በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የኢየሱስን ስም አጥብቆ መያዝ

የኢየሱስን ስም አጥብቆ መያዝ

ምዕራፍ 9

የኢየሱስን ስም አጥብቆ መያዝ

ጴርጋሞን

1. የሚቀጥለውን የኢየሱስ መልእክት የተቀበለው የትኛው ጉባኤ ነበር? እነዚህስ ክርስቲያኖች እንዴት ባለች ከተማ ይኖሩ ነበር?

ከሰምርኔስ ተነስተን በባሕሩ ዳርቻ አድርገን ወደ ሰሜን 80 ኪሎ ሜትር ከተጓዝን በኋላ 24 ኪሎ ሜትር ወደ መሐል አገር የካይኩስን ወንዝ ሸለቆ አቋርጠን ስንመጣ በአሁኑ ጊዜ ቤርጋማ፣ በጥንት ዘመን ደግሞ ጴርጋሞን ትባል ወደነበረችው ከተማ እንደርሳለን። ከተማዋ በውስጥዋ በነበረው የዘዩስ ወይም የጁፒተር ቤተ መቅደስ ምክንያት ዝነኛ ሆና ነበር። በ1800ዎቹ ዓመታት የመሬት ቁፋሮ አጥኚዎች የዚህን ቤተ መቅደስ መሰዊያ ወደ ጀርመን አገር ወስደውት ነበር። እስከ አሁን ድረስ በበርሊን በሚገኘው የጴርጋሞን ሙዚየም ከሌሎች ብዙ የአረማውያን አማልክት ሐውልቶችና ምስሎች ጎን ሆኖ ይታያል። ጌታ ኢየሱስ በዚያ ጣዖት አምልኮ በተስፋፋበት ከተማ ይኖር ለነበረው ጉባኤ ምን መልእክት ይልክ ይሆን?

2. ኢየሱስ ማንነቱን ያሳወቀው እንዴት ነበር? ‘በሁለት በኩል የተሳለ ሠይፍ’ መያዙስ ምን ትርጉም አለው?

2 ኢየሱስ እንደሚከተለው በማለት በመጀመሪያ ማንነቱን አሳወቃቸው። “በጴርጋሞንም ወዳለው ወደ ቤተ ክርስቲያን መልአክ እንዲህ ብለህ ጻፍ:- በሁለት ወገን የተሳለ ስለታም ሰይፍ ያለው እንዲህ ይላል።” (ራእይ 2:12) እዚህ ላይ ኢየሱስ በ⁠ራእይ 1:16 ላይ ስለራሱ የተሰጠውን መግለጫ መድገሙ ነበር። ፈራጅና ፍርድ አስፈጻሚ እንደመሆኑ መጠን ደቀ መዛሙርቱን የሚያሳድዱትን ሁሉ ይመታቸዋል። ይህ ዋስትና የጴርጋሞንን ጉባኤ በጣም የሚያጽናናው ነበር። ይሁን እንጂ ፍርድን በሚመለከት በጉባኤው ውስጥ የነበሩትም ቢሆኑ ይሖዋ ‘በቃል ኪዳኑ መልእክተኛ’ በኢየሱስ ክርስቶስ በመጠቀም ክርስቲያኖች ነን እያሉ ጣዖት በሚያመልኩ፣ ዝሙት በሚፈጽሙ፣ በሚዋሹ፣ አጭበርባሪዎች በሆኑና ችግረኞችን በማይረዱ ሰዎች ላይ ‘ፈጣን ምሥክር’ እንደሚሆንባቸው ማስጠንቀቂያ ሊሰጣቸው ይገባ ነበር። (ሚልክያስ 3:1, 5፤ ዕብራውያን 13:1-3) አምላክ በኢየሱስ በኩል የሚሰጠውን ምክርና ተግሣጽ ልብ ብሎ መቀበል ይገባቸዋል።

3. በጴርጋሞን ምን ዓይነት የሐሰት አምልኮ ይካሄድ ነበር? “የሰይጣን ዙፋን” በዚያ አለ ሊባል የቻለውስ ለምን ነበር?

3 አሁን ኢየሱስ ለጉባኤው እንዲህ አለ:- “የሰይጣን ዙፋን ባለበት የምትኖርበትን አውቃለሁ።” (ራእይ 2:13ሀ) በእውነትም እነዚህ ክርስቲያኖች በሰይጣናዊ አምልኮ ተከብበው ነበር። ከዘዩስ ቤተ መቅደስ በተጨማሪ የፈውስ አምላክ የሆነው የአዬስኩላፕየስ መስገጃ በከተማይቱ ውስጥ ይገኝ ነበር። በተጨማሪም ጴርጋሞን ለንጉሠ ነገሥቱ አምልኮ ለሚፈጸመው የምዋርት ሥርዓት ማዕከል በመሆን የታወቀች ነበረች። ሰይጣን ተብሎ የተተረጎመው የዕብራይስጥ ቃል ትርጉሙ “ተቃዋሚ” ማለት ነው። “ዙፋኑ” ደግሞ አምላክ ለጊዜው እንዲኖር የፈቀደውን የሰይጣን አገዛዝ ያመለክታል። (ኢዮብ 1:6 የአዲሲቱ ዓለም ትርጉም ባለማጣቀሻ መጽሐፍ ቅዱስ የግርጌ ማስታወሻ) በጴርጋሞን ከተማ የጣዖት አምልኮ በጣም የተስፋፋ መሆኑ የሰይጣን “ዙፋን” በዚያች ከተማ ውስጥ የጸና መሠረት የነበረው መሆኑን ያመለክታል። በዚያ ይኖሩ የነበሩት ክርስቲያኖች የብሔር አምልኮ በመፈጸም ጎንበስ ብለው ስላልሰገዱለት ሰይጣን ምን ያህል ተናድዶ ይሆን!

