በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የአምላክ ቅዱስ ምሥጢር—ታላቁና ክብራማ መደምደሚያው!

የአምላክ ቅዱስ ምሥጢር—ታላቁና ክብራማ መደምደሚያው!

ምዕራፍ 26

የአምላክ ቅዱስ ምሥጢር—ታላቁና ክብራማ መደምደሚያው!

1. (ሀ) ዮሐንስ ቅዱሱ ምሥጢር ወደ ፍጻሜ መድረሱን ያስታወቀን እንዴት ነው? (ለ) የመላእክት ሠራዊት ጮክ ብለው የተናገሩት ለምንድን ነው?

ብርቱው መልአክ በ⁠ራእይ 10:1, 6, 7 ላይ በመሐላ የተናገረውን ቃል ታስታውሳለህን? እንዲህ ብሎ ነበር:- “ወደ ፊት አይዘገይም፣ ዳሩ ግን ሰባተኛው መልአክ ሊነፋ ባለው ጊዜ ድምፁም በሚሰማበት ዘመን፣ ለባሪያዎቹ ለነቢያት የምሥራች እንደሰበከላቸው የእግዚአብሔር ምሥጢር ይፈጸማል።” ይህ የመጨረሻ መለከት እንዲነፋ ይሖዋ የቀጠረበት ጊዜ አሁን ደርሶአል። ታዲያ ቅዱሱ ምስጢር የሚፈጸመው እንዴት ነው? ዮሐንስ ይህን ሲነግረን በጣም ተደስቶ ነበር። “ሰባተኛው መልአክ ነፋ፤ በሰማይም:- የዓለም መንግሥት ለጌታችንና ለእርሱ ለክርስቶስ ሆነች፣ ለዘላለምም እስከ ዘላለም ይነግሣል የሚሉ ታላላቅ ድምፆች ሆኑ።” (ራእይ 11:15) እነዚህ የመላእክት ሠራዊት ጮክ ብለው እንደ ነጎድጓድ ባለ ድምፅ የሚናገሩበት ምክንያት ነበራቸው። ይህ ታሪካዊ ማስታወቂያ ለመላው ጽንፈ ዓለም አስፈላጊ የሆነ ማስታወቂያ ነው። ሕያዋን ፍጥረታትን ሁሉ በጣም የሚያሳስብ ነው።

2. ቅዱሱ ምሥጢር ወደ ድል አድራጊ መደምደሚያው የደረሰው መቼና በምን ድርጊት ነው?

2 ቅዱሱ ምሥጢር ወደ ታላቁ አስገራሚ መደምደሚያው መጥቷል! ጌታ ይሖዋ የራሱን ክርስቶስ ተባባሪ ንጉሥ እንዲሆን በዙፋን ላይ ባስቀመጠበት በ1914 በድል አድራጊነትና በታላቅ ግርማ ተፈጽሟል። ኢየሱስ ክርስቶስ አባቱን ወክሎ እርምጃ በመውሰድ ጠላት በሆነው የሰው ልጆች ዓለም ላይ መግዛት ጀምሯል። ተስፋ የተደረገው ዘር እንደመሆኑ መጠን እባቡንና አጫፋሪዎቹን ፈጽሞ አጥፍቶ በምድር ላይ ገነታዊ ሰላም ለማስፈን መንግሥታዊ ሥልጣን ተቀብሎአል። (ዘፍጥረት 3:15፤ መዝሙር 72:1, 7) ኢየሱስ መሲሐዊ ንጉሥ እንደመሆኑ መጠን የይሖዋን ቃል ይፈጽማል። “ከዘላለም እስከ ዘላለም” የጽንፈ ዓለሙ ሉዓላዊ ጌታ በመሆን መግዛት የሚገባውንና “የዘላለም ንጉሥ” የሆነውን የአባቱን ትክክለኛነት ያረጋግጣል።—1 ጢሞቴዎስ 1:17

3. ይሖዋ አምላክ ምንጊዜም ቢሆን ንጉሥ ቢሆንም በምድር ላይ ሌሎች የበላይ ወይም ሉዓላዊ ገዥዎች እንዲኖሩ የፈቀደው ለምንድን ነው?

