በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ለሚመለሱት የሚደረግ የሞቀ አቀባበል

ለሚመለሱት የሚደረግ የሞቀ አቀባበል

ምዕራፍ 21

ለሚመለሱት የሚደረግ የሞቀ አቀባበል

1. በዚህ ምዕራፍ ውስጥ ስለ ምን ዓይነት ሰዎች እንወያያለን?

ብዙ ሰዎች ባለፉት ጊዜያት ከመጽሐፍ ቅዱስ እውነት ጋር በቂ ግንኙነት ስለነበራቸው እውነተኛው አምላክ ይሖዋ መሆኑን ለማወቅና ስለ ዓላማዎቹም አንዳንድ ግንዛቤዎችን ለማግኘት ችለው ነበር። የይሖዋ ምሥክሮች ባይሆኑም ከምሥክሮቹ ጋር መጽሐፍ ቅዱስን አጥንተው ይሆናል። ወይም ምናልባት ወላጆቻቸው ምሥክሮች ኖረው ይሆናል። ብዙዎቹ በመንግሥት አዳራሽ በሚደረጉት አንዳንድ ስብሰባዎች ተገኝተዋል። ምናልባትም የመንግሥቱን መልእክት ለሌሎች ለማሰማት በመጠኑ ተሳትፈው ይሆናል። ይሁን እንጂ ሕይወታቸውን የአምላክን ፈቃድ በማድረጉ ላይ ለማዋል አልወሰኑም ነበር። ለምን?

2. (ሀ) ከይሖዋ ድርጅት ወጥተው የሄዱት ለምንድን ነው? (ለ) የመመለስ ምኞት ያደረባቸውስ ለምንድን ነው?

2 ዓለም ጠቃሚ የሚመስሉ ማራኪ ነገሮችን ታቀርብላቸዋለች። ለሕይወታቸው ደስታ የሚጨምሩ የሚስሉ ነገሮች ሲቀርቡላቸው እነዚህን ነገሮች ለማሳደድ ከይሖዋ ድርጅት ወጥተው ይሄዳሉ። ከጊዜ በኋላ ግን አንዳንዶቹ የጠበቁትን ዓይነት ሕይወት እንዳላገኙ ይመለከታሉ። ከእንቅልፍ ይነቁና አሁን ባሉበት ሁኔታ ከቀጠሉ ከዓለም ጋር እንደሚጠፉ ትዝ ይላቸዋል። በይሖዋ “ቤት” አግኝተውት የነበረው የደኅንነት ስሜትና መንፈሳዊ ብልጽግና ከአእምሯቸው ስላልወጣ ወደዚያ ለመመለስ ይፈልጋሉ። ግን ይሖዋ ይቀበላቸው ይሆን?

አባካኝ የነበረ ልጅ ተመለሰ

3. (ሀ) በአባካኙ ልጅ ምሳሌ ላይ ኢየሱስ ስለ ተመሳሳይ ሁኔታ ምን ብሎ ገልጿል? (ለ) አባትየው የማን ምሳሌ ነው?

3 ኢየሱስ ስለ አንድ አባካኝ ልጅ በተናገረው የታወቀ ምሳሌ ላይ የዚህ ጥያቄ መልስ ተጠቁሞልናል። ኢየሱስ ሁለት ልጆች ስለነበሩት ሰው የሚገልጽ ምሳሌ ተናገረ። ታናሹ ልጅ ከሀብቱ የሚደርሰውን እንዲሰጠው አባቱን ጠየቀው። ድርሻውን ካገኘ በኋላ ወደ ሩቅ አገር ሄዶ ገንዘቡን ሁሉ በጭፈራና በግድ የለሽነት ጨረሰ። ስለዚህ አባካኝ ሆነ ማለት ነው። ልጁ የሄደበት አገር በረሃብ በተጠቃ ጊዜ ግን ጭንቅ ያዘውና የእሪያዎች ጠባቂ ሆነ። ነገር ግን ከእሪያዎቹ መኖ እንኳን ለመብላት አይፈቀድለትም ነበር። ስለዚህ ችግሩ አነቃውና ወደ አእምሮው ተመለሰ። በአባቱ ቤት ያሉ አገልጋዮች እንኳን እንዴት ጥሩ ሆነው እንደሚኖሩ ትዝ ሲለው ለመመለስ ቆረጠ። ኃጢአት ሠርቻለሁ ብሎ ለማመንና እንደ ልጅ ሳይሆን እንደ አገልጋይ አድርጎ አባቱ እንዲቀበለው ለመማጸን ወሰነ። (ሉቃስ 15:11–19) ይሁን እንጂ ይህን ሁሉ በደል ከፈጸመ በኋላ አባቱ እንዲመለስ ይፈቅድለት ይሆን? በዚህ ምሳሌ ላይ እንደ አባት ሆኖ የተገለጸው ይሖዋ የእንዲህ ዓይነቱን ሰው መመለስ እንዴት ይመለከተዋል?