4. (ሀ) ኢየሱስ በጴርጋሞን የነበሩትን ክርስቲያኖች ምን ብሎ አመስግኖአቸው ነበር? (ለ) የሮማ እንደራሴ የነበረው ፕሊኒ በክርስቲያኖች ላይ ይፈጸም ስለነበረው ነገር ለንጉሠ ነገሥት ትራጃን ምን ብሎ ጽፎ ነበር? (ሐ) የጴርጋሞን ክርስቲያኖች ሕይወታቸውን አደጋ ላይ የሚጥል ሁኔታ ቢኖርም ምን ዓይነት አካሄድ ተከትለው ነበር?

4 አዎ፣ በጴርጋሞን ከተማ “የሰይጣን ዙፋን” ይገኝ ነበር። ቢሆንም ኢየሱስ ቀጥሎ እንደተናገረው “ይሁን እንጂ ስሜን አጥብቀህ ይዘሃል፤ ሃይማኖትህን አልካድህም፤ ታማኝ ምስክሬ የነበረው አንቲጳስ ሰይጣን በሚኖርበት በእናንተ ከተማ በተገደለ ጊዜ በእኔ ማመንህን አልተውህም።” (ራእይ 2:13ለ የ1980 ትርጉም) ይህ እንዴት ያለ መንፈስን የሚያነቃቃ የምሥጋና ቃል ነበር! አንቲጳስ ሰማዕት ሆኖ የተገደለው በአጋንንታዊ የአምልኮ ሥርዓቶች ባለመካፈሉና በሮማ ንጉሠ ነገሥት አምልኮ ባለመተባበሩ እንደሆነ አያጠራጥርም። ዮሐንስ ይህን ትንቢት ከመቀበሉ ብዙም ሳይቆይ የሮማው ንገሠ ነገሥት የትራጃን እንደራሴ የነበረው ታናሹ ፕሊኒ ክርስቲያኖች ናቸው ተብለው የተወነጀሉ ሰዎችን ምን እንደሚያደርግ ለትራጃን ጽፎለት ነበር። ይህንንም አድራጎቱን ንጉሠ ነገሥቱ ደግፎለት ነበር። ክርስቲያን መሆናቸውን የካዱ ሰዎች ፕሊኒ እንደተናገረው “እኔ የምለውን እየደገሙ አማልክትን ካወደሱ፣ ለምስልህ [ለትራጃን ምስል] ወይንና እጣን ከሰዉና . . . ክርስቶስን ከረገሙ በኋላ” ይለቀቁ ነበር። ክርስቲያኖች እንደሆኑ የተደረሰባቸው ሁሉ ይገደሉ ነበር። በጴርጋሞን የነበሩት ክርስቲያኖች ይህን የመሰለ አደጋ የተደቀነባቸው እንኳን ቢሆን እምነታቸውን አልካዱም። ኢየሱስ የይሖዋ ስም አስከባሪና የተሾመ ፈራጅ በመሆን የተሰጠውን ከፍተኛ ደረጃ ማክበራቸውን ስላልተዉ ‘የኢየሱስን ስም አጥብቀው ይዘው’ ነበር። የመንግሥቱ ምሥክሮች በመሆን የኢየሱስን ፈለግ በታማኝነት ተከትለዋል።

5. (ሀ) በዘመናችን በክርስቲያኖች ላይ ከባድ ስደት ያስነሳው የትኛው ዘመናዊ የንጉሠ ነገሥት አምልኮ አምሳያ ነው? (ለ) መጠበቂያ ግንብ ለክርስቲያኖች ምን ዓይነት እርዳታ ሲሰጥ ቆይቶአል?

5 ኢየሱስ በብዙ አጋጣሚዎች ይህንን ክፉ ዓለም የሚገዛው ሰይጣን እንደሆነ አሳውቆ ነበር። ኢየሱስ በፍጹም አቋሙ ስለጸና ሰይጣን በእርሱ ላይ ምንም ዓይነት ሥልጣን እንደሌለው ተናግሮአል። (ማቴዎስ 4:8-11፤ ዮሐንስ 14:30) በዘመናችን በጣም ኃያላን የሆኑት “የሰሜን ንጉሥ” እና “የደቡብ ንጉሥ” ዓለምን በቁጥጥራቸው ሥር ለማድረግ እርስበርሳቸው ተፎካክረዋል። (ዳንኤል 11:40) ዛሬ ሰዎች በአርበኝነት ስሜት እንዲቃጠሉ ተደርገዋል። በአሁኑ ጊዜ ምድርን ያጥለቀለቀው የብሔራዊ ስሜት ማዕበል በጥንት ዘመን ይፈጸም ከነበረው የንጉሥ አምልኮ ጋር ተመሳሳይነት አለው። በህዳር 1, 1939፣ በህዳር 1, 1979 እና በመስከረም 1, 1986 የመጠበቂያ ግንብ እትሞች ላይ ስለ ገለልተኝነት የወጡት ርዕሰ ትምህርቶች መጽሐፍ ቅዱስ በዚህ ጉዳይ ላይ የሚሰጠውን ትምህርት ግልጽ ስላደረጉ በይሖዋ ስም እየተመላለሱ እንደ ኢየሱስ ዓለምን በድፍረት ድል ለመንሳት ለሚፈልጉ ክርስቲያኖች ሁሉ ጠቃሚ የሆነ መመሪያ ተሰጥቶአል።—ሚክያስ 4:1, 3, 5፤ ዮሐንስ 16:33፤ 17:4, 6, 26፤ 18:36, 37፤ ሥራ 5:29

6. የይሖዋ ምሥክሮች በዘመናችን እንደ አንቲጳስ የጸና አቋም የያዙት እንዴት ነው?