3 ይሁን እንጂ “የዓለም መንግሥት . . . የጌታችን” የይሖዋ መንግሥት የሆነው እንዴት ነው? ምንጊዜም ቢሆን ይሖዋ ንጉሥ አልነበረምን? አዎ፣ ነበር። ሌዋዊው አሳፍም “እግዚአብሔር ግን ከዓለም አስቀድሞ ንጉሥ ነው” ሲል ዘምሮአል። ሌላው መዝሙራዊ ደግሞ “እግዚአብሔር [“ይሖዋ፣” NW] ነገሠ። . . . ዙፋንህ ከጥንት ጀምሮ የተዘጋጀ ነው፣ አንተም ከዘላለም ነህ” ብሎአል። (መዝሙር 74:12፤ 93:1, 2) ይሁን እንጂ ይሖዋ በታላቅ ጥበቡ ሌሎች ሉዓላዊ ገዥዎች እስከ ጊዜው ድረስ በምድር ላይ እንዲኖሩ ፈቅዶ ነበር። ይህንንም ስላደረገ የሰው ልጅ ያለአምላክ ብቻውን ራሱን ለማስተዳደር ስለመቻሉና ስላለመቻሉ በኤደን ገነት የተነሳው ጥያቄ ሙሉ ምላሽ እንዲያገኝ አስችሎአል። የሰው አገዛዝ ከንቱ መሆኑ ተረጋግጦአል። የአምላክ ነቢይ የተናገረው የሚከተለው ቃል እውነት ሆኖአል። “አቤቱ የሰው መንገድ ከራሱ እንዳይደለ አውቃለሁ፣ አካሄዱንም ለማቅናት ከሚራመድ ሰው አይደለም።” (ኤርምያስ 10:23) የመጀመሪያዎቹ ወላጆቻችን ከአምላክ ካፈነገጡበት ጊዜ ጀምሮ መላው ምድር ‘በቀደመው እባብ’ በሰይጣን ዲያብሎስ ሲገዛ ቆይቶአል። (ራእይ 12:9፤ ሉቃስ 4:6) አሁን ግን ትልቅ ለውጥ የሚደረግበት ጊዜ ደረሰ። ይሖዋ ትክክለኛ ቦታውን ለማረጋገጥ በምድር ላይ የነበረውን የሉዓላዊ ገዥነት ሥልጣኑን በአዲስ መንገድ ማለትም በተሾመው መሲሐዊ መንግሥት አማካኝነት ይጠቀምበታል።

4. መለከቶቹ በ1922 መነፋት በጀመሩ ጊዜ ምን ነገር ግልጽ ሆነ? አስረዳ።

4 የሰባቱ መለከቶች መነፋት በ1922 በጀመረ ጊዜ በሴዳር ፖይንት፣ ኦሃዮ ተደርጎ በነበረው የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች ስብሰባ ላይ ወንድም ጄ ኤፍ ራዘርፎርድ “መንግሥተ ሰማያት ቀርባለች” በሚለው ጥቅስ ላይ የተመሠረተ ንግግር አቅርቦ ነበር። (ማቴዎስ 4:17) ንግግሩን ሲደመድም የሚቀጥሉትን ቃላት ተናግሮ ነበር። “እንግዲህ አሁን የልዑል አምላክ ልጆች በሙሉ ወደ መስኩ ተመለሱ። ትጥቃችሁን አንሱ። ጭምቶች፣ ብርቱዎች፣ ትጉሆችና ደፋሮች ሁኑ። ታማኝና እውነተኛ የጌታ ምሥክሮች ሁኑ። የባቢሎን ቅሬታ በሙሉ ባድማ እስኪሆን ድረስ በውጊያው ወደፊት ግፉ። መልእክቱን በስፋትና በርቀት አውጁ። ዓለም ይሖዋ አምላክ እንደሆነና ኢየሱስ ክርስቶስ ደግሞ የጌቶች ጌታና የነገሥታት ንጉሥ እንደሆነ ማወቅ ይኖርበታል። ይህ የቀኖች ሁሉ ቀን ነው። እነሆ ንጉሡ በመግዛት ላይ ነው! እናንተ ደግሞ አዋጅ ነጋሪዎቹ ናችሁ። ስለዚህ ንጉሡንና መንግሥቱን አስታውቁ፣ አስታውቁ፣ አስታውቁ።” በክርስቶስ ኢየሱስ የሚተዳደረው የአምላክ መንግሥት ጉልህ ሆኖ ታይቶ ነበር። በዚህም ምክንያት በመላእክቱ ሰባት መለከቶች መነፋት የተገለጸውን የፍርድ መልእክት የሚጨምረው ታላቅ የመንግሥት ሥራ በአዲስ ኃይል ተጀመረ።

5. በ1928 ሰባተኛውን የመለከት ድምፅ ያሳወቀው የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች ስብሰባ በተደረገበት ጊዜ ምን ነገር ተፈጸመ?

