በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

አንተ በግልህ ምን ታደርጋለህ?

አንተ በግልህ ምን ታደርጋለህ?

ምዕራፍ 16

አንተ በግልህ ምን ታደርጋለህ?

1. በግለሰብ ደረጃ ምን ውሳኔ ማድረግ ያስፈልጋል?

ይሖዋን አገልግል ብሎ ማንም ሰው ሊወስንልህ አይችልም። የትዳር ጓደኛህ የታመነች የአምላክ አገልጋይ ከሆነች ይህ ትልቅ በረከት ሊሆንልህ ይችላል። በተመሳሳይም ወላጆችህ ይሖዋን የሚወዱ ከሆኑ ሞገስ በሚያሰጥ ሁኔታ ውስጥ ትገኛለህ ማለት ነው። በቤተሰብ ውስጥ እንደዚህ የመሰሉ ሁኔታዎች መኖራቸው ይሖዋን “በመንፈስና በእውነት” ከሚያመልኩት ጋር ለመቀላቀል የበለጠ ግፊት ያሳድራሉ። (ዮሐንስ 4:23, 24) ይሁን እንጂ ውሎ አድሮ አንተ ራስህ የግል ውሳኔ ማድረግ ይኖርብሃል። በእርግጥ ይሖዋን ትወዳለህን? ከአገልጋዮቹስ አንዱ ለመሆን ትፈልጋለህን? ጽድቅ በሚሰፍንበት ዓለም ውስጥ ለመኖር በእርግጥ ትፈልጋለህን?

2. (ሀ) አንድ ወላጅ ይሖዋን ስለማገልገል ያለው አቋም ትልቅ ለውጥ ሊያመጣ የሚችለው ለምንድን ነው? (ለ) ወላጆች ለልጆቻቸው ጥሩ ጅምር ለመስጠት ሊያደርጓቸው የሚችሉ አምስት ነገሮች ምንድን ናቸው?

2 ወላጅ ከሆንክ ልጆችህ በአምላክ መንግሥት ሥር የዘላለም ሕይወት አግኝተው ለማየት እንደምትፈልግ የተረጋገጠ ነው። የራሳቸውን የሕይወት ጐዳና ለመቀየስ በሚያበቃቸው ዕድሜ ላይ ከደረሱ በኋላ የሚያደርጉትን ልትቆጣጠር አትችልም። ይሁን እንጂ አንተ ራስህ በእውነተኛው አምልኮ ረገድ የምታደርገው ነገር፣ በጎ ወይም መጥፎ የሆነ ኃይለኛ ተጽዕኖ ሊያሳድርባቸው ይችላል። ይሖዋን ከማገልገል ወደኋላ የምትል ከሆነ ይህ ማመንታትህ የዘላለም ሕይወትን ጉዞ ለመጀመር የሚያስችላቸው የተሻለ ዕድል እንዲያመልጣቸው ሊያደርግ ይችላል። ወይም ራስህን ለአምላክ ከወሰንክ በኋላ ውሳኔህን ለመተግበር ቸልተኛ ብትሆን መላው ቤተሰብ ወደ ከባድ መንፈሳዊ አዘቅት ሊያሽቆለቁልና በታላቁ መከራ ጊዜ ሁሉንም ነገር ወደማጣት ሊደርስ ይችላል። ነገር ግን የሚጠበቅብህን በመፈጸም በኩል ጥሩ የታማኝነት ምሳሌ ብታሳያቸው፣ ልጆችህ የአምላክን ቃል እንዲያጠኑ ራስህ ብትረዳቸው፣ በራስህና በልጆችህ ልብ ውስጥ ለይሖዋ ፍቅርን፣ ለሚታየው ድርጅቱም አክብሮትን ብትኮተኩት፣ የአምላክን ፈቃድ ማድረግ ከምን እንደሚጠብቃቸው ብታስገነዝባቸውና በቅዱስ አገልግሎት እንዴት ደስታ ማግኘት እንደሚቻል ብታሳያቸው ወደ ሕይወት በሚመራው ጐዳና ለመጓዝ ጥሩ ጅምር ሰጠሃቸው ማለት ነው። ይህን ሕይወት መጨበጥ የሚቻለው ይሖዋ ጥረታችሁን ከባረከላችሁ ብቻ ነው። (ከ2 ጢሞቴዎስ 1:5 ጋር አወዳድር።) ለዚህ ውጤት ዘወትር ጸልይ። ብዙ ጥረት ማድረግም ይፈለግብሃል። ይሁን እንጂ ውጤቱ ሲታይ ምንም ያህል ብትደክም የሚቆጭ አይሆንም!