4. ልጁ በተመለሰ ጊዜ አባቱ አንዴት ተቀበለው?

4 ኢየሱስ በመቀጠል በነገሩ ላይ የይሖዋን ስሜት ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ሐሳብ ተናገረ:- “እርሱም [ታናሹ ልጅ] ገና ሩቅ ሳለ አባቱ አየውና አዘነለት፣ ሮጦም አንገቱን አቀፈውና ሳመው። ልጁም:- አባቴ ሆይ በሰማይና በፊትህ በደልሁ፤ ወደ ፊትም ልጅህ ልባል አይገባኝም [“ከሞያተኞችህ እንደ አንዱ አድርገኝ” አዓት ] አለው። አባቱ ግን ባሪያዎቹን አለ:- ፈጥናችሁ ከሁሉ የተሻለ ልብስ አምጡና አልብሱት፣ ለእጁ ቀለበት ለእግሩም ጫማ ስጡ፤ የሰባውንም ፍሪዳ አምጥታችሁ እረዱት፣ እንብላም ደስም ይበለን፤ ይህ ልጄ ሞቶ ነበርና ደግሞም ሕያው ሆኖአል፤ ጠፍቶም ነበር ተገኝቶአልም። ደስም ይላቸው ጀመር።” — ሉቃስ 15:20–24

ይህ ምሳሌ ዛሬ እንዴት ይሠራል?

5. (ሀ) በኢየሱስ ምሳሌ ውስጥ በተጠቀሰው ታላቅ ልጅ የተመሰሉት እነማን ናቸው? (ለ) እንግዲያው በአባካኙ ታናሽ ልጅ የተመሰሉት እነማን ናቸው?

5 በዚህ ምሳሌ ላይ ታላቁ ወይም የበኩሩ ልጅ ‘በሰማይ የተጻፉትን የበኩራት ማኅበር’ በትክክል ይወክላል። (ዕብራውያን 12:23) ታናሹስ ልጅ? ሰማያዊ ተስፋ ካላቸው “ታናሽ መንጋ” የተለየ ቡድን የሚያመለክት መሆን ይኖርበታል። ስለ ታናሹ ልጅ የተሰጠው መግለጫ በሁሉም የጌታ “ሌሎች በጎች” ላይ አይሠራም። በአንዳንዶች ላይ ግን ይሠራል። ሌሎች በጎች መሰብሰብ እንዳለባቸው በግልጽ ከታወቀበት ከ1935 በፊትም ቢሆን እውነተኛው አምላክ ይሖዋ ብቻ መሆኑን የሚያውቁ ሰዎች ነበሩ። በአምላክ መንግሥት ሥር ምድራዊ ሕይወት እንደሚኖር ያውቁ ነበር። እነዚህ ሰዎች የሰማያዊ ሕይወት ተስፋ ያላቸው “የበኩራት ማኅበር” ክፍል እንደሆኑ አድርገው አያስቡም ነበር። ሆኖም ራሳቸውን ለይሖዋ አገልግሎት በመወሰን ፋንታ በዓለማዊ ነገሮች ተዋጡ። አምላክ የሰጣቸውን “ድርሻ” ማለትም እንዲጠቀሙበት የፈቀደላቸውን ጊዜና ሕይወት በራስ ወዳድነት ለግል ጥቅም ብቻ አውለውት ነበር። ነገር ግን በ1935 የይሖዋ አገልጋዮች ለመጀመሪያ ጊዜ “እጅግ ብዙ ሰዎች” እነማን እንደሆኑ ሲብራራላቸው ታናሹን ልጅ የሚመስሉ ብዙ ሰዎች በአባታቸው ቤት ለማገልገል በሙሉ ልባቸው ተነሳስተው ራሳቸውን አቀረቡ። ያ ጊዜ ኢየሱስ በምሳሌው ላይ እንደገለጸው የደስታ ጊዜ ሆነ።