5 የሰባተኛው መልአክ የመለከት ድምፅ የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች በዴትሮይ፣ ሚሺጋን ከሐምሌ 30 እስከ ነሐሴ 6, 1928 አድርገውት በነበረው ከፍተኛ ስብሰባ ላይ በጉልህ ተንጸባርቆ ነበር። በዚያ ጊዜ 107 የሚያክሉ ሬዲዮ ጣቢያዎች በአንድ መስመር ተገናኝተው የስብሰባውን ፕሮግራም አሰራጭተው ነበር። ኒው ዮርክ ታይምስ ስለዚህ የሬዲዮ ስርጭት ሲገልጽ ‘እስከ ዛሬ ጊዜ ከተደረጉት የሬዲዮ ስርጭቶች ሁሉ ሰፊ የሆነና ከፍተኛ ወጪ የተከፈለበት ነው’ ብሎ ነበር። ስብሰባው ጠንካራ የሆነ “ይሖዋን የሚደግፍና ሰይጣንን የሚቃወም” መግለጫ በከፍተኛ ስሜትና ግለት አስተላለፈ። መግለጫው ሰይጣንና ክፉ ድርጅቱ በአርማጌዶን እንደሚጠፉና ጽድቅን የሚወዱ ሁሉ ነፃነት እንደሚያገኙ የሚገልጽ ነበር። የአምላክ መንግሥት ተገዥዎች በዚህ ስብሰባ ላይ የወጣውን መንግሥት የተባለ ባለ 368 ገጽ መጽሐፍ በማግኘታቸው በጣም ተደስተው ነበር። ይህም መጽሐፍ “አምላክ የቀባውን ንጉሥ በ1914 ዙፋኑ ላይ እንዳስቀመጠው” የሚያረጋግጥ ግልጽ ማስረጃ አቅርቦ ነበር።

ይሖዋ ኃይሉን ጨበጠ

6. ዮሐንስ ክርስቶስ በአምላክ መንግሥት መንገሡንና ዙፋን ላይ መቀመጡን የሚገልጸውን ማስታወቂያ የነገረን እንዴት ነው?

6 ክርስቶስ የአምላክ መንግሥት ንጉሥ ሆነ። ይህ ማስታወቂያ እንዴት ያለ ከፍተኛ ደስታ እንደሚያስገኝ ዮሐንስ ይነግረናል:- “በእግዚአብሔርም ፊት በዙፋኖቻቸው የተቀመጡ ሀያ አራቱ ሽማግሌዎች በግምባራቸው ተደፍተው ለእግዚአብሔር እየሰገዱ እንዲህ አሉ:- ያለህና የነበርህ ሁሉን የምትገዛ ጌታ እግዚአብሔር [“ይሖዋ፣” NW] ሆይ፣ ትልቁን ኃይልህን ስለ ያዝህ ስለ ነገሥህም እናመሰግንሃለን።”—ራእይ 11:16, 17

7. (ሀ) የ24ቱ ምሳሌያዊ ሽማግሌዎች ምድራዊ ቀሪዎች (ለ) ከሙታን ተነስተው ሰማያዊ ሥፍራቸውን የያዙት ምሳሌያዊ 24 ሽማግሌዎች ለይሖዋ አምላክ ምሥጋና ያቀረቡት እንዴት ነው?

7 ይህን ምሥጋና ለይሖዋ ያቀረቡት ሰማያዊ ቦታቸውን የያዙት የክርስቶስ ቅቡዓን ወንድሞች ምሳሌ የሆኑት 24 ሽማግሌዎች ናቸው። እነዚህ 144,000 ቅቡዓን ቀሪዎች ከ1922 ጀምሮ በመለከቶቹ መነፋት የተቀሰቀሰውን ሥራ በምድር ላይ በከፍተኛ ትጋት ሲፈጽሙ ቆይተዋል። በ⁠ማቴዎስ 24:3 እስከ 25:46 የተገለጸውን ምልክት ሙሉ ትርጉም ተረድተዋል። ይሁን እንጂ ታማኝነታቸውን እስከ ሞት ድረስ ያረጋገጡት የምሥክርነት ባልንጀሮቻቸው ቀደም ሲል በጌታ ቀን መጀመሪያ ላይ የሰማይ ቦታቸውን እንዲይዙ ከሙታን ስለተነሱ መላውን የ144, 000 ክፍል በመወከል በግምባራቸው እየተደፉ ለይሖዋ ለመስገድ ችለዋል። (ራእይ 1:10፤ 2:10) እነዚህ ሁሉ ጌታቸው ቅዱስ ምሥጢሩን ሳይዘገይ ወደ ታላቅ ፍጻሜ በማድረሱ ምንኛ አመስጋኞች ናቸው!

8. (ሀ) የሰባተኛው መለከት መነፋት በብሔራት ላይ ምን ዓይነት ውጤት አስከትሎአል? (ለ) ብሔራት የተቆጡት በማን ላይ ነው?

8 በሌላ በኩል ደግሞ የሰባተኛው መለከት መነፋት ለአሕዛብ ምንም ዓይነት ደስታ አላመጣላቸውም። የይሖዋን ቁጣ የሚቀምሱበት ጊዜ ደርሶባቸዋል። ዮሐንስ እንደሚገልጸው:- “አሕዛብም ተቆጡ፣ ቁጣህም መጣ፣ በሙታንም ትፈርድ ዘንድ ዘመን መጣ፣ ለባሪያዎችህም ለነቢያትና ለቅዱሳን ስምህንም ለሚፈሩት ለታናናሾችና ለታላላቆችም ዋጋቸውን ትሰጥ ዘንድ፣ ምድርንም የሚያጠፉትን ታጠፋ ዘንድ ዘመን መጣ።” (ራእይ 11:18) አሕዛብ ከ1914 ጀምሮ እርስ በርሳቸው፣ በአምላክ መንግሥትና በተለይም በይሖዋ ሁለት ምሥክሮች ላይ በአስፈሪ ሁኔታ ሲቆጡ ቆይተዋል።—ራእይ 11:3

9. ብሔራት ምድርን ሲያጠፉ የቆዩት እንዴት ነው? አምላክስ ምን ለማድረግ ወስኖአል?