3. (ሀ) ከቤተሰብህ ተቃውሞ ቢያጋጥምህ ምን ማድረግ ትችላለህ? (ለ) ያም ሆኖ ተቃውሞው ቢቀጥልስ?

3 ምናልባት ግን ቤተሰቦችህ ለይሖዋ ያለህን ፍቅር የማይጋሩህ በመሆናቸው ችግር አጋጥሞህ ይሆናል። “በጣም አጥብቀህ አትያዘው” እያሉ ሊያዳክሙህ ይሞክራሉን? ወይም ደግሞ ቀጥተኛ ተቃውሞ አስነስተውብሃልን? የአምላክን ዓላማ መረዳቱ የሚያስገኘውን ደስታ እንዲካፈሉ እንዴት ልትረዳቸው ትችላለህ? ብዙውን ጊዜ ቤተሰቦችህ ወደ መንግሥት አዳራሹ እንዲመጡና በዚያ የሚደረገውን ራሳቸው እንዲያዩ መጋበዝ መሰናክሎቹን ለማስወገድ ሊረዳ ይችል ይሆናል። እዚያ ከተገኙ በኋላ ስለ ይሖዋ ምሥክሮች እምነትና ተግባር ላሏቸው ጥያቄዎች ግልጽ መልስ ለማግኘት ከአንዱ ሽማግሌ ጋር ሊነጋገሩ ይችላሉ። ያም ተደርጎ ተቃውሞው ቢቀጥልስ? እንደሚከተለው በማለት ራስህን መጠየቅ ያስፈልግሃል:- ‘ለይሖዋና ለልጁ ለኢየሱስ ክርስቶስ ያለኝ ፍቅር፤ እንዲሁም እነርሱ ላደረጉልኝ ነገር ያለኝ የምስጋና ስሜት ችግሮችን ለመቋቋም ፈቃደኛ ለመሆን የሚያበቃ ያህል ጥልቀት አለውን? ከተቻለ ቤተሰቦቼም ጭምር የአምላክ የዘላለም ሕይወት ዝግጅት ተጠቃሚ ይሆኑ ዘንድ ትክክለኛ ምሳሌ እንዳሳያቸው የሚገፋፋ በቂ ፍቅር አለኝን?’ — ማቴዎስ 10:36–38፤ 1 ቆሮንቶስ 7:12, 13, 16

አሕዛብ በዙሪያው የሚሰባሰቡበት ምልክት

4. በእውነት ይሖዋን እንደምንወድ እንዴት ማሳየት እንችላለን?

4 በየትም ቦታ ያሉ ሰዎች አሁን በመሲሐዊቷ መንግሥት ጎን በመሰለፍ ለይሖዋ ያላቸውን ፍቅር ለማሳየት የሚያስችል አጋጣሚ አላቸው። የይሖዋ ስም የደረሰበትን ስድብ ሁሉ የምታስወግደው መንግሥት እርሷ ናት። ለመንግሥቲቱ ያለን ዝንባሌ ስለራሱ ስለ ይሖዋ ምን እንደሚሰማን ቁልጭ አድርጎ ያሳያል።

5. (ሀ) በኢሳይያስ 11:10 ላይ በዘመናችን ምን ነገር እንደሚሆን አስቀድሞ ተገልጾ ነበር? (ለ) ይህስ ምን ማለት ነው?