6. በአፈጻጸሙ ላይ አንዳንድ ሰዎች የትልቁን ልጅ ዝንባሌ ያሳዩት እንዴት ነው? ይሁን እንጂ የሁሉም ቀሪዎች ሁኔታ እንደዚያ ነበርን?

6 እውነትም በዚያን ጊዜ በታናሹ ልጅ የተመሰለው ቡድን ሲመለስ ሁሉም የደስታው ተካፋይ አልሆነም። ይህ እንደሚሆን ኢየሱስ በምሳሌው ላይ አመልክቶ ነበር። ይሁን እንጂ ‘የታናሹ መንጋ’ ቀሪዎች በሙሉ እንደዚህ ያለ መንፈስ አላሳዩም። ኢየሱስ በምሳሌው ላይ እንደነዚህ ያሉ ኃጢአተኞች ከልብ ሲመለሱ በመጀመሪያ ደስ ያላላቸውም እንኳ ከይሖዋ ጋር በደስታው ለመካፈል በሩ ክፍት እንደሚሆንላቸው ገልጿል። — ሉቃስ 15:7, 10, 25–32

7, 8. (ሀ) በቅርብ ዓመታት አንዳንዶች ከይሖዋ ቤት ወጥተው እንዲሄዱ ያደረጋቸው ምንድን ነው? (ለ) አንዳንዶቹ እንደ አባካኙ ልጅ እንደሆኑ የተሰማቸው በምን መንገዶች ነው? (ሐ) መመለስ የሚያስፈልጋቸው ለምንድን ነው?

7 ይሁን እንጂ በ1930ዎቹ አጋማሽ ላይ ከታዩት ክስተቶች ጀምሮ በአንዳንድ መንገድ እንደ አባካኙ ልጅ መሆናቸውን የተገነዘቡ ሌሎች ሰዎች ታይተዋል። ስለ ይሖዋ መንፈሳዊ ቤተሰብ ማለትም ስለሚታየው ደርጅቱ ጠንቅቀው ያውቃሉ፤ ነገር ግን “ወደ ሩቅ አገር” እንደሄዱ ያህል በአኗኗራቸው ከድርጅቱ ርቀው ሄደው ነበር። የይሖዋን አገልጋዮች አልተቃወሙም፤ ቢሆንም፣ አኗኗራቸው በአምላክ ቃል ውስጥ ካሉት የአቋም መስፈርቶች ጋር የሚስማማ አልነበረም። ጠቅላላ ሕይወታቸውን በሰብዓዊ ሥራቸውና በራሳቸው ዙሪያ በመገንባት በአምላክ ፊት ላለባቸው ግዴታና ለምንኖርባቸው ጊዜያት አጣዳፊነት ተገቢ ክብደት ሳይሰጡ ቀሩ። አንዳንዶቹ በወቅቱ በጉባኤው ውስጥ የነበሩ ሰዎች ባሳዩት አለፍጽምና ተጎዱ፤ ይሖዋ ነገሮችን እስኪያርማቸው ድረስ ግን በትዕግሥት አልጠበቁም። ይሁን እንጂ እነዚህ ሁሉ ከእምነት ቤተሰብ ራሳቸውን ካገለሉ በኋላ ምን ዓይነት ሁኔታ አጋጠማቸው?