9 አሕዛብ በታሪክ ዘመናት ሁሉ ለአንድ አፍታ እንኳን ጋብ ባላለው ጦርነታቸውና በመጥፎ አያያዛቸው ምድርን ሲያጠፉ ወይም ሲያበላሹ ቆይተዋል። ከ1914 ወዲህ ግን ይህ ምድርን የማጥፋት ድርጊት በጣም ተባብሶ አስደንጋጭ ደረጃ ላይ ደርሶአል። በስግብግብነትና በምግባረ ብልሹነት ምክንያት በረሐዎች ተስፋፍተዋል፣ ብዙ ለም መሬቶች ጠፍ ሆነዋል። የአሲድ ዝናብና የሬዲዮ ጨረር የሚያዘንቡ ዳመናዎች ሰፊ አካባቢዎች ላይ ጉዳት አድርሰዋል። ለምግብነት የሚያገለግሉ ዕጽዋትና አዝርዕት ተበክለዋል። የምንተነፍሰው አየርና የምንጠጣው ውኃ ተበክሎአል። ከኢንዱስትሪዎች የሚወጣው ቆሻሻ በምድርና በባሕር ፍጥረታት ሕይወት ላይ አደገኛ ሁኔታ ደቅኖአል። በአንድ ወቅት ልዕለ ኃያላን መንግሥታት የሰው ልጆችን በሙሉ በኑክሌር መሣሪያ ሙሉ በሙሉ ያጠፋሉ የሚል ስጋት ተፈጥሮ ነበር። ይሁን እንጂ ይሖዋ ‘ምድርን የሚያጠፉትን ስለሚያጠፋ’ ደስ ሊለን ይገባል። ምድርን እንደዚህ ወዳለው አሳዛኝ ሁኔታ በጣሉአት ትዕቢተኛና አምላክ የለሽ ሰዎች ላይ የቅጣት ፍርዱን ይፈጽማል። (ዘዳግም 32:5, 6፤ መዝሙር 14:1-3) በዚህም ምክንያት ይሖዋ እነዚህን ክፉ አድራጊዎች ወደ ፍርድ ለማቅረብ ሦስተኛው ወዮታ እንዲመጣ አድርጎአል።—ራእይ 11:14

ምድርን ለሚያጠፉ ወዮላቸው!

10. (ሀ) ሦስተኛው ወዮታ ምንድን ነው? (ለ) ሦስተኛው ወዮታ በማሠቃየት ብቻ የማያበቃው በምን መንገድ ነው?

10 ሦስተኛው ወዮታ እነሆ! ፈጥኖ ይመጣል! ይህ ወዮታ ይሖዋ “የእግሩ መረገጫ” የሆነችውን ይህችን ውብ ምድር የሚያረክሱትን ሰዎች የሚያጠፋበት መሣሪያ ነው። (ኢሳይያስ 66:1) ወዮታውን የሚያንቀሳቅሰው የአምላክ ቅዱስ ምስጢር የሆነው የአምላክ መሲሐዊ መንግሥት ነው። የአምላክ ጠላቶች በተለይም የሕዝበ ክርስትና መሪዎች ከአንበጣው መቅሰፍትና ከፈረሰኞቹ ሠራዊት ከመጡት ሁለት ወዮታዎች ብዙ ሥቃይ ተቀብለዋል። የይሖዋ መንግሥት ራሱ የሚያመጣው ሦስተኛ ወዮታ ግን ሥቃይ በማድረስ ብቻ ተወስኖ አይቀርም። (ራእይ 9:3-19) በአጥፊው የሰው ልጆች ኅብረተሰብና በገዥዎቹ ላይ የሞት ቅጣት በማምጣት ከቦታቸው ያስወግዳቸዋል። ይህም የሚሆነው የይሖዋ ፍርድ የመጨረሻ ከፍተኛ ደረጃ ላይ በሚደርስበት በአርማጌዶን ጦርነት ነው። ዳንኤል በትንቢት እንደተናገረው ይሆናል። “በእነዚያም ነገሥታት [ምድርን በሚያጠፉት ገዥዎች] ዘመን የሰማይ አምላክ ለዘላለም የማይፈርስ መንግሥት ያስነሳል። ለሌላ ሕዝብም የማይሰጥ መንግሥት ይሆናል። እነዚያንም መንግሥታት ሁሉ ትፈጫቸዋለች፣ ታጠፋቸውማለች ለዘላለምም ትቆማለች።” የአምላክ መንግሥት እንደ አንድ ግርማ ያለው ውብ ተራራ በመሆን ክብር በተጎናጸፈች ምድር ላይ ትገዛለች። ይህም የይሖዋን ሉዓላዊነት ከማረጋገጡም በላይ ለሰው ልጆች ሁሉ ዘላለማዊ ደስታ ያመጣል።—ዳንኤል 2:35, 44፤ ኢሳይያስ 11:9፤ 60:13

11. (ሀ) ትንቢቱ የሚገልጸው የትኞቹን ተከታታይ የሆኑ አስደሳች ክንውኖች ነው? (ለ) ለሰው ልጆች የሚዘረጋው የማይገባ ደግነት ምንድን ነው? ይህስ የሚፈጸመው በማንና እንዴት ነው?

