በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

‘ከባቢሎን ወጥታችሁ ሽሹ’

‘ከባቢሎን ወጥታችሁ ሽሹ’

ምዕራፍ 11

‘ከባቢሎን ወጥታችሁ ሽሹ’

1. (ሀ) አምላክን ምን ዓይነት አምልኮ እንደሚያስደስተው እንዴት ለማወቅ እንችላለን? (ለ) አምላክ ከምን እንድንሸሽ አሳስቦናል?

ብዙ ሰዎች ሕይወትን በተመለከተ ለሚነሱባቸው ጥያቄዎች አጥጋቢ መልስ ለማግኘት ከአንዱ ሃይማኖት ወደ ሌላው ሄደዋል። በሃይማኖቶቹ ላይ በአንድ በኩል የእምነትና የድርጊት ተመሳሳይነት፣ በሌላው በኩል ደግሞ ብዙ ልዩነቶችን ተመልክተዋል። ይሁን እንጂ የትኞቹ መልሶች እውነት እንደሆኑ፣ የትኞቹ ድርጊቶችም በእርግጥ አምላክን እንደሚያስደስቱ ማንም ሰው እርግጠኛ ለመሆን የሚችለው የአምላክን ቃል መመሪያው አድርጎ ከተጠቀመበት ብቻ ነው። በመጽሐፍ ቅዱስ አማካይነት ፈጣሪ ከራሱና ከዓላማዎቹ ጋር ያስተዋውቀናል። በተጨማሪም የሐሰት አምልኮን ሥረ መሠረት ገልጦ ያሳየናል። ይህንንም በማድረግ “ታላቂቱ ባቢሎን” ብሎ ከሚጠራት ራሳችንን እንድንጠብቅ ያስጠነቅቀናል፤ ከእርሷ ወጥተን ‘እንድንሸሽ’ ብርቱ ማሳሰቢያ ይሰጠናል። ይህንን ማስጠንቀቂያ ተከትለህ እርምጃ ወስደሃልን? — ራእይ 18:4, 21፤ ኤርምያስ 51:6

2. “ታላቂቱ ባቢሎን” ምንድን ነች?

2 “ታላቂቱ ባቢሎን” ምንድን ነች? ከጥንቷ ባቢሎን የበቀሉ አመለካከቶችን፣ እምነቶችን ወይም ድርጊቶችን የሚደግፉ ሃይማኖቶች ሁሉ ጠቅለል ተደርገው ሲታዩ ታላቂቱ ባቢሎን ይባላሉ። በዚህም ምክንያት የጥንቷን ባቢሎን አመሠራረትና ሃይማኖት በመመርመር የታላቂቱ ባቢሎንን መለያ ጠባዮች ማወቅ ይቻላል።

3. (ሀ) የጥንቷ ባቢሎን እንዴት ተመሠረተች? መሥራቿስ ሰዎች ምን ዓይነት መንፈስ እንዲያድርባቸው ያነሳሳ ነበር? (ለ) ያ መንፈስ ዛሬ ባሉት ሃይማኖቶች ላይ በምን መንገድ ተንጸባርቋል?

3 የኖኅ ዘመን የጥፋት ውኃ ካለፈ ከአንድ መቶ ዘመን በላይ ቆይቶ የባቤል ከተማ (በኋላ ባቢሎን ተብላ የተጠራችው) በአንድ ግንብ ዙሪያ ተገነባች። የዕቅዱ ጠንሳሽ ናምሩድ እንደሆነ ከማስረጃዎቹ መገንዘብ ይቻላል። ይህ ናምሩድ በግብረ አበሮቹ ልብ ውስጥ በይሖዋ ላይ የማመፅ መንፈስና ለራሳቸው ታላቅ ክብርን የመፈለግ ምኞት አሳደረ። (ዘፍጥረት 10:9, 10 አዓት፤ 11:1–9) በዛሬው ጊዜ ይህን መንፈስ ታያለህን? ሃይማኖታውያን ነን የሚሉት እንኳን ሳይቀሩ የአምላክን ቃል ችላ ሲሉና ሃይማኖትን ለራስ ትኩረት መሳቢያ፣ አልፎ ተርፎም ትልቅ ክብር ማግኛ አድርገው ሲጠቀሙበት ታያለህን?