6 እንዲህ ያለው ምክር በአስቸኳይ የሚያስፈልግ ነበር። በምክንያታዊነት ላይ ያልተመሠረተ የአርበኝነት ስሜት እየተጋጋለ በሄደበት ዘመን የይሖዋ ምሥክሮች በሙሉ፣ ቅቡዓንም ሆኑ ባልንጀሮቻቸው በእምነት ጠንክረው መቆም ነበረባቸው። በዩናይትድ ስቴትስ በመቶ የሚቆጠሩ ተማሪዎችና አስተማሪዎች ለብሔሩ ሰንደቅ ዓለማ ሰላምታ ባለመስጠታቸው ምክንያት ከትምህርት ቤት ሲባረሩ በጀርመን አገር ደግሞ የይሖዋ ምሥክሮች ስዋስቲካ የተባለውን ምልክት ለመሳለም እምቢተኛ በመሆናቸው ከባድ ስደት ደርሶባቸዋል። ቀደም ሲል እንደተገለጸው በሺህ የሚቆጠሩ ታማኝ የይሖዋ አገልጋዮች በብሔራዊ ስሜት አምልኮ ለመካፈል ፈቃደኛ ባለመሆናቸው በሂትለር ናዚዎች ተገድለዋል። በጃፓን አገር የሺንቶ የንጉሥ አምልኮ ከፍተኛ ደረጃ ላይ ደርሶ በነበረበት በ1930ዎቹ ዓመታት ሁለት አቅኚ አገልጋዮች በጃፓን ቅኝ ግዛት ሥር በነበረችው በታይዋን ብዙ የመንግሥት ዘር ዘርተው ነበር። ወታደራዊ መሪዎች እነዚህን አገልጋዮች ወደ እስር ቤት ከተቱአቸው። አንደኛው አገልጋይ በደረሰበት ከፍተኛ ሥቃይ ምክንያት ሞቶአል። ሁለተኛው ደግሞ ከተለቀቀ በኋላ ከጀርባው ጥይት ተተኩሶበት ሞቶአል። ዘመናዊ አንቲጳስ ሆነ። እስከ ዘመናችን ድረስ ብሔራዊ ምስሎች የሚመለኩባቸውና ለብሔሩ ፍጹም የሆነ አምልኮታዊ ተገዥነት ማሳየት ግዴታ የሆነባቸው አገሮች አሉ። ብዙ ወጣት የይሖዋ ምሥክሮች ክርስቲያናዊ ገለልተኝነታቸውን ጠብቀው በድፍረት በመቆማቸው ምክንያት ሲታሰሩ ጥቂቶች ያልሆኑ ደግሞ ተገድለዋል። እንዲህ ያለ ፈተና የሚያጋጥምህ ወጣት ከሆንህ ‘ነፍስን ጠብቆ የሚያኖረው እምነት’ እንዲኖርህ በየዕለቱ የአምላክን ቃል አጥና። የዘላለም ሕይወት ተስፋህን ጠብቀህ ለመኖር ትችላለህ።—ዕብራውያን 10:39 እስከ 11:1፤ ማቴዎስ 10:28-31

7. በሕንድ አገር የሚኖሩ ወጣቶች የብሔር አምልኮትን ፈተና የተቋቋሙት እንዴት ነው? ምን ውጤትስ ተገኘ?

7 በትምህርት ቤት ያሉ ወጣቶችም ተመሳሳይ ፈተና አጋጥሞአቸዋል። በ1985 በሕንድ አገር በኬራ ክፍለ ሀገር ውስጥ የይሖዋ ምሥክሮች ልጆች የሆኑ ሦስት ትንንሽ ወጣቶች ብሔራዊ መዝሙር በመዘመር በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሠረተውን እምነታቸውን ለማላላት እምቢተኞች ሆኑ። ሌሎች ሲዘምሩ በአክብሮት ቀጥ ብለው ቢቆሙም እንኳ ከትምህርት ቤታቸው ተባረሩ። አባታቸው ይግባኝ እያለ ጉዳዩን እስከ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ድረስ አደረሰው። የጠቅላይ ፍርድ ቤቱም ለወጣቶቹ ከመፍረዱ በተጨማሪ ሁለቱ ዳኞች በፍርድ ሐተታቸው ላይ በድፍረት እንዲህ ብለዋል:- “ባሕላችን መቻቻልን ያስተምራል፣ ፍልስፍናችን መቻቻልን ያስተምራል፣ ሕገ መንግሥታችን መቻቻልን ተግባራዊ ሲያደርግ ቆይቶአል። ይህን የጠራ አቋም አንበርዘው።” በዚህ ጉዳይ ምክንያት የተጻፉት የጋዜጦች ሐተታዎችና የርዕሰ አንቀጽ አምዶች በዚያን ጊዜ ከምድር ነዋሪዎች ውስጥ አንድ አምስተኛ የሚሆነውን ለያዘው ለዚህ አገር ሕዝብ እውነተኛውን አምላክ ይሖዋን የሚያመልኩና ለመጽሐፍ ቅዱስ ሥርዓቶች የጸና አቋም ያላቸው ሰዎች በዚህ አገር እንዳሉ እንዲያውቅ አስችለውታል።

ምግባረ ብልሹነትን የሚያመጡ ተጽእኖዎች

8. ኢየሱስ ለጴርጋሞን ክርስቲያኖች ምን የተግሣጽ ቃል መናገር አስፈልጎት ነበር?