11 ሦስተኛው ወዮታ በጌታ ቀን በተከታታይ በሚፈጸሙ አስደሳች ክንውኖች የታጀበ ነው። ሙታን የሚፈረዱበትና አምላክ ‘ለባሪያዎቹ ለነቢያትና ስሙን ለሚፈሩ ቅዱሳን ዋጋቸውን የሚሰጥበት’ ጊዜ ነው። የሙታን ትንሣኤ ይሆናል ማለት ነው። ከአሁን በፊት ያንቀላፉ ቅቡዕ የሆኑ ቅዱሳን ከሙታን የተነሱት በጌታ ቀን መጀመሪያ ላይ ነው። (1 ተሰሎንቄ 4:15-17) ከዚያ በኋላ ደግሞ የቀሩት ቅዱሳን ቅጽበታዊ ትንሣኤ እያገኙ አብረዋቸው ይኖራሉ። የይሖዋን ስም የሚፈሩት ከታላቁ መከራ በሕይወት የሚያልፉት እጅግ ብዙ ሰዎችም ሆኑ በክርስቶስ የሺህ ዓመት ግዛት ከሙታን የሚነሱት ‘ታላላቅና ታናናሽ ሙታን’ እንዲሁም በጥንት ዘመን ነቢያት የነበሩ የአምላክ ባሮች ዋጋቸውን ይቀበላሉ። የአምላክ መሲሐዊ መንግሥት የሞትንና የሲኦልን ቁልፍ ስለያዘ መሲሑ ለዚህ ከፍተኛ ዝግጅት ለሚበቁ ሁሉ የዘላለምን ሕይወት ሽልማት እንዲዘረጋ መንገዱን ይከፍትለታል። (ራእይ 1:18፤ 7:9, 14፤ 20:12, 13፤ ሮሜ 6:22፤ ዮሐንስ 5:28, 29) ይህ የሕይወት ስጦታ፣ ሞት የማይደፍረው ሰማያዊ ሕይወትም ሆነ የዘላለም ምድራዊ ሕይወት እያንዳንዱ ተሸላሚ በከፍተኛ አመስጋኝነት ሊቀበለው የሚገባ የይሖዋ የማይገባ ደግነት ነው!—ዕብራውያን 2:9

የኪዳኑም ታቦት ታየ!

12. (ሀ) በ⁠ራእይ 11:19 መሠረት ዮሐንስ በሰማይ ምን ተመለከተ? (ለ) የቃል ኪዳኑ ታቦት የምን ምሳሌ ሆኖ ነበር? እስራኤላውያን ወደ ባቢሎን ግዞት በተወሰዱ ጊዜ የቃል ኪዳኑ ታቦት ምን ሆነ?

12 ይሖዋ በመግዛት ላይ ነው። በመሲሐዊ መንግሥቱ አማካኝነት ሉዓላዊነቱን በሰው ልጆች ሁሉ ላይ በአስደናቂ ሁኔታ ዘርግቶአል። ይህም ዮሐንስ ቀጥሎ በተመለከተው ነገር ተረጋግጦአል:- “በሰማይም ያለው የእግዚአብሔር መቅደስ ተከፈተ፣ የኪዳኑም ታቦት በመቅደሱ ታየ፣ መብረቅና ድምፅም ነጎድጓድም የምድርም መናወጥ ታላቅም በረዶ ሆነ።” (ራእይ 11:19) የአምላክ የቃል ኪዳን ታቦት በራእይ መጽሐፍ ውስጥ የተጠቀሰበት ቦታ ይህ ብቻ ነው። ታቦቱ ይሖዋ በሕዝቦቹ በእስራኤላውያን መካከል መኖሩን የሚያሳውቅ የሚታይ ምልክት ነበረ። ይህ ታቦት በመገናኛ ድንኳኑና በኋላም ሰሎሞን በሠራው ቤተ መቅደስ ውስጥ በቅድስተ ቅዱሳኑ ውስጥ ይቀመጥ ነበር። እስራኤላውያን በ607 ከዘአበ በባቢሎናውያን ተማርከው ወደ ግዞት በተወሰዱ ጊዜ ግን ኢየሩሳሌም ባድማ ስለሆነች የቃል ኪዳኑ ታቦትም የደረሰበት ሳይታወቅ ቀርቶአል። ይህ የሆነው የዳዊት ቤት ወኪሎች በይሖዋ ዙፋን ላይ መቀመጣቸው በቀረ ጊዜ ነበር።—1 ዜና 29:23 *

13. የአምላክ የቃል ኪዳን ታቦት በአምላክ ሰማያዊ ቤተ መቅደስ ውስጥ መታየቱ ምን ያመለክታል?