8 ከጊዜ በኋላ አንዳንዶቹ በመንፈሳዊ እንደደኸዩ ተገነዘቡ። ምንም እንኳ ለጊዜው የደስታ ጊዜ ቢያሳልፉም ዘላቂ ደስታ እንዳልጨበጡ ለማየት ቻሉ። አኗኗራቸው በአካል፣ በስሜትና በመንፈሳዊ እንደጎዳቸውም ተረድተው ይሆናል። ያለ አምላክና ያለ ተስፋ እንደሚኖሩት ሰዎች እነርሱም በውስጣቸው ባዶነት ተሰምቷቸዋል። (ኤፌሶን 2:12) እውነተኛ ደስታ ያገኙት በይሖዋ “ቤት” ሳሉ ብቻ እንደነበረ ትዝ አላቸው። ስለዚህ ለመመለስ ፈለጉ። ታዲያ መመለስ ይገባቸዋልን? በጐስቋላ ሁኔታቸው ቢቀጥሉ ምን ጥቅም ሊያገኙ ይችላሉ? መዘግየቱ ሌላ ጣጣ ሊያመጣ ይችላል። ከዓለም ጋር የሙጥኝ ብለው ከቀጠሉ ዓለም በሚጠፋበት ጊዜ እነርሱም ሕይወታቸውን ያጣሉ።

9. (ሀ) ይሖዋ እንደነዚህ ያሉ ሰዎች እንዲመለሱ የሚፈልገው ለምንድን ነው? (ሕዝቅኤል 18:23) (ለ) በበኩላቸውስ ምን ማድረግ ይኖርባቸዋል?

9 ይሁን እንጂ እንደነዚህ ያሉ ሰዎች ሊመለሱ ይችላሉን? ይሖዋ እንዲመለሱ ሞቅ ያለ ጥሪ ያቀርብላቸዋል፤ የሚታየው ድርጅቱም ለሚመለሱ ሁሉ ፍቅራዊ እርዳታ ያደርጋል። (ዘካርያስ 1:3, 4) የሚያስፈልገው ምንድን ነው? በኢየሱስ ምሳሌ ላይ እንደተገለጸው ወደ ልባቸው መመለስ፣ በራስ አነሳሽነት ጉዞውን መጀመርና በይሖዋ ላይ ኃጢአት መሥራታቸውን አምነው መቀበል ይገባቸዋል። ክርስቲያናዊ ያልሆነ መጥፎ ጠባይ ተጠናውቷቸው ከነበረም ይህን ጠባይ እርግፍ አድርገው ለመተዋቸውና በእውነት ንስሐ ለመግባታቸው አሳማኝ ማስረጃ ለሽማግሌዎች ማሳየት ይኖርባቸዋል። ከዚህ በኋላ በጥብቅ የሚፈልጉት ነገር የይሖዋ ድርጅት አባል ሆነው ይሖዋን ማገልገል መሆን ይኖርበታል። (ሉቃስ 15:18–21፤ ምሳሌ 28:13) በልባቸው ያለው ፍላጎት በእርግጥ ይህ ከሆነ መጥፎ ሥራቸውንና ሐሳባቸውን ትተው ወደ ይሖዋ መመለሳቸው ታላቅ ደስታ እንደሚያመጣላቸው እርግጠኞች ሊሆኑ ይችላሉ። (ኢሳይያስ 55:7) ይሁን እንጂ ደስታቸው በመንግሥት አዳራሹ በሚደረግላቸው ሞቅ ያለ አቀባበል ብቻ እንዳይቀር መንፈሳዊነታቸው በደንብ መጠገን ይኖርበታል።

በጥሩ መሠረት ላይ መገንባት

10. (ሀ) ንስሐ የሚገቡ ሁሉ ይሖዋ እንዲያሟሉ ለሚፈልግባቸው ብቃቶች ምን ዝንባሌ መያዝ አለባቸው? (ለ) ከይሖዋ ጋር የጠበቀ የግል ዝምድና መኮትኮት የሚችሉት እንዴት ነው?