4. ባቢሎናዊ ሃይማኖት ስለ ራሱ ስለ አምላክ የሚገልጸውን እውነት ያጣመመው እንዴት ነው?

4 በባቢሎን ሃይማኖት ውስጥ የሥላሴ አማልክት የጐላ ሚና ነበራቸው። አኑ፣ ቤልና ኢአ የተባሉ ሦስት አማልክት ጣምራ የሆነ የሥላሴ አምላክ ነበራቸው። ሌላው የሦስት አማልክት ጣምራ ሲን፣ ሻማሽና ኢሽታር የተባሉ አማልክትን የሚያካትት ነበር። በተጨማሪም የባቢሎን የአምልኮ ቦታዎች በምስሎች የተሞሉ ነበሩ። ይህ ሁሉ፣ ስሙ ይሖዋ የሆነ አንድ አምላክ ብቻ አለ የሚለው ሐቅ እንዲድበሰበስ ወይም እንዲሸፈን አድርጓል። (ዘዳግም 4:39፤ ዮሐንስ 17:3) አማልክቱ አላቸው ተብሎ የሚታሰበው ባሕርይና ተግባር፣ እንዲሁም ብዙ ሰዎች ሕይወት በሌላቸው ምስሎች መጠቀማቸው፣ ስለ ፈጣሪ የተጣመመ ግንዛቤ እንዲቀረጽባቸው አድርጓል። — ኤርምያስ 10:10, 14፤ 50:1, 38፤ 1 ቆሮንቶስ 10:14, 19–22

5. (ሀ) ሞትን በተመለከተ የተስፋፋው ባቢሎናዊ እምነት በአዲስ መልክ ተቀብቶ የቀረበ ሰይጣን ለሔዋን የነገራት የመጀመሪያው ውሸት ነው ለማለት የሚቻለው እንዴት ነው? (ለ) ይህስ ወደ ምን ሌሎች ትምህርቶች የሚመራ ሆኗል?

5 ባቢሎናውያን ሞት ወደ ሌላ ዓይነት ሕይወት የሚያሸጋግር መሰላል ብቻ ነው ብለው ያምኑ ነበር። ይህ ግን አምላክ ለመጀመሪያዎቹ ወላጆቻችን ከነገራቸው ሐሳብ ጋር ይጋጫል። የግሪክ ፈላስፎች ሰው የማትሞት ነፍስ አለችው በማለት ይህን አስተሳሰብ ይበልጥ አዳብረውታል። የዲያብሎስ የመጀመሪያ ውሸት አዳምና ሔዋን ለአምላክ ባይታዘዙም በሥጋ ‘ፈጽሞ አይሞቱም’ የሚል ነበር። አሁን ደግሞ ሰዎች ለዘላለም የምትኖረው እነርሱ ሊያዩዋት የማይችሉ በውስጣቸው የምትገኝ ነገር ነች ተብሎ ይነገራቸው ጀመር። ይህ የሐሰት ትምህርት ማቃጠያ ሲኦል፣ መንጽሔ፣ የቀድሞ አባቶች አምልኮና የመሳሰሉትን ብዙ እምነቶች አስከትሏል። — ዘፍጥረት 3:1–5፤ መክብብ 9:5, 10፤ ሕዝቅኤል 18:4

6. (ሀ) ሥረ መሠረታቸው ባቢሎናዊ ሃይማኖት የሆኑ አሁን ያሉ ሌሎች ልማዶች ምንድን ናቸው? (ለ) ይህስ የቱን ያህል ከባድ ጉዳይ ነው?

