በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

‘ታናሹ ብርቱ ብሔር ሆነ’

‘ታናሹ ብርቱ ብሔር ሆነ’

ምዕራፍ 20

‘ታናሹ ብርቱ ብሔር ሆነ’

1. (ሀ) የእውነተኛ አምላኪዎቹ ቁጥር ስለመጨመሩ ይሖዋ አስቀድሞ ምን ብሎ ነበር? (ለ) ይህን ጭማሪ የሚያመጣው ማን ነው? እንዴትስ?

ይሖዋን የሚያመልኩ ሰዎች ከአጠቃላዩ ሕዝብ ጋር ሲወዳደሩ በቁጥር ምን ጊዜም አናሳ ናቸው። በጊዜያችን ግን ጽድቅ ወዳዶችን በደስታ በሚያስፈነድቅ ሁኔታ ቁጥራቸው በፍጥነት እያደገ ነው። ይሖዋ ስለ እድገቱ መጠን ሲናገር “ታናሹ ሺህ፣ የሁሉም ታናሽ ብርቱ ብሔር ይሆናል፣ እኔ ይሖዋ በዘመኑ ይህን አፋጥነዋለሁ” ብሏል። (ኢሳይያስ 60:22 አዓት) ጥቅሱ እንደሚገልጸው ይህን የሚያደርገው ይሖዋ ራሱ ነው። እንዴት? አገልጋዮቹ በዙሪያቸው ካሉት ብሔራት በጣም ልዩ የሚሆኑበትና ቅን ልብ ያላቸውን ሁሉ የሚስብ ሁኔታ እንዲኖር በማድረግ ነው።

2. (ሀ) ኢሳይያስ 60:1, 2 የሚናገረው ለማን ነው? (ለ) “የይሖዋ ክብር” በእርሷ ላይ የበራው በምን መንገድ ነው? (ሐ) ቀሪዎቹ ‘ብርሃን ያበሩት’ እንዴት ነው?

2 ይህ ሁኔታ በኢሳይያስ 60:1, 2 ላይ አስቀድሞ ተገልጿል። በዚያ ጥቅስ ላይ ይሖዋ የእርሱን “ሴት” ማለትም ታማኝ መንፈሳውያን ፍጡሮቹንና በምድር ላይ ያሉትን በመንፈስ የተወለዱ ልጆቹ ያቀፈውን ድርጅቱን አስመልክቶ እንዲህ ብሏል:- “ብርሃንሽ መጥቶአልና፣ የእግዚአብሔርም ክብር ወጥቶልሻልና ተነሺ አብሪ። እነሆ፣ ጨለማ ምድርን ድቅድቅ ጨለማም አሕዛብን ይሸፍናል፤ ነገር ግን በአንቺ ላይ እግዚአብሔር ይወጣል ክብሩም በአንቺ ላይ ይታያል።” ለዚህ ጉልህ ልዩነት መሠረት የሚሆነው በኢየሱስ ክርስቶስ የምትመራዋ መሲሐዊት መንግሥት በ1914 መወለዷ ነው። በዚያን ጊዜ መንግሥቲቱን በወለደችው ሰማያዊት ድርጅቱ ላይ “የይሖዋ ክብር” [አዓት ] አብርቷል። ይህም ታላቅ ደስታ እንዲሰማቸው ምክንያት ሆኖላቸዋል። (ራእይ 12:1, 2, 5, 10–12) በምድርም ላይ የመንግሥቱ ወራሽ የሆኑት ቅቡዓን ቀሪዎች የዚህ ደስታ ተካፋይ ሆነዋል። ከ1919 መባቻ ጀምሮ እነርሱም የአምላክ መንግሥት እውነተኛና ብቸኛዋ የሰው ዘር ተስፋ እንደሆነች በማወጅ ብርሃን ፈንጥቀዋል። — 1 ጴጥሮስ 2:9፤ ማቴዎስ 5:14–16

3. (ሀ) በተለይ ከ1914 ጀምሮ ‘ጨለማ ምድርን የሸፈናት’ ለምንድን ነው? (ለ) እውነተኛው መፍትሔ ምን ብቻ ነው?