5 ይሖዋ ነቢዩ ኢሳይያስን “በዚያን ቀን እንዲህ ይሆናል፤ ለአሕዛብ ምልክት ሊሆን የቆመውን የእሴይን ሥር አሕዛብ [ያለበትን እየጠየቁ] ይፈልጉታል፤ ማረፊያውም የተከበረ ይሆናል” ብሎ እንዲጽፍ በመንፈስ አነሳስቶታል። (ኢሳይያስ 11:10) ይህ “የእሴይ ሥር” የላቀ ክብር የተቀዳጀው ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ንጉሣዊ ሥልጣን ጨብጦ መግዛት በጀመረ ጊዜ ሕይወት ሰጪ “ሥር” ሆነና ከእሴይ በልጁ በንጉሥ ዳዊት በኩል ለነበረው የመሲሐዊ ነገሥታት መሥመር አዲስ ሕይወት ሰጠ። (ራእይ 5:5፤ 22:16) ከ1914 ጀምሮ ‘ለአሕዛብ ምልክት ሆኖ ቆሞአል’፤ ማለትም ሕዝቦች እየመጡ የሚሰባሰቡበት ዓርማ ሆኗል። ይሖዋ ራሱ እንደ ምልክት፣ ይኸውም እውነተኛ መሲሐዊ ንጉሥ አድርጎ አስነስቶታል። — ኢሳይያስ 11:12

6. (ሀ) ሰዎች በሰማያዊው ንጉሥ ዙሪያ እንዲሰባሰቡ ያስቻላቸው ምንድን ነው? (ለ) ሰዎች ‘እየጠየቁ’ ወደ ‘ምልክቱ’ በመምጣታቸው ምን ለማወቅ ችለዋል?

6 ይሁን እንጂ እዚህ ምድር ላይ ያሉ ሰዎች በሰማይ በሚኖር ንጉሥ ዙሪያ እንዴት ሊሰባሰቡ ይችላሉ? በማስተዋል ዓይናቸው እርሱን ማየት እንዲችሉ ከመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ማግኘት ያስፈልጋቸዋል። የመንፈሳዊ እስራኤል ቀሪዎች በመንፈስ ቅዱስ እየተመሩ ይህን ሥራ በብርቱ ትጋት ሲያካሄዱ ኖረዋል፤ የተቋቋመችውን የአምላክ መሲሐዊት መንግሥት ምሥራች በመላዋ ምድር አውጀዋል። ከሁሉም ብሔራት የተውጣጡ ግለሰቦች መልእክቱን ሰምተው በአድናቆት ተቀብለውታል። የመንግሥቱ ተገዥዎች በመሆን በገነቲቱ ምድር ላይ የዘላለም ሕይወት ለማግኘት የሚያስችሉት መለኮታዊ ብቃቶች እንዲብራሩላቸው ጠይቀዋል። ከመጽሐፍ ቅዱስ በተሰጧቸው መልሶች ስለረኩም ከእነዚህ ብቃቶች ጋር የሚስማማ ነገር በመሥራት በይሖዋ መሲሐዊት መንግሥት ጎን ተሰልፈዋል። አንተስ ይህን አድርገሃልን?

‘ይሰማሉ፣ ነገር ግን አያደርጉትም’

7. ሰዎች ለመጽሐፍ ቅዱስ መልእክት ምን ስሜት ሊያሳዩ እንደሚችሉ ነው በሕዝቅኤል 33:30–33 ላይ አስቀድሞ የተነገረው?