6 በተጨማሪም የባቢሎን ሃይማኖት ሰዎች ራሳቸውን ለማበልጸግና ሌሎችን ለመቆጣጠር እንዲያስችላቸው ከሰው ችሎታ በላይ የሆነ እውቀት ለማግኘት የሚሞክሩበትን ኮከብ ቆጠራን፣ ምዋርትን፣ አስማትንና ጥንቆላን ይጨምር ነበር። (ዳንኤል 2:27፤ ሕዝቅኤል 21:21) ስለ እነዚህ ነገሮች ሁሉ መጽሐፍ ቅዱስ ማስጠንቀቂያ ቢሰጥም ዛሬ እነዚህ ድርጊቶች እንዴት በጣም ተስፋፍተዋል! ሰዎች በእነዚህ ልማዶች ጠንቅ በአጋንንት እጅ ይወድቃሉ፤ አጋንንት ደግሞ ለሚሰጡት ጥቅም ጭካኔ የተሞላበት ወሮታ ያስከፍላሉ። — ዘዳግም 18:10–12፤ ኢሳይያስ 8:19፤ ሥራ 16:16፤ ራእይ 18:21, 23

7. ታላቂቱ ባቢሎን (ሀ) ከፖለቲካ ገዥዎች ጋር እንደምትባልግ (ለ) ብዙ ሀብት እንዳላት (ሐ) በደም አፍሳሽነት ተጠያቂ እንደሆነች የሚያረጋግጡ ምን ማስረጃዎችን አይተሃል?

7 የታላቂቱን ባቢሎን ማንነት ለይቶ ለማወቅ የሚረዳ ተጨማሪ ነገርም አለ። መጽሐፍ ቅዱስ ከፖለቲካ መሪዎች ጋር እንደምትባልግ፣ ብዙ ሀብት እንዳላትና ደም አፍሳሽ እንደሆነች፣ የአምላክን አገልጋዮች ደም ጭምር እንደምታፈስ ይናገራል። (ራእይ 17:1–6፤ 18:24) በዚህ በኩል የዓለም ሃይማኖቶች ያስመዘገቡት ታሪክ በአደባባይ የሚታወቅ ነው።

ለእውነት ያለህ ፍቅር ምን ያህል ነው?

8. የታላቂቱ ባቢሎን አምላክ በእርግጥ ማን ነው?

8 አንድ ሰው በየትኛውም የታላቂቱ ባቢሎን ክፍል ውስጥ ቢገኝ፣ በበዓሎቿ ቢካፈል ወይም የእርሷን መንገዶች ቢከተል በዚህ የሚከበረው ማን ነው? ይሖዋ እንዳልሆነ የታወቀ ነው። ከዚህ ይልቅ ግለሰቡ የሰውን ልጆች አእምሮ ላጨለመው ‘ለዚህ የነገሮች ሥርዓት አምላክ’ ወድቆ እንደሰገደለት ያህል ነው። — 2 ቆሮንቶስ 4:4 አዓት

9. ሰይጣን በሃይማኖት ይህን ያህል ብዙ ሰዎች ሊያስት የቻለው እንዴት ነው?

9 ይሁን እንጂ ይህን የሚያህሉ ብዙ ሰዎች ተሳስተው እንዴት ሊጠመዱ ቻሉ? መጽሐፍ ቅዱስ “የእውነትን ፍቅር ስላልተቀበሉ” በሰይጣን ወጥመድ ተይዘዋል በማለት መልሱን ይሰጠናል። (2 ተሰሎንቄ 2:9–12) ይህ ሊያስደንቀን አይገባም። እቤታቸው፣ በሥራ ቦታ ወይም ስሕተታቸው ሲነገራቸው ሁልጊዜ እውነት የሚናገሩ ስንት ሰዎች ታውቃለህ? እውነትን የያዘው የአምላክ ቃል መጽሐፍ ቅዱስ ምን እንደሚል ሲያዩ የቀድሞ እምነታቸውን ወይም ልማዳቸውን፣ አኗኗራቸውንም እንኳን ለመተውና ከቃሉ ጋር ተስማምተው ለመኖር ፈቃደኛ የሚሆኑት ምን ያህል ናቸው? አንተ ራስህ ፈቃደኛ ነህን?