8 አዎ፣ በጴርጋሞን የነበሩት ክርስቲያኖች ፍጹም አቋማቸውን ጠብቀዋል። ይሁን እንጂ ኢየሱስ “የምነቅፍብህ ጥቂት ነገር አለኝ” ብሎታል። ምን የሚያስነቅፋቸው ነገር አድርገው ይሆን? ኢየሱስ እንዲህ በማለት ይነግረናል:- “ዳሩ ግን ለጣዖት የታረደውን እንዲበሉና እንዲሴስኑ በእስራኤል ልጆች ፊት ማሰናከያን ሊያኖርባቸው ባላቅን ያስተማረ የበለዓምን ትምህርት የሚጠብቁ በዚያ ከአንተ ጋር” አሉ።—ራእይ 2:14

9. በለዓም ማን ነበር? እርሱስ የሰጠው ምክር ‘ለእስራኤል ልጆች ማሰናከያ’ የሆነው እንዴት ነበር?

9 በሙሴ ዘመን የሞዓብ ንጉሥ የነበረው ባላቅ ስለ ይሖዋ መንገዶች መጠነኛ ዕውቀት የነበረውን በለዓም የተባለ እሥራኤላዊ ያልሆነ ነቢይ እሥራኤላውያንን እንዲረግም ቀጥሮት ነበር። ይሖዋ ለእሥራኤላውያን በረከት ብቻ ለጠላቶቻቸው ደግሞ ወዮታ ብቻ እንዲናገር በማስገደድ በለዓምን ተቃወመው። በዚህ ምክንያት የተናደደውን ባላቅን ደስ ለማሰኘት ሲል በለዓም እሥራኤላውያን ሊጎዱ የሚችሉበትን ሥውር ዘዴ መከረው። የሞአብ ሴቶች የእሥራኤልን ወንዶች አስነዋሪ የሆነ የዝሙት ኃጢአት እንዲሰሩና የሐሰት አምላክ የነበረውን ብዔል ፌጎርን እንዲያመልኩ እንዲያስቱአቸው መከረው። ዘዴው ተሳክቶለታል። የይሖዋ የጽድቅ ቁጣ ስለነደደ መቅሰፍት ልኮ 24, 000 የሚያክሉትን ዘማውያን እሥራኤሎች ገደለ። መቅሰፍቱ የቆመው ፊንሐስ ከእስራኤል ሕዝብ መካከል ክፋትን ለማስወገድ እርምጃ በወሰደ ጊዜ ነበር።—ዘኍልቁ 24:10, 11፤ 25:1-3, 6-9፤ 31:16

10. በጴርጋሞን ጉባኤ ውስጥ እንዴት ያለ ማሰናከያ ሰርጎ ገብቶ ነበር? እነዚህ ክርስቲያኖች ሕግ መተላለፋቸውን አምላክ ችላ የሚልላቸው የመሰላቸው ለምን ነበር?

10 ታዲያ በዮሐንስ ዘመን ተመሳሳይ እንቅፋቶች በጴርጋሞን ተፈጥረው ነበርን? አዎ፣ ነበር። የሥነ ምግባር ብልግናና የጣዖት አምልኮ ወደ ጉባኤው ሰርጎ ገብቶ ነበር። እነዚህ ክርስቲያኖች አምላክ በሐዋርያው ጳውሎስ በኩል የሰጠውን ማስጠንቀቂያ ልብ አላሉም ነበር። (1 ቆሮንቶስ 10:6-11) ብዙ ስደት ተቋቁመው ስለጸኑ ይሖዋ በጾታ ሥነ ምግባር ረገድ የሚሠሩትን ጥፋት እንደማይቆጥርባቸው ተሰምቶአቸው ይሆናል። በዚህም ምክንያት ኢየሱስ እንዲህ ያለውን ክፋት ማስወገድ እንደሚኖርባቸው ግልጽ አደረገላቸው።

11. (ሀ) ክርስቲያኖች መጠበቅ የሚኖርባቸው ከምን ነገር ነው? እንዴት ያለውንስ አስተሳሰብ ማስወገድ ይኖርባቸዋል? (ለ) ባለፉት ዓመታት ምን ያህል ሰዎች ከክርስቲያን ጉባኤ ተወግደዋል? የተወገዱበትስ ምክንያት በአብዛኛው ምንድን ነው?

11 ዛሬም በተመሳሳይ ክርስቲያኖች “የአምላካችንን የማይገባ ደግነት ለሴሰኝነት ማመካኛ አድርገው እንዳይለውጡ” መጠንቀቅ ይኖርባቸዋል። (ይሁዳ 4) መጥፎ የሆነውን ሁሉ የመጥላትና በክርስቲያናዊ መልካም ሥነ ምግባር ለመመላለስ ‘ሥጋችንን እየጎሰምን የማስገዛት’ ግዴታ አለብን። (1 ቆሮንቶስ 9:27፤ መዝሙር 97:10፤ ሮሜ 8:6) በአምላክ አገልግሎት ቀናተኛ መሆንና ስደት ተቋቁሞ ፍጹም አቋምን መጠበቅ በሴሰኝነት ድርጊቶች እንድንካፈል ፈቃድ ያሰጠናል ብለን ማሰብ አይኖርብንም። ባለፉት ዓመታት በአብዛኛው በሴሰኝነት ምክንያት ከዓለም አቀፉ የክርስቲያን ጉባኤ የተወገዱት ሰዎች ብዛት በአሥር ሺህዎች የሚቆጠር ሆኖአል። በአንዳንድ ዓመታት በጥንት እስራኤላውያን መካከል ብዔል ፌጎርን በማምለካቸው ምክንያት ከተገደሉት የበለጡ ሰዎች ተወግደዋል። ከእነዚህ ሰዎች መካከል እንዳንቆጠር ራሳችንን ጠንክረን እንጠብቅ።—ሮሜ 11:20፤ 1 ቆሮንቶስ 10:12

12. በጥንት የአምላክ አገልጋዮችም ላይ ሆነ በዘመናችን ባሉት ክርስቲያኖች ላይ ተፈጻሚነት ያለው ሥርዓት ምንድን ነው?