7 የይሖዋ ምሥክሮች በቅንዓት ስለሚሠሩ ብዙ ጊዜ የሰዎች መወያያ ርዕስ ሆነዋል። ይሁን እንጂ እነዚህ ሰዎች የይሖዋ ምሥክሮች ስለሚያውጁት መልእክት ምን ይላሉ? የብዙዎቹ ስሜት ከነቢዩ ሕዝቅኤል ጋር በባቢሎን ውስጥ የነበሩት ስደተኞች ካሳዩት ስሜት ጋር ይመሳሰላል። ስለ እነርሱ ይሖዋ እንዲህ ብሏል:- “አንተም፣ የሰው ልጅ ሆይ፣ የሕዝብህ ልጆች . . . እርስ በርሳቸውም . . . እንሂድና እግዚአብሔር ያለው ቃል ምን እንደ ሆነ እንስማ ብለው ይናገራሉ። ሕዝብ እንደሚመጣ ወደ አንተ ይመጣሉ፣ እንደ ሕዝቤም በፊትህ ይቀመጣሉ፣ ቃልህንም ይሰማሉ ነገር ግን አያደርጉትም፤ በአፋቸው ብዙ ፍቅር ይገልጣሉ፣ ልባቸው ግን ስስታቸውን ትከተላለች። እነሆ፣ አንተ መልካም ድምፅ እንዳለው እንደሚወደድ መዝሙር ማለፊያም አድርጎ በገና እንደሚጫወት ሰው ሆነህላቸዋል፤ ቃልህንም ይሰማሉ ነገር ግን አያደርጉትም። እነሆ፣ ይህ ይመጣል፤ በመጣም ጊዜ እነርሱ ነቢይ በመካከላቸው እንደ ነበረ ያውቃሉ።” — ሕዝቅኤል 33:30–33

8. አንዳንድ ሰዎች ይህ ዝንባሌ እንዳላቸው እንዴት ያሳያሉ?

8 የይሖዋ ምሥክሮችን የሚያደንቁና መጽሐፍ ቅዱሳዊ ጽሑፎቻቸውን የሚወዱ ብዙ ሰዎች አሉ። እቤታችሁ መጽሐፍ ቅዱስን በነፃ እናስተምራችሁ የሚል ግብዣ ሲቀርብላቸውም ይቀበሉ ይሆናል። አንዳንዶቹም ምሥክሮቹ ወደሚያደርጓቸው ልዩ ስብሰባዎች ከጓደኞቻቸው ጋር ይመጣሉ። ለምሳሌ ያህል በዓመታዊው የኢየሱስ ክርስቶስ ሞት መታሰቢያ በዓል ላይ የተሰብሳቢዎቹ ቁጥር ብዙ ጊዜ የይሖዋ ምሥክሮቹን ቁጥር ማጠፉ ያልተለመደ ነገር አይደለም። በአንዳንድ አገሮችም የተሰብሳቢው ብዛት ከምሥክሮቹ ቁጥር በአምስት ጊዜ ይበልጣል። ይሁን እንጂ የመጽሐፍ ቅዱስ እውነቶችን ሰምተው ምን አድርገዋል? አምስት ሚልዮን የሚያክሉ ሰዎች እነዚህን እውነቶች ከልብ በመቀበል ሕይወታቸውን በዚያው መሠረት አስተካክለዋል። ሌሎቹ ግን የሚሰጠውን ትምህርት እነርሱን ለማዝናናት እንደቀረበ አስደሳች መዚቃ ብቻ አድርገው ተመልክተውታል። ከዳር ቆመው እየተመለከቱ ምናልባት አይዟችሁ ይሉ ይሆናል፤ ነገር ግን ሕይወታቸውን ለአምላክ አይወስኑም፤ በቅዱስ አገልግሎቱም አይሳተፉም።

9. ጥበበኛ የሆነ ሰው ከመጠራጠርና ትንሽ ልቆይ ከማለት ይልቅ ምን ያደርጋል?

9 በመጠራጠርና በመቆየት ምን ጥቅም ይገኛል? እንደዚያ ማድረጉ በቅርቡ ከሚመጣው የበቀል ቀን የይሖዋን ሞገስና ጥበቃ እንደማያስገኝ የታወቀ ነው። በሕይወት ከሚተርፉት መካከል ለመሆን ከፈለግህ ‘ወደ ይሖዋ መጠጋትና’ የእርሱ ንብረት መሆንህን በተጨባጭ ማሳየት ይኖርብሃል። — ዘካርያስ 2:11፤ ማቴዎስ 7:21

ትክክለኛ ውሳኔ አድርገዋል

10, 11. (ሀ) ኦባብ ማን ነበር? ምን ግብዣስ ቀርቦለት ነበር? (ለ) ያደረገውን ውሳኔ እንዴት እናውቃለን?