3 በተቃራኒው ደግሞ በ1914 የዓለም ብሔራት የራሳቸውን ሉዓላዊነት ለማስጠበቅ መናቆር ጀመሩና እስከ ዛሬ ድረስ ሊወጡ ወዳልቻሉበት የውጊያና የስጋት ዘመን ተዘፈቁ። “ሳይንሳዊ እድገት” የተደረገ ቢሆንም ከዚያን ጊዜ ወዲህ የሚታየው አለመረጋጋት ብዙ ሰዎች የወደፊቱ ሕይወታቸው ምንም አስተማማኝ ነገር እንደማይታይበት አስገንዝቧቸዋል። በእውነትም ‘ጨለማ ምድርን ሸፍኗል።’ ለምን ከዚህ ሊወጡ አልቻሉም? ምክንያቱም ብሔራት ይሖዋን ሉዓላዊ ገዥ አድርገው ለመቀበል አሻፈረን ስላሉ ነው። ግፋ ቢል አንዳንድ መሪዎች በስም ለማይጠሩት “አምላክ” አፋዊ ክብር ይሰጡ ይሆናል። ነገሮችን ራሳቸው ለማካሄድ ቆርጠዋል። የተደቀኑባቸው ችግሮች ግን ከሰው አቅም በላይ ናቸው። (ኤርምያስ 8:9፤ መዝሙር 146:3–6) ያሁኑ ዓለም ከስግብግብነቱና ከንቅዘቱ ጋር ወደ ‘መጨረሻ ቀኖቹ’ ገብቷል። ዓለም ከፊቱ የተጋረጠውን ጥፋት ማስቀረት የሚችልበት ምንም መንገድ የለም። የወደፊቱን ጊዜ በልበ ሙሉነት ሊጠብቁ የሚችሉት በአምላክ መንግሥት ላይ ሙሉ እምነት ያላቸው ሰዎች ብቻ ናቸው። በቁጥር እያደጉ የሄዱ ልበ ቅን የሆኑ ሰዎች ይህንን እየተገነዘቡ ነው። እነርሱም ስለ መንግሥቲቱ ማውራት ብቻ ሳይሆን አኗኗራቸውን ከስብከታቸው ጋር ለማጣጣም አጥብቀው ከሚጥሩት የይሖዋ ምስክሮች ጋር ተባብረው በመሥራት ላይ ናቸው።

‘ታናሹ ሺህ ሆነ’

4. በኢሳይያስ 60:4 አፈጻጸም ላይ የመጀመሪያ ትኩረት የተሰጠው የትኛውን ቡድን ለመሰብሰቡ ሥራ ነው?

4 አንደኛው የዓለም ጦርነት ሲያበቃ የመንግሥቱ ወራሾች ገና ተሰብስበው አላለቁም ነበር። ከክርስቶስ ጋር በሰማይ የሚገዙት፣ ጠቅላላ ቁጥራቸውም 144,000 እንደሚሆን አስቀድሞ የተገለጹት የሰማያዊቷ ኢየሩሳሌም “ወንዶች ልጆች” እና “ሴቶች ልጆች” ተጨማሪ አባላት ገና መምጣት ነበረባቸው። ይሁን እንጂ ይሖዋ የዚህን ሥራ መጠናቀቅ አስመልክቶ “ዓይኖችሽን አንሥተሽ በዙሪያሽ ሁሉ ተመልከቺ፤ ሁሉ ተሰብስበው እነዚህ ወደ አንቺ ይመጣሉ፤ ወንዶች ልጆችሽ ከሩቅ ይመጣሉ፣ ሴቶች ልጆችሽንም በጫንቃ ላይ ይሸከሙአቸዋል” በማለት ተናግሯል። (ኢሳይያስ 60:4) በ1919ና ከዚያ በኋላ መንግሥቱን ለማስታወቅ በተደረገው እንቅስቃሴ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ተጨማሪ ሰዎች ራሳቸውን ለይሖዋ ወሰኑ፤ ተጠመቁ፤ በኋላም በመንፈስ ቅዱስ ተቀቡ። ሆኖም ጠቅላላው የመንግሥቱ ወራሾች “ታናሽ መንጋ” ብቻ እንደሚሆኑ ኢየሱስ ተናግሯል። (ሉቃስ 12:32) ስለዚህ የኢሳይያስ 60:22 ትንቢት እንዲፈጸም ወደ እውነተኛው አምልኮ ሌሎች ሰዎችም መሰብሰብ እንደሚኖርባቸው የተረጋገጠ ነው። ደግሞም በእርግጥ ተሰብስበዋል!