12 በተጨማሪም ኢየሱስ በጴርጋሞን የነበሩት ክርስቲያኖች ‘ለጣዖት የተሰዋውን በመብላታቸው’ ገስጾአቸዋል። ይህ ድርጊታቸው ምን ነገሮችን የሚጨምር ነበር? ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ክርስቲያኖች ከጻፈው ለመረዳት እንደሚቻለው አንዳንዶች በክርስቲያናዊ ነፃነታቸው አለአግባብ በመጠቀም ሆን ብለው የሌሎችን ሕሊና ሳይጐዱ አልቀሩም። ከዚህም በላይ በአንዳንድ የጣዖት አምልኮ ሥርዓቶች ይካፈሉ የነበሩ ይመስላል። (1 ቆሮንቶስ 8:4-13፤ 10:25-30) ዛሬም ክርስቲያኖች በክርስቲያናዊ ነፃነታቸው በሚጠቀሙበት ጊዜ ሌሎችን ላለማደናቀፍ እየተጠነቀቁ ራስ ወዳድነት የሌለበት ፍቅር ማሳየት ይኖርባቸዋል። የቴሌቪዥን፣ የሲኒማና የስፖርት ኮከቦችን በማምለክ ወይም ገንዘብን ወይም የገዛ ራሳቸውን ሆድ አምላካቸው በማድረግ በዘመናዊ የጣዖት አምልኮ እንዳይካፈሉ መጠንቀቅ ይኖርባቸዋል።—ማቴዎስ 6:24፤ ፊልጵስዩስ 1:9, 10፤ 3:17-19

መናፍቅነትን አስወግድ!

13. ኢየሱስ በመቀጠል ለጴርጋሞን ክርስቲያኖች ምን የተግሣጽ ቃል ተናግሮአል? ጉባኤውስ ይህን መቀበል ያስፈለገው ለምን ነበር?

13 በተጨማሪም ኢየሱስ በጴርጋሞን የነበሩትን ክርስቲያኖች እንዲህ በማለት ገስጾአቸዋል:- “እንዲሁ የኒቆላውያንን ትምህርት እንደ እነዚህ የሚጠብቁ ሰዎች ከአንተ ጋር ደግሞ አሉ።” (ራእይ 2:15) ኢየሱስ ቀደም ሲል የኤፌሶንን ክርስቲያኖች የዚህን ኑፋቄ ሥራዎች በመጥላታቸው አመስግኖአቸው ነበር። በጴርጋሞን የነበሩት ክርስቲያኖች ግን ጉባኤውን ከመናፍቅነት ስለማንጻት ጉዳይ መመከር አስፈልጎአቸዋል። ኢየሱስ በ⁠ዮሐንስ 17:20-23 ላይ የጸለየለት አንድነት እንዲጠበቅ ክርስቲያናዊ የአቋም ደረጃዎችን ስለማስጠበቅ ጠንካራ አቋም መውሰድ ነበረባቸው። ‘ሕይወት በሚገኝበት ትምህርት ደግሞ መምከርና ተቃዋሚዎቹንም መውቀስ’ ያስፈልጋቸው ነበር።—ቲቶ 1:9

14. (ሀ) የክርስቲያን ጉባኤ ከጥንት ዘመናት ጀምሮ ከእነማን ጋር መታገል አስፈልጎት ነበር? እነዚህንስ ሐዋርያው ጳውሎስ የገለጸው እንዴት ነው? (ለ) የተገነጠሉ ቡድኖችን ለመከተል ያዘነበሉ ሁሉ የትኛውን የኢየሱስ ቃል መከተል ይኖርባቸዋል?

14 የክርስቲያን ጉባኤ ገና ከመጀመሪያው አንስቶ በለስላሳና በሚሸነግል አንደበታቸው ክርስቲያኖች ይሖዋ ባዘጋጀው የመገናኛ መስመር አማካኝነት የተማሩትን “ትምህርት የሚቃወሙ መለያየትንና ማሰናከያን” የሚያመጡትን ትዕቢተኛ ከሃዲዎች ለመቋቋም ተገድዶ ነበር። (ሮሜ 16:17, 18) ሐዋርያው ጳውሎስ በመልእክቶቹ ሁሉ ስለዚህ አደጋ ሳያስጠነቅቅ አላለፈም። * ኢየሱስ እውነተኛውን ጉባኤ ወደ ክርስቲያናዊ ንጽሕናና አንድነት በመለሰበት በዚህ ዘመንም ቢሆን የመናፍቅነት አሳሳቢነት ፈጽሞ አልተወገደም። ስለዚህ የተገነጠሉ ቡድኖችን ለመከተልና ኑፋቂያዊ ድርጅት ለማቋቋም አስበው የነበሩ ካሉ የሚከተለውን የኢየሱስ ቃል መፈጸም ይኖርባቸዋል:- “እንግዲህ ንሥሐ ግባ፣ አለዚያ ፈጥኜ እመጣብሃለሁ፣ በአፌም ሠይፍ እዋጋቸዋለሁ።”ራእይ 2:16

15. ኑፋቄ የሚጀምረው እንዴት ነው?