10 የኢየሱስ ክርስቶስ ተከታይ በመሆን ይሖዋን ለማምለክ የመረጡ ሁሉ ይህን የወሰኑት ራሳቸው ናቸው። የሰማያዊቷ መንግሥት ወራሾች ሁኔታም ከዚህ የተለየ አይደለም። አሁን ደግሞ ሌሎች ሰዎችም ከታላቁ መከራ በሕይወት ለመትረፍና ፍጹም የተስተካከሉ ሁኔታዎች ባሏት ምድር ላይ ለመኖር የራሳቸውን ምርጫ እንዲያደርጉ ታላቅ ዕድል ተከፍቶላቸዋል። ኦባብ እነዚህ ሰዎች ሊኮርጁት የሚገባ ጥሩ አርአያ ትቶላቸዋል።

11 ኦባብ የሙሴ አማች ነበር። ነገር ግን በምድያም አገር የሚኖሩት የቄናውያን ነገዶች አባል ነበር እንጂ እስራኤላዊ አልነበረም። የእስራኤል ሕዝብ በሙሴ በኩል ሕጉን ከተቀበለና ለይሖዋ አምልኮ ቅዱሱን የመገናኛ ድንኳን ከሠራ በኋላ በሰሜን በኩል ወደ ተስፋይቱ ምድር የሚንቀሳቀሱበት ጊዜ ደረሰ። የይሖዋን መገኘት የሚያመለክተው የደመና ዓምድ በፊታቸው እየሄደ የሚጓዙበትን አቅጣጫና የሚሰፍሩበትን ቦታ ያመለክታቸው ነበር። ይሁን እንጂ አገሩን የሚያውቅና የሆነ ቦታ ላይ በሚሰፍሩበት ጊዜ የሚያስፈልጓቸውን አንዳንድ ነገሮች ለማግኘት የሚመራቸው ሰው ቢያገኙ ይረዳቸዋል። ሙሴ ኦባብን አብሯቸው እንዲሄድ ጋበዘው። ኦባብ ግን በትውልድ አገሩ ከዘመዶቹ ጋር መቆየት እንደሚሻለው በማሰብ በመጀመሪያ ግብዣውን ለመቀበል አቅማማ። ቢሆንም ሙሴ ነገሩን እንደገና እንዲያስብበትና ለእስራኤል ‘እንደ ዓይን’ ሆኖ አብሮ በመሄድ ይሖዋ ለሕዝቡ ከሚሰጠው በረከት ተካፋይ እንዲሆን አጥብቆ ጠየቀው። መሳፍንት 1:16 እንደሚያመለክተው ኦባብ እሺ በማለት የጥበብ እርምጃ ወስዷል። — ዘኁልቁ 10:29–32

12. (ሀ) በዛሬው ጊዜ ኦባብን የሚመስሉት እነማን ናቸው? በምንስ መንገዶች? (ለ) በዛሬው ጊዜ ሙሴ ለኦባብ ካቀረበው ግብዣ ጋር የሚመሳሰለው ምንድን ነው?