5. ሌላ ጭማሪ ከየት እንደሚመጣ ነው ኢሳይያስ 55:5 የሚገልጸው?

5 እነርሱም በኢሳይያስ 55:5 ላይ እንደሚከተለው ተጠቅሰዋል:- “እነሆ፣ የማታውቀውን ሕዝብ ትጠራለህ፣ የእስራኤልም ቅዱስ አክብሮሃልና ስለ አምላክህ ስለ እግዚአብሔር የማያውቁህ ሕዝብ ወደ አንተ ይሮጣሉ።” እነዚህ ከመንፈሳዊ እስራኤል ውጭ ያሉ ሰዎች ናቸው። ከብዙ ብሔራት የተውጣጡ ቢሆኑም ኅብረት አላቸው፤ ሁሉም የአምላክን መንግሥት በታማኝነት ይደግፋሉ። ከዚህ በፊት የመንፈሳዊ እስራኤል ቀሪዎች በነበራቸው ቅዱሳን ጽሑፎችን የመረዳት አቅም ‘ያላወቁት’ “ሕዝብ” ነበር። ይህም ሕዝብ ቢሆን ለአምላክ አገልጋዮች ተገቢውን እውቅና አልሰጠም ነበር። ነገር ግን መንፈሳዊ እስራኤላውያኑ እውነተኛውን አምላክ የሚያመልኩ መሆናቸውን የመንግሥቱ ስብከት ሲያስገነዝባቸውና በአምላክ በረከት ብቻ ሊገኝ የሚችል መንፈሳዊ ውበት በእነርሱ ላይ ሲመለከቱ ወደ እነርሱ ሊሳቡ ችለዋል።

6. የመንግሥቱ መልእክት ምን ያህል ተዳርሷል? ምን አስደሳች ውጤቶችስ ተገኝተዋል?

6 ሰይጣን የመንግሥቱ መልእክት እንዳይሰበክ ለመከላከልና የሰዎችን ትኩረት ወደ ሌሎች ነገሮች ለመቀልበስ የተቻለውን ሁሉ ቢጥርም የእውነት ብርሃን ወደ ሩቅ የምድር ክፍሎች ዘልቋል። ውጤቱም አምላክ ከብዙ ጊዜ በፊት የራሱን “ሴት” አስመልክቶ እንደሚከተለው ሲል በትንቢት እንደተናገረው ነው:- “በዚያን ጊዜ የባሕሩ በረከት ወደ አንቺ ስለሚመለስ፣ የአሕዛብም ብልጥግና ወደ አንቺ ስለሚመጣ፣ አይተሽ ደስ ይልሻል፣ ልብሽም ይደነቃል ይሰፋማል። . . . የእግዚአብሔርንም ምስጋና ያወራሉ።” (ኢሳይያስ 60:5, 6) አዎን፣ በአንድ ወቅት ከአምላክ የራቀው የሰው ዘር “ባሕር” ክፍል የነበሩና ሕይወታቸውም ብሔራትን በሚሸፍነው “ድቅድቅ ጨለማ” ምክንያት ጨልሞ የነበረው “እጅግ ብዙ ሰዎች” ከመንፈሳዊ እስራኤላውያን ጋር ተቀላቅለዋል። ከብሔራት የመጡት በአምላክ ዓይን በእርግጥም ውድ የሆነ ሀብት ናቸው።

7. ስለ ጭማሪው አስቀድሞ በሰጠው መግለጫ ላይ ይሖዋ በፊቱ ውድ የሚሆነውን ነገር ያመለከተው እንዴት ነው?