15 መናፍቅነት የሚጀመረው እንዴት ነው? አንድ የራሱን አስተሳሰብ የሚከተል አስተማሪ ነኝ ባይ አንዳንድ የመጽሐፍ ቅዱስ እውነቶችን (በመጨረሻው ዘመን ስለመኖራችን የመሰሉትን) በማስተባበል ጥርጣሬ መዝራት ይጀምር ይሆናል። በዚህ ጊዜ ጥቂት ሰዎች አንድ ቡድን ያቋቁሙና ተከታዮቹ ይሆናሉ። (2 ጢሞቴዎስ 3:1፤ 2 ጴጥሮስ 3:3, 4) አለዚያም አንድ ሰው ብድግ ይልና ይሖዋ ሥራውን የሚያስፈጽመበትን መንገድ በመተቸት የመንግሥቱን መልእክት ይዞ ከቤት ወደ ቤት መሄድ ቅዱስ ጽሑፋዊም አስፈላጊም አይደለም እያለ ምን አደከመን የሚል መንፈስ እንዲስፋፋ ያደርጋል። እንደነዚህ ያሉት ሰዎች ኢየሱስና ሐዋርያት በተካፈሉበት አገልግሎት ለመካፈል በመቻላቸው ራሳቸውን ዝቅ ሊያደርጉና የትህትና መንፈስ ሊኖራቸው ይገባ ነበር። እነርሱ ግን መገንጠልን ይመርጡና አንዳንድ ጊዜ ብቻ ተገናኝተው መጽሐፍ ቅዱስን የሚያነቡበት አነስተኛ ቡድን ያቋቁማሉ። (ማቴዎስ 10:7, 11-13፤ ሥራ 5:42፤ 20:20, 21) እንደነዚህ ያሉት ሰዎች ስለ ኢየሱስ ሞት መታሰቢያ አከባበር፣ ከደም ስለመራቅ ስለተሰጠው ቅዱስ ጽሑፋዊ ትዕዛዝ፣ ስለ በዓላት አከባበርና ስለ ትንባሆ አጠቃቀም የራሳቸው የሆነ አስተሳሰብ አላቸው። ከዚህም በላይ የይሖዋን ስም አቃልለው ይመለከታሉ። ብዙ ሳይቆዩ የታላቂቱ ባቢሎንን የልቅነት መንገድ መከተል ይጀምራሉ። ከሁሉ የሚከፋው ደግሞ አንዳንዶቹ በሰይጣን ተገፋፍተው ወንድሞቻቸው በነበሩት ላይ በመነሳት ‘ባሮቹን መማታት’ መጀመራቸው ነው።—ማቴዎስ 24:49፤ ሥራ 15:29፤ ራእይ 17:5

16. (ሀ) በከሃዲዎች ተጽእኖ ምክንያት የሚወላውሉ ሰዎች ፈጥነው ንስሐ መግባት የሚኖርባቸው ለምንድን ነው? (ለ) ንስሐ ለመግባት እምቢተኞች የሆኑ ሁሉ ምን ይደርስባቸዋል?

16 በክህደት ትምህርት ምክንያት ወዲያና ወዲህ የሚዋልሉ ሁሉ ኢየሱስ ንስሐ እንዲገቡ የሰጠውን ማስጠንቀቂያ ፈጥነው ቢቀበሉ ጥሩ ነው። የክህደት ፕሮፓጋንዳ ክፉ መርዝ ስለሆነ ሊወገድ ይገባዋል። የክህደት ፕሮፓጋንዳ ኢየሱስ ለጉባኤው ከሚመግበው ንጹሕ፣ ጻድቅና ፍቅር የሞላበት እውነት የተለየ ነው። መሠረቱም ቅንዓትና ጥላቻ ነው። (ሉቃስ 12:42፤ ፊልጵስዩስ 1:15, 16፤ 4:8, 9) ንስሐ ለመግባት አሻፈረን የሚሉትን ግን ጌታ ኢየሱስ ‘ከአፉ በሚወጣው ረዥም ሠይፍ ይዋጋቸዋል።’ ኢየሱስ በምድር ላይ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ባሳለፈው የመጨረሻ ምሽት የጸለየለትን አንድነት ለማስጠበቅ ሕዝቦቹን በማበጠር ላይ ነው። (ዮሐንስ 17:20-23, 26) ከሃዲዎች በኢየሱስ ቀኝ እጅ ያሉት ኮከቦች የሚሰጡትን በፍቅር ላይ የተመሠረተ ምክር ስለማይቀበሉ ኢየሱስ “በውጭ ወዳለው ጨለማ” አውጥቶ በመጣል ከባድ የቅጣት ፍርድ ይፈጽምባቸዋል። በአምላክ ሕዝቦች መካከል እንደ እርሾ ሆነው እንዳይበክሉ ይወገዳሉ።—ማቴዎስ 24:48-51፤ 25:30፤ 1 ቆሮንቶስ 5:6, 9, 13፤ ራእይ 1:16

‘የተሰወረ መና እና ነጭ ድንጋይ’

17. ድል የሚነሱ ቅቡዓን ክርስቲያኖች ምን ሽልማት ይጠብቃቸዋል? የጴርጋሞን ክርስቲያኖች ምን ነገር ማሸነፍ ያስፈልጋቸዋል?