13 አሁን ከ2,500 ዓመት ከሚበልጥ ጊዜ በኋላ ታቦቱ እንደገና ታየ። ይሁን እንጂ ዮሐንስ በራእይ የተመለከተው ታቦት በምድራዊ ቤተ መቅደስ ውስጥ አልነበረም። በሰማያዊው የአምላክ መቅደስ ውስጥ ያለ ይመስላል። አሁንም እንደገና ይሖዋ የዳዊት ዘር በሆነ ንጉሥ አማካኝነት መግዛት ጀምሮአል። ይሁን እንጂ ንጉሡ ክርስቶስ ኢየሱስ ንግሥናውን የተቀበለው የይሖዋን ፍርድ በሚያስፈጽምበት ከፍተኛ ቦታ በሰማያዊ ኢየሩሳሌም ነው። (ዕብራውያን 12:22) የሚቀጥሉት የራእይ ምዕራፎች ይህንን ነገር በይበልጥ ግልጽ ያደርጉልናል።

14, 15. (ሀ) በጥንትዋ ኢየሩሳሌም የቃል ኪዳኑን ታቦት ለማየት የሚችለው ማን ብቻ ነበር? ለምንስ? (ለ) በሰማያዊው የአምላክ ቤተ መቅደስ ግን የቃል ኪዳኑን ታቦት እነማን ለማየት ይችላሉ?

14 በጥንታዊቷ ምድራዊት ኢየሩሳሌም ታቦቱ የሚቀመጠው ከቅድስቱ በመጋረጃ በሚከለለው ቅድስተ ቅዱሳን ውስጥ ስለነበረ ለእስራኤላውያን በሙሉ በቤተ መቅደሱ ለሚያገለግሉት ካህናትም እንኳን አይታይም ነበር። (ዘኁልቁ 4:20፤ ዕብራውያን 9:2, 3) ታቦቱን ለማየት የሚችለው የስርየት ቀን በሚከበርበት ዓመታዊ በዓል ወደ ቅድስተ ቅዱሳኑ የሚገባው ሊቀ ካህናት ብቻ ነበር። በሰማያት ያለው ቤተ መቅደስ በተከፈተ ጊዜ ግን ምሳሌያዊው ታቦት ለይሖዋ ሊቀ ካህናት ለኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ሳይሆን ዮሐንስን ጨምሮ የበታች ካህናት ለሆኑት 144, 000ዎች ታይቶአል።

15 ከሙታን ተነስተው ወደ ሰማይ ከሚሄዱት መካከል ትንሣኤ በማግኘት በኩር የሆኑት ቅቡዓን በይሖዋ ዙፋን ዙሪያ የተቀመጡት 24 ሽማግሌዎች ክፍል በመሆን ቦታቸውን ስለያዙ ይህን ምሳሌያዊ ታቦት ከቅርብ ሊመለከቱት ችለዋል። በምድር ላይ ያሉትም የዮሐንስ ክፍል አባሎች ከይሖዋ መንፈስ ባገኙት ማስተዋል ይሖዋ በመንፈሳዊ ቤተ መቅደሱ መገኘቱን ተረድተዋል። በተጨማሪም የሰው ልጅ በአጠቃላይ ይህን አስደናቂ ክንውን እንዲያስተውል የሚያስችለው ምልክት ታይቶ ነበር። የዮሐንስ ራእይ ስለ መብረቅ፣ ስለ ድምፆች፣ ስለ ነጎድጓድ፣ ስለ ምድር መናወጥና ስለ በረዶ ገልጾ ነበር። (ከ⁠ራእይ 8:5 ጋር አወዳድር።) እነዚህ ነገሮች ምን ያመለክታሉ?

16. መብረቅ፣ ድምፅ፣ ነጎድጓድ፣ የምድር መናወጥና ታላቅ የበረዶ ዝናብ የኖረው እንዴት ነው?