7 በኢየሩሳሌም ከተማ የይሖዋ ቤተ መቅደስ እንደገና በሚሠራበት ጊዜ ይሖዋ ነቢዩ ሐጌን “አሕዛብን ሁሉ አናውጣለሁ፣ በአሕዛብ ሁሉ የተመረጠውም ዕቃ ይመጣል፤ ይህንንም ቤት በክብር እሞላዋለሁ፣ ይላል የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር” ብሎ እንዲያስታውቅ አነሳስቶት ነበር። (ሐጌ 2:7) ይህ የብሔራት መናጋትና መናወጥ በመጨረሻው ወደ ጥፋታቸው ያደርሳቸዋል። ይህ ከመሆኑ በፊት ግን ‘ከአሕዛብ ሁሉ የተመረጠው ዕቃ’ ከውስጣቸው ተሰብስቦ ወደ ታላቁ የይሖዋ መንፈሳዊ ቤተ መቅደስ ማለትም ወደ አጽናፈ ዓለሙ የአምልኮ ቤቱ መግባት ይኖርበታል። ዓለም ተንኮታኩታ በምትጠፋበት ጊዜ በዚህ ቤት ውስጥ ከለላ ያገኛሉ። ለይሖዋ ውድ ዕቃ የሚሆኑት እንደነዚህ ያሉት ሕያዋን አምላኪዎቹ ናቸው። እርሱ የሚፈልገው ቁሳዊ ብልጽግናቸውን አይደለም። (ሚክያስ 6:6–8) ለይሖዋ ሊሰጡ የሚችሉት ዋጋው እጅግ ውድ የሆነው ነገር በሙሉ ነፍስ እርሱን ማምለካቸው ነው። ኃይለኛ የልብ ፍቅርና ቅንዓት የተሞላበትን አገልግሎት እንደ ስጦታ ይዘው ወደ አምላክ ይቀርባሉ። ሁሉም ‘የይሖዋን ምስጋና’ ያስታውቃሉ። የእነርሱ ወደ መድረኩ ብቅ ማለት በሰማይም ሆነ በምድር ላይ የይሖዋን ታማኝ አገልጋዮች በሙሉ እንዴት የሚያስደስት ነበር!

8. የመንግሥቱ ምድራዊ ወራሾች ለመሆን የሚሰበሰቡ ሰዎችን ብዛት አስመልክቶ መጽሐፍ ቅዱስ ምን ጥቆማዎችን ይሰጣል?

8 ገነት በምትሆነው ምድር ላይ ለመኖር በጉጉት የሚጠባበቁት እነዚህ ይሖዋን የሚያመልኩ ሰዎች ቁጥራቸው ምን ያህል ይደርስ ይሆን? መጽሐፍ ቅዱስ የተወሰነ አኀዝ አይሰጥም። የይሖዋ ፍቅራዊ ዝግጅት ተጠቃሚ ለመሆን ከየብሔሩ ለሚመጡ ሁሉ በሩ ክፍት ነው። ይሁን እንጂ ስለሚመጡት ሰዎች ብዛት ግምት እንዲኖረን በኢሳይያስ 60:8 ላይ ጥሩ ጥቆማ ተሰጥቷል። ጥቅሱ እነርሱን እንደ ርግቦች አድርጎ በመግለጽ “እንደ ደመና የሚበሩ” ማለትም ከታች ያለውን ምድር እንደሚያጨልም ደመና ሆነው እንደሚተሙ ይናገራል። ይህም በአጭር ጊዜ ውስጥ እጅግ ብዙ የሆኑ ሰዎች እንደሚንቀሳቀሱ ያመለክታል። ይሖዋን የሚያመልኩ ሰዎች በዚህ ሁኔታ እየጎረፉ ስለሚመጡ ‘ታናሽ’ የነበረው መንፈሳዊ እስራኤል “ሺህ፣ የሁሉም ታናሽ፣ ብርቱ ብሔር ይሆናል፣ እኔ ይሖዋ በጊዜው አፋጥነዋለሁ” በማለት ይሖዋ ተናግሯል። (ኢሳይያስ 60:22 አዓት) ይህስ አሁን ካለው ተጨባጭ ሁኔታ ጋር ይስማማልን?