10. (ሀ) ይሖዋ የሚፈልገው ምን ዓይነት ሰዎችን ነው? (ለ) እኛ እንደነዚህ ዓይነት ሰዎች መሆናችንን እንዴት ለማሳየት እንችላለን?

10 ይሖዋ የሚፈልገው ለእውነት እንደዚህ ያለ ፍቅር ያላቸውን ሰዎች ነው። እርሱ ራሱ “የእውነት አምላክ” ነው። (መዝሙር 31:5) የቃሉ ትምህርቶች የሐሳብ ፈጠራ አይደሉም። እውነት ናቸው። ኢየሱስ ለአንዲት ሳምራዊት “በእውነት የሚሰግዱ ለአብ በመንፈስና በእውነት የሚሰግዱበት ጊዜ ይመጣል . . . አብ ሊሰግዱለት እንደ እነዚህ ያሉትን ይሻልና፤ እግዚአብሔር መንፈስ ነው፣ የሚሰግዱለትም በመንፈስና በእውነት ሊሰግዱለት ያስፈልጋቸዋል” ብሏታል። (ዮሐንስ 4:23, 24) አንተስ እንደዚህ ዓይነት ሰው ለመሆን ትፈልጋለህን?

አምላክ ሕዝቡን ነፃ ያወጣበት ሁኔታ

11. (ሀ) በኢሳይያስ 49:8, 9 ላይ አስቀድሞ የተገለጸው ሁኔታ ምንድን ነው? (ለ) የመጀመሪያ ፍጻሜውንስ መቼ አገኘ? (ሐ) ይህስ የእኛን ትኩረት የሚስበው ለምንድን ነው?

11 ይሖዋ እኛ መመሪያ እንድናገኝ ሲል ከረጅም ጊዜ በፊት ሕዝቡን ከባቢሎን የጭቆና ቀንበር እንደሚያላቅቃቸው የሚገልጽ ተስፋ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እንዲመዘገብ አድርጓል። ይህ ትንቢት በታላቁ ቂሮስ አይሁዶችንና እስራኤላውያን ያልሆኑ ናታኒምን ወደ ኢየሩሳሌም ተመልሰው የይሖዋን ቤተ መቅደስ ለመሥራት እንዲችሉ ነፃ ባወጣቸው ጊዜ ተፈጽሟል። ይሁን እንጂ ታሪኩ በዚህ ብቻ አያበቃም። በዚያን ጊዜ የተፈጸመው ነገር በቂሮስ በተመሰለው በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ሌላ ነፃ የመውጣት እርምጃ እንደሚወሰድ ያመለክት ነበር። የእርሱን መመሪያዎች መከተላችን የግል ክብራቸውን ብቻ ለማስጠበቅ የሚሯሯጡ ሰዎች እንዳያታልሉን ይጠብቀናል። ቀጥሎ ያሉትን ቃላት የሚናገረው ትንቢት በተለይ በኢየሱስ ላይ ይሠራል:- “እግዚአብሔር እንዲህ ይላል:- በተወደደ ጊዜ ሰምቼሃለሁ፣ በመድኃኒትም ቀን ረድቼሃለሁ፤ እጠብቅህማለሁ፣ ምድርንም ታቀና ዘንድ፣ ውድማ የሆኑትንም ርስቶች ታወርስ ዘንድ፣ የተጋዙትንም:- ውጡ በጨለማም የተቀመጡትን:- ተገለጡ ትል ዘንድ ቃል ኪዳን አድርጌ ለሕዝቡ ሰጥቼሃለሁ።” (ኢሳይያስ 49:8, 9) ይህ ትንቢት በኢየሱስ ላይ የተፈጸመው እንዴት ነው?