17 በይሖዋ ቅዱስ መንፈስ አመራር የሚሰጠውን የኢየሱስ ምክር የሚከተሉ ሁሉ ታላቅ ሽልማት ይጠብቃቸዋል። እስቲ አድምጥ:- “መንፈስ ለአብያተ ክርስቲያናት የሚለውን ጆሮ ያለው ይስማ። ድል ለነሣው ከተሰወረ መና እሰጠዋለሁ፣ ነጭ ድንጋይንም እሰጠዋለሁ፣ በድንጋዩም ላይ ከተቀበለው በቀር አንድ ስንኳ የሚያውቀው የሌለ አዲስ ስም ተጽፎአል።” (ራእይ 2:17) ስለዚህ በጴርጋሞን የነበሩት ክርስቲያኖችም በሰምርኔስ እንደነበሩት ክርስቲያኖች ‘ድል እንዲነሱ’ ማበረታቻ ተሰጥቶአቸዋል። የሰይጣን ዙፋን በነበረበት በጴርጋሞን ይኖሩ የነበሩት ክርስቲያኖች ድል ለመንሳት ከፈለጉ ከጣዖት አምልኮ መራቅ ነበረባቸው። ከባላቅ፣ ከበለዓምና ከኒቆላውያን ትምህርት ጋር ግንኙነት የነበረውን የሴሰኝነት፣ የመናፍቅነትና የክህደት መንፈስ ማሸነፍ ነበረባቸው። እነዚህ ቅቡዓን ክርስቲያኖች ይህን ካደረጉ ‘ከተሰወረው መና’ እንዲበሉ ይጋበዛሉ። ይህ ሲባል ምን ማለት ነው?

18, 19. (ሀ) ይሖዋ ለእስራኤላውያን ይሰጣቸው የነበረው መና ምን ነበር? (ለ) የተሰወረውስ መና ምን ነበር? (ሐ) የተሰወረውን መና መብላት የምን ምሳሌ ነው?

18 ይሖዋ በሙሴ ዘመን እሥራኤላውያንን በምድረ በዳ ጉዞአቸው በሕይወት ለማቆየት መና መግቦአቸው ነበር። በሰንበት ቀን ካልሆነ በስተቀር በየጠዋቱ ሁልጊዜ ደቃቅ ውርጭ የሚመስል ቅርፊት ይታይ ስለነበር ይህ መና የተሰወረ አልነበረም። የእስራኤላውያንን ሕይወት ለመጠበቅ የተደረገ መለኮታዊ ዝግጅት ነበር። ይሖዋም ‘በእሥራኤል ትውልድ ሁሉ’ ለመታሰቢያ እንዲሆን ከዚህ መና ወስዶ በወርቅ ማሰሮ ውስጥ እንዲጨምርና በቃል ኪዳኑ ታቦት ውስጥ እንዲያስቀምጥ ሙሴን አዝዞት ነበር።—ዘጸአት 16:14, 15, 23, 26, 33፤ ዕብራውያን 9:3, 4

19 ይህ በጣም ተስማሚ የሆነ ምሳሌ ነበር። ይህ መና ለይሖዋ መገኘት ምሳሌ የሆነው ተአምራዊ ብርሃን ከታቦቱ በላይ ሆኖ ይበራ በነበረበት ቅድስተ ቅዱሳን በተባለው የቤተ መቅደሱ ውስጠኛ ክፍል ውስጥ ተደብቆ ነበር። (ዘጸአት 26:34) ማንም ሰው ወደዚህ ቅዱስ ሥፍራ እንዲገባና ከተሰወረው መና እንዲበላ አይፈቀድለትም ነበር። ኢየሱስ ግን ድል ያደረጉ ቅቡዓን ተከታዮቹ ከተሰወረው መና እንደሚበሉ ተናግሮአል። ክርስቶስ ከእነርሱ በፊት እንዳደረገው “በእጅ ወደ ተሠራች የእውነተኛይቱ ምሳሌ ወደምትሆን ቅድስት” ሳይሆን ወደ ሰማይ ይገባሉ። (ዕብራውያን 9:12, 24) ከሙታን በሚነሱበት ጊዜ ያለመበስበስንና ያለመሞትን ባሕርይ ይወርሳሉ። ይህም አስደናቂ የሆነ የይሖዋ ዝግጅት የማይበላሸውን “የተሰወረ መና” በመቀበላቸው ተመስሎአል። እነዚህ በቁጥር አነስተኛ የሆኑት ድል ነሺዎች በጣም ታላቅ የሆነ መብት ያገኛሉ።—1 ቆሮንቶስ 15:53-57

20, 21. (ሀ) ለቅቡዓን ክርስቲያኖች ነጭ ጠጠር መስጠት የምን ምሳሌ ነው? (ለ) የነጮቹ ጠጠሮች ብዛት 144, 000 ብቻ ስለሆነ እጅግ ብዙ ሰዎች ያላቸው ተስፋ ምንድን ነው?