9. ከ1935 ወዲህ እንደዚህ ያለው ጭማሪ የታየው እንዴት ነው?

9 ከአንደኛው የዓለም ጦርነት በኋላ ስለ መንግሥቲቱ ለሕዝብ ምስክርነት በመስጠቱ ሥራ ይካፈሉ የነበሩት በጥቂት ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ብቻ ነበሩ። በ1935 በዓለም ዙሪያ ጠቅላላ ቁጥራቸው ከ60,000 በታች ነበር። በ1941 የመንግሥቱ አዋጅ ነጋሪዎች ቁጥር የ100,000⁠ን ወሰን አለፈ። በ1953 ከ500,000 በላይ ነበሩ። ከአሥር ዓመት በኋላ ቁጥራቸው አንድ ሚልዮን ደረሰ። በ1994 ማለቂያ ላይ ከፍተኛ ቁጥራቸው 4,914,094 ደርሶ ነበር። ስለወደፊቱ ጊዜ እርግጠኛ ተስፋ የምትሰጠው የአምላክ መንግሥት ብቻ የሆነችበትን ምክንያት ለሌሎች ለማስታወቅ በቀን በአማካይ ከሁለት ሚልዮን ሰዓት በላይ ይሠራሉ። የይሖዋ ምሥክር በመሆን የይሖዋ መሲሐዊት መንግሥት ዜጎች እንደሆኑ ያረጋገጡት ሰዎች ቁጥር ሲታይ በዛሬው ዓለም ውስጥ 60 ብሔራት እያደገ ከሚሄደው ከዚህ “ብሔር” ያነሰ የሕዝብ ቁጥር እንዳላቸው ሊስተዋል የሚገባው ነው። ሆኖም ይህ ልዩ “ብሔር” በዓለም ፖለቲካ ውስጥ አይገባም። ከዚህ ይልቅ ለእውነተኛው አምላክ አገልግሎት ብቻ ያደረ ነው።

10. (ሀ) ይህንን እድገት ስናስብ አስገራሚ የሚያደርጉት ሁኔታዎች ምንድን ናቸው? (ለ) ሌላም ጭማሪ እንደሚኖር የሚጠቁመው ምንድን ነው?

10 ይህ ትንቢት የሚፈጸመው እስከዚህ ደረጃ ድረስ ብቻ ነውን? እስከ አሁን የተከናወነው ነገር የመጽሐፍ ቅዱስን መግለጫ ለማሟላት በቂ ነው። ይህ ሥራ ምን ምን ዕንቅፋቶችን ተቋቁሞ እንደተካሄደ ስናስበው፣ ይኸውም በየጊዜው ያጋጠሙ መሰናክሎች፣ ሥራውን ለማሳካት መለኮታዊ አመራር እንዳልተለየ የሚያረጋግጠው ማስረጃ፣ በዚህ ሥራ የተካፈሉት ሁሉ በሙሉ ልብ ማገልገላቸው ሲታሰብ በእውነት አስደናቂ ነገር ነው። ሥራው በሰዎች አኗኗር ላይ ያመጣቸው ለውጦችም ቢሆኑ የሚያስደንቁ ናቸው። አሁንም ቢሆን ይሖዋን በመደገፍ ግልጽ የሆነ አቋም የሚወስዱ ሰዎች መምጣታቸውን አላቆሙም፤ ሥራውም አልቀዘቀዘም። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ራሳቸውን ለውኃ ጥምቀት የሚያቀርቡት ሰዎች ቁጥር በየወሩ በአማካይ ከ20,000 በላይ ሲሆን በአንዳንድ ዓመታት ከዚህ ቁጥር በጣም የሚበልጡ ሰዎች ይጠመቃሉ። እነዚህ ሁሉ የውኃ ጥምቀታቸው የሚያስከትለውን ኃላፊነት በማሟላት ከመጪው ጥፋት በሕይወት ተርፈው ወደ “አዲስ ምድር” እንደሚገቡ ልብን የሚያረጋጋ ተስፋ አላቸው።

11. (ሀ) እነዚህ በሚልዮን የሚቆጠሩ ሰዎች የአንድ ድርጅት ክፍል እንደሚሆኑ መጽሐፍ ቅዱስ የሚያመለክተው እንዴት ነው? (ለ) የዚህ ድርጅት ዋና ዓላማ ምንድን ነው?