16 ከ1914 ወዲህ በሃይማኖታዊው ዓለም ውስጥ ታላቅ ነውጥ ተፈጥሮ ነበር። ይሁን እንጂ ይህ “የምድር መናወጥ” ስለተቋቋመው የአምላክ መንግሥት ግልጽ መልእክት በሚሰጡ ድምፆች የታጀበ መሆኑ ያስደስታል። ከመጽሐፍ ቅዱስ የተውጣጡ ‘ነጎድጓዳማ ማስጠንቀቂያዎች’ ተሰምተዋል። የአምላክ ትንቢታዊ ቃል እንደ መብረቅ ብልጭታ ከዳር እስከ ዳር ታይቶአል፣ ተነግሮአል። እንደ ከባድ የበረዶ ድንጋይ ያለ መለኮታዊ ፍርድ በሕዝበ ክርስትናና በጠቅላላው ሐሰት ሃይማኖት ላይ ወርዶአል። ይህ ሁሉ ነገር የሰዎችን ትኩረት መሳብ ነበረበት። ይሁን እንጂ አብዛኞቹ ሰዎች በኢየሱስ ዘመን እንደነበሩት የኢየሩሳሌም ሰዎች የእነዚህን የራእይ ምልክቶች ፍጻሜ አለማስተዋላቸው ያሳዝናል።—ሉቃስ 19:41-44

17, 18. (ሀ) የሰባቱ መላእክት መለከቶች መነፋት ራሳቸውን በወሰኑ ክርስቲያኖች ላይ ምን ኃላፊነት አምጥቶባቸዋል? (ለ) ክርስቲያኖች የሥራ ግዴታቸውን ሲፈጽሙ የቆዩት እንዴት ነው?

17 ሰባቱ መላእክት በዚህ ምድር ላይ የሚፈጸሙ ታሪካዊ ክንውኖችን የሚያስታውቁትን መለከቶች መንፋታቸውን ቀጥለዋል። ራሳቸውን የወሰኑ ክርስቲያኖች ሁሉ እነዚህን ማስታወቂያዎች ለዓለም በሙሉ የማስታወቅ ትልቅ ኃላፊነት አለባቸው። ይህንንም ሥራ በማከናወናቸው ምንኛ ደስተኞች ናቸው! ከ1986 እስከ 2005 በነበሩት ሃያ ዓመታት በአገልግሎታቸው ያሳለፉት ሰዓት ከ680,837,042 ተነስቶ በእጥፍ ያህል በመጨመር ወደ 1,278,235,504 ሰዓት ከፍ ማለቱ ለዚህ ማስረጃ ይሆናል። በእውነትም ‘የአምላክ ቅዱስ ምሥጢር ምሥራች’ ‘እስከ ምድር ዳርቻ’ ድረስ በመታወቅ ላይ ነው።—ራእይ 10:7፤ ሮሜ 10:18

18 የአምላክን መንግሥት ዓላማዎች የሚገልጹ ሌሎች ራእዮችም ገና ይጠብቁናል።

[የግርጌ ማስታወሻ]

^ አን.12 ታሲተስ የተባለው ሮማዊ ታሪክ ጸሐፊ፣ ኢየሩሳሌም በ63 ከዘአበ በተወረረች ጊዜ ክኔዩስ ፖምፒየስ ወደ ቤተ መቅደሱ ገብቶ ምንም ነገር እንዳላገኘ ጽፎአል። በውስጡ የቃል ኪዳኑ ታቦት አልነበረም።—ታሲተስ ታሪክ 5.9

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 173 ላይ የሚገኝ ሣጥን]

ጎላ ብለው የሚታዩ የይሖዋ መለከት መሰል የፍርድ መግለጫዎች

1. 1922 ሴዳር ፖይንት፣ ኦሃዮ:- የሕዝበ ክርስትና ሃይማኖታዊ፣ ፖለቲካዊና የታላላቅ ንግድ ድርጅቶች መሪዎች ሰላም፣ ብልጽግናና ደስታ ለማምጣት ያልቻሉበትን ምክንያት እንዲያቀርቡ ግድድር ቀረበላቸው። ፈውስ የሚያስገኘው መሲሐዊው መንግሥት ብቻ እንደሆነ ተገለጸ።

2. 1923 ሎስ አንጀለስ፣ ካሊፎርኒያ:- “ብሔራት ሁሉ ወደ አርማጌዶን በመገስገስ ላይ ናቸው፣ በአሁኑ ጊዜ በሕይወት የሚኖሩ በሚልዮን የሚቆጠሩ ሰዎች ግን ፈጽሞ አይሞቱም” የሚለው የሕዝብ ንግግር ሰላም ወዳድ “በጎች” ሞት ከሚያስከትለው የሰው ልጆች ባሕር እንዲወጡ ጥሪ ቀረበላቸው።

3. 1924 ኮሎምበስ፣ ኦሃዮ:- ቀሳውስት ራሳቸውን ከፍ ከፍ በማድረጋቸውና የመሲሑን መንግሥት ባለማወጃቸው ክስ ቀረበባቸው። እውነተኛ ክርስቲያኖች ሁሉ የአምላክን በቀል መስበክና ሐዘን የተጫነበትን የሰው ልጅ ማጽናናት ይገባቸዋል።

4. 1925 ኢንድያናፖሊስ፣ ኢንድያና:- ሕዝበ ክርስትና ያለችበትን መንፈሳዊ ጨለማ፤ የሰላም፣ የብልጽግና፣ የጤና፣ የሕይወት፣ የነፃነትና የዘላለማዊ ደስታ ተስፋ ከሚሰጠው ብሩሕ የመንግሥት መልእክት ጋር የሚያነጻጽር የተስፋ መልእክት።

