን መንግሥት በዚህች ምድር ላይ ባቋቋመው ራስ ወዳድ የካህናት ክፍል መገዛት ጀመሩ።—ከ⁠1 ቆሮንቶስ 4:8 ጋር አወዳድር።

10. በ1918 በሕዝበ ክርስትና ውስጥ የነበረው ሃይማኖታዊ ሁኔታ እንዴት ያለ ነበር?

10 በ1918 ፍርድ ከአምላክ ቤት በጀመረ ጊዜ መናፍቃን የሆኑት የሕዝበ ክርስትና ቀሳውስት በመጀመሪያው የዓለም ጦርነት ወቅት በሁለቱም ተዋጊ ክፍሎች የሚገኙ ካቶሊኮችና ፕሮቴስታንቶች እርስ በርሳቸው እንዲተራረዱ በማደፋፈር ጦርነቱን በግልጽ ደግፈው ነበር። (1 ጴጥሮስ 4:17) የሕዝበ ክርስትና ሃይማኖቶች እንደ ኤፌሶን ክርስቲያኖች የኒቆላውያንን ሥራ ከመጥላት ይልቅ እርስ በርሳቸው በሚጻረሩ አምላክ የለሽ መሠረተ ትምህርቶች ተውጠዋል። ቀሳውስቶቻቸውም እጣቸውን ከዚህ ዓለም ጋር ጥለዋል። ኢየሱስ ግን ደቀ መዛመርቱ ሁሉ የዚህ ዓለም ክፍል እንዳይሆኑ አስጠንቅቆ ነበር። (ዮሐንስ 15:17-19) ጉባኤዎቻቸው የመጽሐፍ ቅዱስ አጠቃላይ መልእክት ስለሆነው ስለ አምላክ መንግሥት ደንቆሮዎች ስለሆኑ የቅዱሳን ጽሑፎችን እውነት የሚፈነጥቁ መቅረዞች አልሆኑም። አባሎቻቸውም ቢሆኑ የይሖዋ መንፈሳዊ ቤተ መቅደስ ክፍል አይደሉም። ወንዶችና ሴቶች መሪዎቻቸው “ኮከቦች” አይደሉም። እንዲያውም “የዓመፅ ሰው” ክፍል መሆናቸው በግልጽ ታይቶአል።—2 ተሰሎንቄ 2:3፤ ሚልክያስ 3:1-3

11. (ሀ) በ1918 ኢየሱስ ለኤፌሶን ክርስቲያኖች የሰጠውን ምክር ሲፈጽም የተገኘው የትኛው የክርስቲያኖች ቡድን ነበር? (ለ) የዮሐንስ ክፍል ከ1919 ጀምሮ ምን ሲያደርግ ቆይቶአል?

11 የዮሐንስ ክፍል የሆኑት ቅቡዓን ግን ለይሖዋና ለእውነት ባላቸው ፍቅር ተሞልተው ትርምስ ከበዛበት ከአንደኛው የዓለም ጦርነት ዓመታት ብቅ አሉ። ይህም ፍቅራቸው በሚያንገበግብ ቅንዓት ይሖዋን እንዲያገለግሉት አነሳስቶአቸዋል። የመጀመሪያው የመጠበቂያ ግንብ ማህበር ፕሬዚደንት የነበረው ቻርልስ ቴዝ ራስል በ1916 ከሞተ በኋላ እርሱን እንደ ጣዖት በማምለክ በመካከላቸው ኑፋቄ ለማቋቋም የሞከሩትን ሰዎች ተቃውመዋል። ይህ የክርስቲያኖች ቡድን በስደትና በመከራ ከተገሰጸና ከታረመ በኋላ ከጌታው ዘንድ “ጎሽ፣ አበጀህ” የሚል የምሥጋና ቃልና ወደ ጌታው ደስታ እንዲገባ ግብዣ ቀርቦለታል። (ማቴዎስ 25:21, 23) ኢየሱስ በማይታይ ሁኔታ በመንግሥታዊ ስልጣኑ መገኘቱን ያመለክታሉ ብሎ የተናገራቸው ምልክቶች ሁሉ መፈጸማቸውን ከራሳቸው ተሞክሮና ከዓለም ሁኔታ ተገንዝበዋል። ከ1919 ጀምሮም “ለአሕዛብም ሁሉ ምስክር እንዲሆን ይህ የመንግሥት ወንጌል በዓለም ሁሉ ይሰበካል፣ በዚያን ጊዜም መጨረሻው ይመጣል” የሚለውን ትንቢት በመፈጸም ሥራ ለመካፈል ተነሳስተዋል። (ማቴዎስ 6:9, 10፤ 24:3-14) ለይሖዋ የነበራቸው ፍቅር ጎድሎ የተገኘበት ሁኔታ ቢኖር እንኳን ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ተቀጣጥሎ መንደድ ጀመረ።

12. (ሀ) በ1922 በተደረገ ታሪካዊ ስብሰባ ላይ ምን ጥሪ ቀረበ? (ለ) በ1931 እውነተኛ ክርስቲያኖች የትኛውን ስም ተቀበሉ? ከምንስ ነገር ንስሐ ገቡ?