11 እነዚህ በሚልዮን የሚቆጠሩ ሰዎች በየቦታው ተበታትነው አምላክን ባሻቸው መንገድ የሚያገለግሉ የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች አይደሉም። ለሚታየው የይሖዋ ድርጅት ራሳቸውን በማስገዛት የድርጅቱ ክፍል የሆኑ ሰዎች ናቸው። አስቀድመን እንደተመለከትነው በመጀመሪያ የመንግሥቱ ወራሾች ‘ተሰበሰቡ።’ አሁን ደግሞ የምድራዊ ሕይወት ተስፋ ያላቸው ከሁሉም ብሔራት የተውጣጡ ሌሎች ሰዎች ‘ወደ እነርሱ እየመጡ’ ነው። (ኢሳይያስ 60:4, 5) ‘በአንዱ እረኛ’ በኢየሱስ ክርስቶስ የሚመራ ኅብረት ያለው “አንድ መንጋ” ክፍል ሆነዋል። (ዮሐንስ 10:16) ሐዋርያው ጴጥሮስ እውነተኛ ክርስቲያኖችን ‘ዓለም አቀፍ የወንድማማች ማኅበር’ በማለት ገልጿቸዋል። ጳውሎስም ራሳቸውን እንዳያገሉ፤ በዚህ ፋንታ ‘አንድ ላይ እንዲሰበሰቡ፣’ ይልቁንም መለኮታዊው የፍርድ ቀን ሲቀርብ የበለጠ ይህን እንዲያደርጉት አሳስቧል። (1 ጴጥሮስ 5:9 አዓትዕብራውያን 10:23–25) በዚህ መንገድ ይህ ድርጅት ለቆመለት ታላቅ ዓላማ ብቁ ለመሆን አስፈላጊውን ጥንካሬና ትጥቅ ያገኛል። ይህ ዓላማ ምንድን ነው? የይሖዋ ስም ጐላ ብሎ ለሕዝብ እንዲታይ ማድረግ ነው። — 1 ጴጥሮስ 2:9፤ ኢሳይያስ 12:4, 5

መከናወን ያለበት ሥራ

12. (ሀ) ሁላችንም ልንሳተፍበት የሚገባንን ሥራ ኢየሱስ ያመለከተው እንዴት ነው? (ለ) ይህስ ምን ያህል አስፈላጊ ነው? ለምንስ?