12 በአሁኑ ጊዜ የኦባብ አምሳያ የሆኑ ሰዎች አሉ። መንፈሳዊ እስራኤላውያን ባይሆኑም ዕጣቸውን ከእነርሱ ጋር ጥለው አምላክ ወዳዘጋጀው አዲስ ሥርዓት አብረዋቸው ይጓዛሉ። ለዚህ ሲባል ከዓለማዊ ዘመዶቻቸውና ከሰብዓዊ መንግሥታት ጋር የነበራቸውን ትስስር ማቋረጥ አስፈልጓቸዋል። በታላቁ ሙሴ በኢየሱስ ክርስቶስ እየተመሩ ከቀሪ ‘ወንድሞቹ’ ጋር በደስታ ያገልግላሉ። ብዙ ጊዜ የመንግሥቱ ምሥራች የሚሰበክባቸውን አዳዲስ ቦታዎች አቅንተዋል። ብዙዎቹ አቅኚ ወይም ሚስዮናውያን ሆነው በተለይ የመንግሥቱ አዋጅ ነጋሪዎች ይበልጥ ወደሚያስፈለጉባቸው አዳዲስ አካባቢዎች በመሄድ ሙሉ ጊዜያቸውን የአምላክ መንግሥት የሰው ዘር ብቸኛ ተስፋ መሆኗን ለሕዝብ ለማስታወቅ ተጠቅመውበታል። በዚህ ዓይነቱ ቅዱስ አገልግሎት ለመካፈል አሁንም ገና ብዙ አጋጣሚዎች አሉ። ብቃት ያላቸው ሁሉ ለዚህ ራሳቸውን እንዲያቀርቡና አገልግሎትን በዚህ መንገድ በማስፋት ከሚገኘው በረከት ተካፋይ እንዲሆኑ ተጋብዘዋል። ታዲያ አንተስ ግብዣውን ልትቀበለው ትችላለህን?

13. (ሀ) ኢያዔል ማን ነበረች? ባሏ ለይሖዋ አገልጋዮች ምን አቋም ነበረው? (ለ) ኢያዔል የተፈተነችው እንዴት ነው?

13 ኦባብ ከእስራኤል ጋር ለመሄድ ከወሰነ 180 ዓመታት ያህል ካለፉ በኋላ የእርሱ ዝርያ የሆነ ሔቤር የተባለ ሰው ከሚስቱ ከኢያዔል ጋር በመጊዶ አቅራቢያ ይኖር ነበር። ሔቤር ከቀሩት ቄናውያን ተለይቶ በመኖር የእስራኤል ክፉ ጨቋኝ ከነበረው ኢያቢስ ከተባለ የከነዓናውያን ንጉሥ ጋር ሰላማዊ ግንኙነት መሥርቶ ነበር። ባርቅ እስራኤልን ከጭቆናው ነፃ እንዲያወጣቸው ይሖዋ ባስነሳው ጊዜ የኢያቢስ የሠራዊት አለቃ ሲሣራ የጦር ኃይሉንና በመንኮራኩራቸው ላይ ረጃጅም ማጭድ የነበራቸውን ዘጠኝ መቶ ሠረገሎች ሰበሰበ። ሆኖም ይሖዋ በጠላት ሠፈር ሽብር በማስነሳትና ሠረገሎቹ እንዳይንቀሳቀሱ ጐርፍ በመልቀቅ ለሕዝቡ ተዋጋላቸው። ሲሣራ ራሱ ሠረገላውን ጥሎ በእግር ወደ ሔቤር ሚስት ወደ ኤያኤል ድንኳን ሸሸ። እርሷም ሲሣራ ተስፋ እንዳደረገው ወደ ድንኳን አስገባችው። — መሳፍንት 4:4–17፤ 5:20, 21

14. ኢያዔል ምን ወሰነች? ይህስ የምን ማረጋገጫ ነበር?

14 አሁን ፈተና መጣባት። በዚህ የይሖዋ ሕዝብ ጠላት ላይ ምን ታደርግ ይሆን? ሲሣራን ብርድ ልብስ አለበሰችው፣ ጥማቱንም በእርጐ አረካችለትና እንቅልፍ እስኪወስደው ጠበቀች። ሲተኛም “የድንኳን ካስማ ወሰደች፣ በእጅዋም መዶሻ ያዘች፣ ቀስ ብላም ወደ እርሱ ቀረበች፤ በጆሮግንዱ ካስማውን ቸነከረች፤ እርሱም ደክሞ አንቅላፍቶ ነበርና ካስማው ወደ መሬት ጠለቀ፣ እርሱም ሞተ።” የወሰደችው እርምጃ ድፍረትንና ለይሖዋና ለሕዝቡም ፍቅርን የሚጠይቅ ነበር። በተጨማሪም ሳያወላውሉ እርምጃ መውሰድንና ጉልበት የሚጠይቅ ሥራ መሥራትን የሚጨምር ነበር።— መሳፍንት 4:18–22፤ 5:24–27, 31