12 ከእነዚህ መካከል 18,000 የሚያክሉ ክርስቲያኖች በተገኙበትና በሴዳር ፖይንት ኦሃዮ ዩ.ኤስ.ኤ ከመስከረም 5-13, 1922 በተደረገው ታሪካዊ ስብሰባ ላይ የሚከተለው ጥሪ ቀርቦ ነበር። “እናንት፣ የልዑል አምላክ ልጆች ሆይ! ወደ መስኩ ተመለሱ። . . . ዓለም በሞላ ይሖዋ፣ አምላክ እንደሆነና ኢየሱስ ክርስቶስ የጌቶች ጌታና የነገሥታት ንጉሥ እንደሆነ ማወቅ ይኖርበታል። . . . ስለዚህ ንጉሡንና መንግሥቱን አስታውቁ፣ አስታውቁ፣ አስታውቁ።” ታላቅና ውድ የሆነው የይሖዋ ስም ከፍተኛ ቦታ ማግኘት ጀመረ። በ1931 እነዚህ ክርስቲያኖች በኮሎምቦስ ኦሃዮ ዩ.ኤስ.ኤ ትልቅ ስብሰባ አድርገው የይሖዋ ምሥክሮች የሚለውን አምላክ ራሱ በኢሳይያስ ትንቢት የገለጸውን ስም በደስታ ተቀበሉ። (ኢሳይያስ 43:10, 12) የድርጅቱ ዋነኛ መጽሔትም ከመጋቢት 1, 1939 እትሙ ጀምሮ ስሙ ተለውጦ የይሖዋን መንግሥት የሚያስታውቅ መጠበቂያ ግንብ መባል ጀመረ። በዚህ መንገድ ዋነኛውን ክብር ለፈጣሪያችንና ለእርሱ ንጉሣዊ መንግሥት መስጠት ተጀመረ። የይሖዋ ምሥክሮች ለይሖዋ ያላቸውን ፍቅር በማደሳቸው ታላቁን ስሙንና መንግሥቱን ሳያከብሩ ከቀሩበት ከማንኛውም የቀድሞ ሁኔታቸው ንስሐ ገብተዋል።—መዝሙር 106:6, 47, 48

“ድል ለነሳው”

13. (ሀ) የኤፌሶን ክርስቲያኖች ድል ቢነሱ ምን በረከት ይጠብቃቸው ነበር? (ለ) የኤፌሶን ክርስቲያኖች ድል የሚነሱት እንዴት ነበር?

13 በመጨረሻም ኢየሱስ በሌሎቹ መልእክቶቹ እንዳደረገው ታማኝ የመሆን ዋጋ ምን እንደሆነ የአምላክ መንፈስ በኢየሱስ በኩል የገለጸውን ተናገረ። ለኤፌሶን ክርስቲያኖች እንዲህ አላቸው:- “መንፈስ ለአብያተ ክርስቲያናት የሚለውን ጆሮ ያለው ይስማ። ድል ለነሣው በእግዚአብሔር ገነት ካለው ከሕይወት ዛፍ እንዲበላ እሰጠዋለሁ።” (ራእይ 2:7) የሚሰማ ጆሮ ያላቸው ሁሉ ይህ ታላቅ መልእክት ኢየሱስ በራሱ ተነሳስቶ የተናገረው ሳይሆን ሉዓላዊ ገዥያቸው ይሖዋ በመንፈስ ቅዱሱ ወይም በአንቀሳቃሽ ኃይሉ አማካኝነት የተናገረው እንደሆነ ስለሚያውቁ መልእክቱን በጉጉት ይታዘዛሉ። ግን ድል የሚነሱት እንዴት ነው? እስከ ዕለተ ሞቱ ድረስ ፍጹም አቋሙን ጠብቆ “አይዞአችሁ፣ እኔ ዓለምን አሸንፌዋለሁ” ለማለት የቻለውን የኢየሱስን ፈለግ በመከተል ነው።—ዮሐንስ 8:28፤ 16:33፤ በተጨማሪም 1 ዮሐንስ 5:4ን ተመልከት።

14. ኢየሱስ የጠቀሰው “የእግዚአብሔር ገነት” ምን ነገር የሚያመለክት መሆን ይኖርበታል?

14 በኤፌሶን እንደነበሩት ያሉት ቅቡዓን ክርስቲያኖች በምድራዊ ገነት ውስጥ የመኖር ተስፋ ስለሌላቸው “በእግዚአብሔር ገነት ውስጥ ካለው የሕይወት ዛፍ” የመብላት ሽልማት የሚሰጣቸው እንዴት ነው? 144, 000ዎቹ ቅቡዓን ክርስቲያኖች፣ በኤፌሶን ጉባኤ የነበሩትም ጭምር መንፈሳዊ ልጆች ሆነው ከበጉ ከክርስቶስ ኢየሱስ ጋር በሰማያዊቱ የጽዮን ተራራ እንዲነግሡ ከሰው ልጆች መካከል የተዋጁ ስለሆኑ ይህ ገነት በምድር ላይ የሚቋቋመው ገነት ሊሆን አይችልም። (ኤፌሶን 1:5-12፤ ራእይ 14:1, 4) ስለዚህ እዚህ ላይ የተጠቀሰው ገነት እነዚህ ድል አድራጊዎች የሚወርሱት ሰማያዊ የሆነ ገነት መሰል አካባቢ መሆን ይኖርበታል። በዚህ ‘የእግዚአብሔር ገነት’ ውስጥ፣ በዚህ ይሖዋ ራሱ በሚገኝበት ሥፍራ እነዚህ ያለመሞት ባሕርይ የተሰጣቸው አሸናፊዎች ከዘላለም እስከ ዘላለም ይኖራሉ። ከሕይወት ዛፍ መብላታቸውም የሚያመለክተው ይህንኑ ነው።