12 ወደ ይሖዋ ድርጅት የሚገቡ ሁሉ በውስጡ ያሉት ሰዎች ሠራተኞች መሆናቸውን ለማስተዋል ብዙ ጊዜ አይፈጅባቸውም። የኢየሱስ ክርስቶስን አርአያ በመከተል ሁሉም የይሖዋን ስም የሚያስከብረው የአምላክ መንግሥት ምሥራች ትጉህ ሰባኪዎች ናቸው። ኢየሱስ ራሱ “ስለዚህ ተልኬአለሁና ለሌሎቹ ከተማዎች ደግሞ የእግዚአብሔርን መንግሥት ወንጌል እሰብክ ዘንድ ይገባኛል” በማለት ተናግሯል። (ሉቃስ 4:43) ሌሎች ሰዎች ሕይወታቸውን በአምላክ አገልግሎት ዙሪያ መገንባት እንዳለባቸው አጥብቆ አሳስቧቸዋል። ራሱ የሠራውን ሥራ ተከታዮቹም እንዲሠሩት አስተምሯቸዋል። እኛ የምንገኝበትን ጊዜ አስመልክቶ “ለአሕዛብም ሁሉ ምስክር እንዲሆን ይህ የመንግሥት ወንጌል በዓለም ሁሉ ይሰበካል” በማለት ተናግሯል። (ማቴዎስ 24:14) ዛሬ ማንኛችንም ብንሆን ከዚህ የተሻለ ሥራ መሥራት አንችልም። ለምን? ምክንያቱም በዚህ ሥራ አማካኝነት የፍጥረት ሁሉ ደኅንነት የተመካበትን የይሖዋ አምላክን ሕጋዊ ሉዓላዊነት እንደምንደግፍ ስለምናሳይ ነው። በዚህ ሥራ በሙሉ ልብ በመካፈል፣ ይገባናል ለማንለው የይሖዋ ብዙ ደግነት ያለንን አድናቆት እናሳያለን። በተጨማሪም እኛን መሰል የሆኑ የሰው ልጆች ከመጪው ታላቅ መከራ በሕይወት ለመትረፍ የሚያስችላቸውን ብቸኛ መንገድ እንዲከተሉ እንረዳቸዋለን። — ከ1 ጢሞቴዎስ 4:15, 16 ጋር አወዳድር።

13. (ሀ) በኢሳይያስ 60:17 ላይ የይሖዋ ድርጅት ምን ሁኔታዎች እንደሚኖሯት ተገልጿል? (ለ) ይህንን በተሟላ መልኩ ለማግኘትስ ምን ማድረግ ይኖርብናል? (ሐ) ይህን የሚያደርጉ ሁሉ ከፊታቸው ምን ይጠብቃቸዋል?

13 በይሖዋ ድርጅት ውስጥ የሚያገኟቸው ሁኔታዎች ልባቸውን በደስታ ያሞቁታል። ይሖዋ በኢሳይያስ በኩል “አለቆችሽንም ሰላም፣ የበላይ ገዢዎችሽንም ጽድቅ አደርጋለሁ” በማለት አስቀድሞ ተናግሮ ነበር። (ኢሳይያስ 60:17) ይመጣል የተባለለት ሰላም እንዲሁ ሐሳብ ብቻ ሳይሆን እውን የሆነ ነገር ነው። የአምላክ ቅዱስ መንፈስ የሚያፈራው ሰላም ነው። ይህ ማለት ግን አንድ ሰው ወደ ድርጅቱ ስለመጣ ብቻ ይህን ሰላም በተሟላ መልኩ ያገኛል ማለት አይደለም። ራሱ “ሰላም የሚቆምበትን እርስ በርሳችንም የምንታነጽበትን” ነገር መከተልን መማር ይኖርበታል። (ሮሜ 14:19) የሌሎችን አለፍጽምና ለመቻል፣ ትዕግሥትንና ራስን መግዛት ለማሳየት፣ አምላክ ይቅር እንዲለው እንደሚፈልግ ሁሉ እርሱም ሌሎችንም ይቅር ለማለት የሚያስችል አምላካዊ ጥበብ ማፍራት ይኖርበታል። አዎን፣ ‘ሰላምንም ማድረግ’ ይገባዋል። (ያዕቆብ 3:17, 18፤ ገላትያ 5:22, 23፤ ቆላስይስ 3:12–14) ይህን የሚያደርጉ ሁሉ በአሁኑ ጊዜ እየተሰበሰበ ያለው “ብርቱ ብሔር” ክፍል መሆኑ ትልቅ ደስታ አምጥቶላቸዋል። ይህ ሕዝብ “ለደስተኛው አምላክ” ለይሖዋ አገልግሎት ያደረ ሕዝብ ነው። (2 ጢሞቴዎስ 1:11 አዓት) ሰይጣንን ሉዓላዊ ገዥው አድርጎ በተቀበለውና በተገዛለት ጠቅላላ ዓለም ላይ ይሖዋ ፍርዱን ሲያስፈጽም ከጥፋቱ የሚተርፈው የዚህ “ብሔር” አባላት ሕይወት ይሆናል።

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]