5. 1926 ለንደን፣ እንግሊዝ:- ሕዝበ ክርስትናና ቀሳውስትዋ የአምላክ መንግሥት ተቃዋሚዎች መሆናቸውንና የዚህችን ሰማያዊት መንግሥት መወለድ አለማወጃቸውን የሚያጋልጥ የአንበጣ መንጋ የሚመስል መቅሰፍት ወረደባቸው።

6. 1927 ቶሮንቶ፣ ካናዳ:- የፈረሰኛ ሠራዊት በሚመስሉ መልእክተኞች አማካኝነት ሰዎች ሁሉ ‘የተደራጀውን ክርስትና’ ጥለው በመውጣት ለይሖዋ አምላክና ለይሖዋ ንጉሥና መንግሥት ልባዊ ታማኝነት እንዲያሳዩ ጥሪ ቀረበ።

7. 1928 ዴትሮይት፣ ሚሺጋን:- ሰይጣንን የሚቃወምና ይሖዋን የሚደግፍ መግለጫ ወጣ። መግለጫውም በ1914 ዙፋን ላይ የተቀመጠውና የተቀባው የአምላክ ንጉሥ ክፉውን የሰይጣን ድርጅት አጥፍቶ የሰው ልጆችን ነፃ እንደሚያወጣ የሚገልጽ ነበር።

[በገጽ 175 ላይ የሚገኝ ሣጥን]

ምድርን ማበላሸት

“በየሦስት ሴኮንድ አንድ የእግር ኳስ ሜዳ የሚያክል ደን ይወድማል። . . . የእነዚህ ደኖች መውደም ደግሞ በሺህ የሚቆጠሩ የእጽዋትና የእንስሳት ዘሮች እንዲጠፉ ምክንያት ሆኖአል።”—ኢሉስትሬትድ አትላስ ኦፍ ዘ ወርልድ (ራንድ ማክናሊ)

“በሁለት መቶ ዘመናት ውስጥ [ታላላቆቹ ሐይቆች] የዓለም ታላላቅ የቆሻሻ ፍሳሽ ማጠራቀሚያዎች ሆነዋል።”—ዘ ግሎብ ኤንድ ሜይል (ካናዳ)

በሚያዝያ ወር 1986 በቸርኖብል ዩ ኤስ ኤስ አር የደረሰው ፍንዳታና ቃጠሎ “ሂሮሽማና ናጋሳኪ ከተደበደቡበት ጊዜ ወዲህ የታየ በጣም ከባድ የኑክሌር ፍንዳታ ነው። በዓለም አየር፣ ውኃና አፈር ላይ እስከ አሁን የፈነዱትን የሙከራ ኑክሌር ቦምቦች ሁሉ የሚያክል ጨረር እንዲሰራጭ አድርጎአል።”—ጃማዘ ኒው ዮርክ ታይምስ

በጃፓን አገር በሚናማታ ከሚገኝ የኬሚካል ፋብሪካ ሜቲልሜርኩሪ የተባለው ቅመም ወጥቶ ወደ ባሕር ውስጥ ፈስሶአል። በዚህ ኬሚካል የተመረዙትን ዓሦች የበሉ ሰዎች ሚናማታ ዲዚዝ (MD) የተባለ በሽታ ይዞአቸዋል። “ይህም በሽታ በጣም ከባድ የሆነ የነርቭ ቀውስ የሚያመጣ ሲሆን እስከ [1985] ድረስ በጃፓን አገር በሙሉ 2, 578 ሰዎች በሚናማታ በሽታ (MD) እንደተለከፉ ተረጋግጦአል።”—ኢንተርናሽናል ጆርናል ኦፍ ኤፒዶሞሎጂ

[በገጽ 176 ላይ የሚገኝ ሣጥን]

በ⁠ራእይ 11:15-19 ላይ የሚገኙት ከባድ መልእክቶች ለሚቀጥሉት ራእዮች መግቢያ ይሆናሉ። ራእይ ምዕራፍ 12 በ⁠ራእይ 11:15, 17 ላይ የሚገኘውን ታላቅ ማስታወቂያ የሚያብራራና በዝርዝር የሚገልጽ ራእይ ነው። ምዕራፍ 13 ደግሞ በምድር ላይ ጥፋት ያመጣው የሰይጣን የፖለቲካ ድርጅት ከየት እንደተገኘና እንዴት እንደተስፋፋ ስለሚገልጽ ለ11:18 ማብራሪያ ይሰጣል። ምዕራፍ 14 እና 15 ከሰባተኛው መለከት መነፋትና ከሦስተኛው ወዮታ ጋር የሚዛመዱትን የመንግሥት ፍርዶች በዝርዝር ይገልጻል።

[በገጽ 174 ላይ የሚገኙ ሥዕሎች]

ይሖዋ “ምድርን የሚያጠፉትን ያጠፋል”