15. ኢየሱስ ድል ስለመንሳት የተናገረው የሚያበረታታ ቃል እጅግ ብዙ ሰዎችንም የሚመለከተው ለምንድን ነው?

15 144,000ዎቹን ቅቡዓን በታማኝነት የሚደግፉት ምድራውያንስ? እጅግ ብዙ ሕዝብ የሆኑት እነዚህ ተባባሪ ምስክሮችም ድል በመንሳት ላይ ናቸው። ተስፋቸው ግን የተመሠረተው ‘ከሕይወት ውኃ ወንዝ’ ጠጥተውና ‘ከወንዙ ዳርና ዳር ከሚበቅሉት ዛፎች ቅጠል’ በልተው ፈውስ ወደሚያገኙበት ምድራዊ ገነት መግባት ነው። (ራእይ 7:4, 9, 17፤ 22:1, 2) አንተም በዚህ ቡድን ውስጥ ከሆንክ ለይሖዋ ያለህን የጋለ ፍቅር የምትገልጽና በእምነት ገድልም አሸናፊ የምትሆን ያድርግህ። እንዲህ ከሆነ ገነት በምትሆነው ምድር ላይ የዘላለም ሕይወትና ደስታ ልታገኝ ትችላለህ።—ከ⁠1 ዮሐንስ 2:13, 14 ጋር አወዳድር።

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.4 ስለ ሐሰተኛ ሐዋርያት መከሰት ታሪካዊ ዝርዝር መረጃ ለማግኘት ከተፈለገ በይሖዋ ምሥክሮች የተዘጋጀውን ከቅዱሳን ጽሑፎች እየጠቀሱ ማመራመር የተባለውን መጽሐፍ ገጽ 36-43 መመልከት ይቻላል።

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 36 ላይ የሚገኝ ሣጥን]

ለይሖዋና ለልጁ የቀረበ ፍቅራዊ ውዳሴ

የይሖዋ ሕዝቦች በ1905 ባወጡት የመዝሙር መጽሐፍ ላይ ይሖዋን ከሚያወድሱት መዝሙሮች ኢየሱስን የሚያወድሱት መዝሙሮች በእጥፍ ይበልጡ ነበር። በ1928 ባወጡት የመዝሙር መጽሐፋቸው ላይ ይሖዋን የሚያወድሱትና ኢየሱስን የሚያወድሱት መዝሙሮች ብዛት እኩል ሆኖ ነበር። በቅርቡ በ1984 በወጣው የመዝሙር መጽሐፍ ግን ይሖዋ ከኢየሱስ አራት ጊዜ እጥፍ በሚሆኑ መዝሙሮች ተወድሶአል። ይህም ኢየሱስ ራሱ “ከእኔ አብ ይበልጣል” ሲል ከተናገረው ቃል ጋር የሚስማማ ነው። (ዮሐንስ 14:28) የይሖዋ ፍቅር ከሁሉ የበለጠ መሆን ይኖርበታል። በዚህ ላይ ደግሞ ለኢየሱስ የጠለቀ ፍቅርና ውድ ለሆነው ቤዛዊ መሥዋዕቱና የአምላክ ሊቀ ካህናትና ንጉሥ በመሆን ለተቀበለው ሹመቱ ልባዊ አድናቆት ማሳየት ይኖርብናል።

[በገጽ 34 ላይ የሚገኝ ሰንጠረዥ]

የኢየሱስ ምክር አሰጣጥ

(የተጠቀሱት የራእይ ምዕራፎችና ቁጥሮች ናቸው)

መልእክቱ ምክር የምስጋና በግልጽ ማረሚያ የሚገኙት

የተላከበት ለመስጠት መግቢያ የታወቀ እና/ወይም በረከቶች

ጉባኤ ያስቻለው ችግር ማበረታቻ

ሥልጣን

ኤፌሶን 2:1 2:2,3 2:4 2:5, 6 2:7

ሰምርኔስ 2:8 2:92:10 2:11

ጴርጋሞን 2:12 2:13 2:14, 15 2:16 2:17

ትያጥሮን 2:18 2:19 2:20, 21 2:24, 25 2:26-28

ሰርዴስ 3:13:1, 2 3:3, 4 3:5

ፊልድልፍያ 3:7 3:83:8-11 3:12

ሎዶቅያ 3:143:15-17 3:18-20 3:21