20 በተጨማሪም እነዚህ ድል አድራጊዎች “ነጭ ድንጋይ” ይቀበላሉ። በሮማ ፍርድ ቤቶች የፍርድ ውሣኔ ሲሰጥ በጠጠር መጠቀም የተለመደ ነበር። * ነጭ ጠጠር ነጻ መሆንን የሚያመለክት ሲሆን ጥቁር ጠጠር ደግሞ ጥፋተኛ ነህ የሚል ፍርድ፣ አብዛኛውን ጊዜ የሞትን ፍርድ ያመለክት ነበር። ኢየሱስ በጴርጋሞን ለነበሩት ክርስቲያኖች “ነጭ ድንጋይ” [ወይም “ጠጠር፣” NW] መስጠቱ ንፁሕ፣ ነቀፋና ነውር የሌለባቸው ናቸው ብሎ እንደፈረደላቸው ያመለክታል። ይሁን እንጂ የኢየሱስ ቃል ሌላም ተጨማሪ ትርጉም ሊኖረው ይችላል። በሮማውያን ዘመን ጠጠር በጣም ታላቅ ወደሆነ ዝግጅት እንደሚያስገባ ቲኬት ሆኖ ያገለግል ነበር። ስለዚህ አንድ ድል አድራጊ ቅቡዕ ክርስቲያን ነጭ ጠጠር መቀበሉ በበጉ ሠርግ ጊዜ በሰማይ ላይ ልዩ የክብር ቦታ እንዲያገኝ የመፈቀዱን በጣም ልዩ የሆነ መብት ሊያመለክት ይችላል። የእነዚህ ጠጠሮች ወይም ድንጋዮች ብዛት 144, 000 ብቻ ነው።—ራእይ 14:1፤ 19:7-9

21 ታዲያ አንተ የቅቡዓኑ ተባባሪ አምላኪዎች የሆኑት እጅግ ብዙ ሰዎች ክፍል ከሆንክ ጨርሶ ተጥለሃል ማለት ነውን? በፍጹም አይደለም። ወደ ሰማይ የሚያስገባው ነጭ ድንጋይ ባይሰጥህም ጸንተህ ከቆምክ ከታላቁ መከራ አልፈህ ገነትን በምድር ላይ መልሶ ለመመሥረት በሚደረገው አስደሳች ሥራ ልትካፈል ትችላለህ። በዚህም ሥራ ከሙታን የሚነሱት ከክርስትና በፊት የነበሩ ታማኝ ሰዎችና በቅርብ ጊዜያት የሞቱ የሌሎች በጎች ክፍል አባላት የሆኑ ሰዎች አብረውህ ይካፈላሉ። የክርስቶስ ቤዛ ተጠቃሚ የሆኑ ሰዎች በየተራ ከሙታን ተነስተው በመጨረሻ ሁሉም በገነቲቱ ምድር የመኖር ዕድል ያገኛሉ።—መዝሙር 45:16 የ1980 ትርጉም፤ ዮሐንስ 10:16፤ ራእይ 7:9, 14

22, 23. ለቅቡዓን ክርስቲያኖች በሚሰጠው ጠጠር ላይ የተጻፈው ስም ትርጉም ምንድን ነው? ይህስ እንዴት ያለ ማበረታቻ ሊሰጣቸው ይገባል?

22 በድንጋዩ ላይ የተጻፈው አዲስ ስም ምንድን ነው? ስም አንድ ሰው የሚታወቅበትና ከሌሎች የሚለይበት ነገር ነው። እነዚህ ቅቡዓን ክርስቲያኖች ጠጠሩን የሚቀበሉት ምድራዊ ሥራቸውን በድል አድራጊነት ከጨረሱ በኋላ ነው። ስለዚህ በጠጠሩ ላይ ያለው ስም በሰማይ ከኢየሱስ ጋር የመሆን መብታቸውን የሚያመለክት ነገር መሆን ይኖርበታል። ይህም መብት ሰማያዊውን መንግሥት የሚወርሱት ብቻ የሚያውቁትና የሚቀበሉት በጣም ልዩ የሆነ ቅርርብ ያለበት የቅዱስ አገልግሎት ደረጃ ነው። ስለዚህ ‘ከሚቀበለው በስተቀር ማንም የማያውቀው’ ስም ወይም የማዕረግ ስያሜ ነው።—ከ⁠ራእይ 3:12 ጋር አወዳድር።

23 ይህም የዮሐንስ ክፍል የሆኑት “መንፈስ ለአብያተ ክርስቲያናት የሚለውን” እንዲሰሙና በሥራ እንዲያውሉ የሚያነሳሳቸው እንዴት ያለ ጠንካራ ምክንያት ነው! በተጨማሪም ባልንጀሮቻቸው የሆኑት እጅግ ብዙ ሰዎች በዚህ ምድር ላይ አብረዋቸው እስካሉ ድረስ ከእነርሱ ጋር በመተባበር በታማኝነት እንዲያገለግሉና የይሖዋን መንግሥት በማሳወቁ ሥራ እንዲካፈሉ የሚገፋፋቸው ጠንካራ ምክንያት ነው።

[የግርጌ ማስታወሻዎች]

^ አን.20 በባለ ማጣቀሻው አዲሲቱ ዓለም ትርጉም ሥራ 26:10ንና የግርጌ ማስታወሻውን ተመልከት።

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]

[በገጽ 43 ላይ የሚገኙ ሥዕሎች]

የጣዖት አምልኮ ምን ያህል የተስፋፋ እንደነበረ የሚያሳዩ እነዚህ ማስረጃዎች በበርሊን በሚገኘው በጴርጋሞን ሙዚየም ውስጥ ይታያሉ

[በገጽ 45 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

በቃል ኪዳኑ ታቦት ውስጥ ጥቂት መና ተደብቆ ነበር። ድል ለነሱት ቅቡዓን የተሰወረ መና መሰጠቱ ያለመሞትን ባሕርይ እንደሚወርሱ ያመለክታል

[በገጽ 45 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ነጩ ድንጋይ የሚሰጠው ወደ በጉ ሠርግ እንዲገቡ ለተፈቀደላቸው ነው