10 ወደ ይሖዋ ቤተሰብ የሚመለሱ ሁሉ በተለይ የሚያስፈልጋቸው፣ የይሖዋን ባሕርያት የተለያዩ ገጽታዎች ጥሩ አድርጎ ማወቅና ከእርሱም ጋር የጠበቀ ግላዊ ዝምድና ኮትኩቶ ማሳደግ ነው። ይሖዋ እንድናደርገው የሚጠይቀን ነገር ሁሉ ለራሳችን ጥቅም መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋቸዋል። የእርሱ ትእዛዛት ከሕይወታችን ውስጥ ደስታን የሚነጥቁን አይደሉም። ከዚህ ይልቅ ጊዜያዊ ደስታን ሰጥተው በመጨረሻው መራራ ፍሬን የሚያሳጭዱ ነገሮችን ከማድረግ ይጠብቁናል። (ኢሳይያስ 48:17፤ ገላትያ 6:7, 8) ይሖዋ የሚገሥጸን ለእኛ ካለው ፍቅር የተነሳ ነው። (ምሳሌ 3:11, 12) የግል ጥናት፣ ያጠናነውን ማሰላሰል፣ ልባዊ ጸሎትና ዘወትር በስብሰባ መገኘት በይሖዋ ላይ ሙሉ በሙሉ መደገፍንና ምንም ነገር ከማድረጋችን በፊት መመሪያውን ለማወቅ መጣርን እንድንለምድ ይረዱናል። — ምሳሌ 3:5, 6

11. የባዘኑ ሰዎች (ሀ) በውስጣቸው ለክፋት ጥላቻ መኮትኮት (ለ) ነገሮችን ለመረዳት መጣር (ሐ) አምላካዊ የሥነ ምግባር መስፈርቶችን ዘወትር በሥራ ላይ ማዋል (መ) ሊያደርጉት ያቀዱት ነገር የሚያስከትለውን ውጤት ማጤንን መልመድ (ሠ) ለሌሎች በፍቅር ማሰብ የሚረዳቸው እንዴት ነው?

11 ባዝነው የነበሩት ሰዎች ምን ነገሮች ትክክል ወይም ስሕተት እንደሆኑ ያውቁ ይሆናል። አሁን ግን በልባቸው ውስጥ ለክፋት ጥላቻ መኮትኮትና ክፋት በዙሪያቸው እስካለ ድረስ እንደዚያ ማድረጋቸውን መቀጠል ይኖርባቸዋል። (መዝሙር 97:10) እውቀት ለማግኘት ብቻ ሳይሆን ነገሮችን ለመረዳት መጣራቸው ለዚህ ይረዳቸዋል። ይህ ማለት በመጀመሪያ ነገሮችን ከአምላክ ጋር እያገናዘቡ ማየት አለባቸው ማለት ነው። ይሖዋ እኛን ለማስተማር የሚጠቀምባቸውን የተለያዩ መንገዶች መቀበልና ለምክሩ የምናሳየው ስሜት ከእርሱ ጋር ያለንን ዝምድና እንዴት እንደሚነካው ማወቅ ያስፈልገናል። (ምሳሌ 4:7፤ 9:10) አቋማችን የሚወላውል መሆን የለበትም፤ በማናቸውም ጊዜና ሁኔታ የምናደርገው ሁሉ የይሖዋን የአቋም መሥፈርት የሚያሟላ መሆን እንዳለበት መርሳት የለብንም። (ቲቶ 2:11, 12፤ 1 ተሰሎንቄ 4:7) ልናገኝ የምንችለው ጊዜያዊው ደስታ ብቻ ሳይሆን ውሳኔአችን በመጨረሻ የሚያስከትለው ውጤት ቁልጭ ብሎ እንዲታየን ጠንቃቆች መሆን አለብን። (ከምሳሌ 20:21፤ ከ23:17, 18ና ከዕብራውያን 11:24–26 ጋር አወዳድር።) ከዚህም ሌላ የምንናገራቸውና የምናደርጋቸው ነገሮች በሌሎች ላይ ስለሚያመጡት ውጤት በፍቅር ተገፋፍተን ማሰብ ያስፈልገናል። — ሮሜ 15:1, 2

12. (ሀ) ስለ ሰይጣንና ስለ ዘዴዎቹ ምን ማወቃችን ጥበቃ ይሆንልናል? (ለ) በዚህ ውጊያ ለማሸነፍ ምን ያስፈልገናል?