15. በዛሬው ጊዜ ሰዎች እንደ ኢያዔል መሆናቸውን እያስመሰከሩ ያሉት እንዴት ነው?

15 ይሖዋን ያመልኩ እንደነበሩት እስራኤላውያን ያልሆኑ ሌሎች ሰዎች ሁሉ ኢያዔልም ለክርስቶስ መንፈሳዊ ወንድሞች መልካም የሚያደርጉት የ“ሌሎች በጎች” አምሳያ ነች። የቅርብ ዘመዶቻቸው ከዓለምና ከገዥው ክፍል ጋር የቱንም ያህል ቅርብ ግንኙነት ቢኖራቸው ዓለማዊ መሪዎች በይሖዋ ሕዝብ ላይ በሚፈጽሙት ጭቆና “ሌሎች በጎች” አይስማሙም። ታማኝነታቸው ለታላቁ ባርቅ ለጌታ ኢየሱስ ክርስቶስና ለእውነተኛ ተከታዮቹ ነው። እነዚህ የኢያዔል ክፍል የሆኑ ሰዎች ራሳቸው በዓለማዊ መሪዎች ላይ እጃቸውን አያነሱም፤ ሆኖም የይሖዋን አገልጋዮች ለመጨቆን የሚሸረበውን ማንኛውንም ተንኮል ለማክሸፍ የሚችሉትን ሁሉ ያደርጋሉ። ይሖዋ ጠላቶቹን ሁሉ ለመደምሰስ ባለው ዓላማ ሙሉ በሙሉ እንደሚስማሙ ከማሳወቅ ወደኋላ አይሉም።

16, 17. (ሀ) በሥራ ምዕራፍ 8 ላይ ምን ልንከተለው የሚገባን ምሳሌ ተመዝግቦልናል? (ለ) ከዚያስ በኋላ ምን ማድረጋችንን መቀጠል ይገባናል?

16 ሊባክን የሚችል ጊዜ የለም። በይሖዋና በመሲሐዊቷ መንግሥቱ ላይ በእርግጥ እምነት ካለህና አኗኗርህን መጽሐፍ ቅዱስ ካሰፈራቸው ብቃቶች ጋር አስማምተህ ከሆነ ሳትዘገይ ይህን አቋምህን በግልጽ አሳይ። በሐዋርያት ሥራ ምዕራፍ 8 ላይ የተጠቀሰው ኢትዮጵያዊ ጃንደረባ ያሳየውን ዓይነት መንፈስ አንጸባርቅ። ምን ማድረግ እንደሚፈለግበት ሲገባው ወዲያው ስለ ኢየሱስ የሚገልጸውን ምሥራች ላብራራለት ለፊልጶስ “እንዳልጠመቅ የሚከለክለኝ ምንድር ነው?” ብሎ ጠየቀው። ወዲያውም በውኃ ተጠመቀ።

17 በዚህ መንገድ ጥሩ ጅምር ካደረግህ በኋላ ከይሖዋ ጋር ያለህን ዝምድና በየቀኑ አጠናክረው፤ ቃሉን በሕይወትህ ውስጥ እንዴት የበለጠ ልትሠራበት እንደምትችል ለማወቅ ተጣጣር፣ በዚህ የነገሮች ሥርዓት የመጨረሻ ቀኖች ውስጥ መንግሥቱን ለማወጅ በሚካሄደው እጅግ በጣም አስፈላጊ በሆነ ሥራ የተቻለህን ያህል ሙሉ ተሳትፎ አድርግ።

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]