12 ክርስቲያኖች እንደመሆናችን መጠን በመንፈሳዊ ውጊያ ውስጥ እንደምንገኝ ማስታወሳችን እጅግ ያበረታናል። ቀንደኛው ጠላታችን ሰይጣን ዲያብሎስ ነው፤ አጋንንቱም እንደዚሁ ጠላቶቻችን ናቸው። ሰይጣን በሆነ ዘዴ ተጠቅሞ ይሖዋ ከሰጠን ሥራ ሊያፈናቅለን ይፈልጋል። እንደ ምንም አዘናግቶ የይሖዋን የሥነ ምግባር መስፈርት ገሸሽ እንድናደርግና እርሱ ገዥ የሆነለት ዓለም ክፍል እንድንሆን ይጥራል። የእርሱ ወጥመዶች ብዙውን ጊዜ ተገቢ ለሆኑት የተፈጥሮ ምኞቶች (ይኸውም ለደስታ፣ ለሥጋዊ ምቾት፣ ለፍቅርና ለመወደድ) የሚጋብዙ ናቸው። ሆኖም እንደነዚህ ያሉት ምኞቶች ዓላማቸውን ስተው ትልቅ ትኩረት እንድንሰጣቸው ወይም ተገቢ ባልሆኑ መንገዶች እንድንፈጽማቸው ይገፋፋናል። ለመንፈሳዊ ሕይወታችን በምናደርገው በዚህ ውጊያ አሸናፊዎች ሆነን ልንወጣ የምንችለው አምላክ ባዘጋጀልን መንፈሳዊ የጦር መሣሪያዎች ሁሉ በመጠቀም ብቻ ነው። — ኤፌሶን 6:11–18

13. (ሀ) ለነፍሳችን ዕረፍት ማግኘት የምንችለው እንዴት ነው? (ለ) ክርስቶስን በመምሰል ይሖዋን ማገልገል በእርግጥ ደስታ የሚያመጣልን ለምንድን ነው?

13 ወደ እርሱ ብንቀርብና ‘ቀንበሩን’ ብንሸከም ለነፍሳችን እረፍት እንደምናገኝ’ ኢየሱስ ተናግሯል። (ማቴዎስ 11:29, 30) ‘ቀንበር’ መሸከም ደግሞ ማገልገል ማለት ነው። ቢሆንም የልጁን ፈለግ በመከተል ይሖዋን ማገልገል እውነተኛ እረፍት ይሰጣል። እንዴት? ምክንያቱም እውነተኛ ነፃነት ስለሚያመጣ ነው። የኃጢአት ባሪያዎች ወይም እስረኞች መሆናችንን አቁመናል፤ ማድረግ እንደሌለብን የምናውቃቸውን፣ ምናልባትም ማድረግ የማንፈልጋቸውን ነገሮች መፈጸምን ትተናል። (ዮሐንስ 8:32, 34–36) ኢየሱስ ክርስቶስን መሠረት በማድረግ ክርስቲያናዊ ባሕርያችንን በእርሱ ላይ ከገነባን እርሱ በይሖዋ ዓላማ ውስጥ ያለውን ቦታ እንቀበላለን፣ እናዳምጠዋለን፣ ከእርሱም እንማራለን። እርሱ የአባቱን ፈቃድ ማድረግ ያስደስተው ነበር። እኛም ይህን እንማራለን። (ዮሐንስ 4:34፤ መዝሙር 40:8) የአምላክን የሥነ ምግባር መሥፈርቶች ለማሟላት አጥብቀን ስንጥር ንጹሕ ኅሊና እናገኛለን። ለራስ ብቻ ከመኖር ይልቅ፣ መስጠት ከሚያስገኘው ደስታ ተካፋይ እንሆናለን። (ሥራ 20:35) ሕይወት እውነተኛ ዓላማ ያለው ይሆንልናል። ከሁሉም በላይ ግን፣ ልጆቹ ለሚሆኑት ሁሉ አባት የሚሆነው ይሖዋ ሞገሱን እንደሰጠን ይታወቀንና ደስ ይለናል። — ምሳሌ 10:22

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]