12. (ሀ) ይህ ትንቢት በኢየሱስ ላይ እንዴት ተፈጸመ? (ሉቃስ 4:16–18) (ለ) በዚህስ ውስጥ ለእኛ የሚሆን ምን ማበረታቻ አለ?

12 ይሖዋ የኢየሱስን ጸሎቶች መልሷል። ኢየሱስ ሃይማኖታዊ ሐሰትን በድፍረት ሲያጋልጥና ‘ሰዎችን ነፃ የሚያወጣውን እውነት’ ሲያስታውቅ አምላክ ልጁን ረድቶታል፤ ጠብቆታልም። (ዮሐንስ 8:32) ኢየሱስን ለማጥፋት ብዙ ሰይጣናዊ ጥረቶች ቢደረጉም በምድር ላይ የሚያከናውነውን ሥራ እስኪፈጽም ድረስ ይሖዋ ልጁን ጠብቆታል። ከዚያ በኋላ ይሖዋ ፈጽሞ የማይከስም ሕይወት ሰጥቶ ከሞት በማስነሳት ወደ ሰማይ ወሰደው። እዚያም ሰዎችን ነፃ የማውጣት ሥራውን ቀጠለ። ይሖዋ ኢየሱስን ከታላቂቱ ባቢሎን እስራት ሰዎች ለመፈታታቸው ማረጋገጫ የሚሆን “ቃል ኪዳን” ወይም ማስተማመኛ አድርጎታል። ኢየሱስ ከሞት ተነስቶና የላቀ ክብር ተላብሶ በሰማይ እንደሚገኝ ሁሉ ቅን ልብ ያላቸው ሰዎች በሙሉ ከታላቂቱ ባቢሎን ሃይማኖታዊ ጨለማ ነፃ መውጣታቸው የተረጋገጠ ነገር ነው። አንተስ የዚህ ነፃነት ተጠቃሚ ትሆናለህን?

13. ከ36 እዘአ ጀምሮ ኢየሱስ “ለአሕዛብ ብርሃን” የሆነው እንዴት ነው?

13 ነፃ የማውጣቱ እርምጃ ምን ያህል ስፋት እንደሚኖረው ለማመልከት ይሖዋ “እስከ ምድር ዳር ድረስ መድኃኒት ትሆን ዘንድ ለአሕዛብ ብርሃን አድርጌ ሰጥቼሃለሁ” በማለት አስቀድሞ ተናግሮ ነበር። (ኢሳይያስ 49:6) ስለዚህ በ36 እዘአ አሕዛብ ወይም አይሁድ ካልሆኑ ብሔራት የመጡ ሰዎች ከመንፈሳዊ እስራኤል ጉባኤ ጋር እንዲቀላቀሉ ተደረገ። ይሁን እንጂ በቅቡዓን ክርስቲያኖች ጉባኤ ውስጥ የአሕዛብ መጨመር ኢየሱስ “ለአሕዛብ ብርሃን” ይሆናል ለሚለው ትንቢት የተሟላ ፍጻሜ አይሆንም።

14. (ሀ) “ከአሕዛብ” ውስጥ ኢየሱስ ብርሃን የሚሆነው ለእነማን ጭምር ነው? (ለ) የጥንቷ ባቢሎንን ለቀው የወጡ የትኞቹ ወገኖች ለእነርሱ ጥላ ነበሩ? (ሐ) እነርሱስ ኢሳይያስ 49:10 በሚፈጸምበት ጊዜ ምን ዓይነት መንፈሳዊ በረከቶችን አግኝተዋል?

14 ኢየሱስ በምድር ላይ የዘላለም ሕይወት የሚያገኙ ‘ሌሎች በጎችንም’ ወደፊት እንደሚሰበሰብ ያውቅ ነበር። (ዮሐንስ 10:16) አይሁዶች በ537 ከዘአበ ከባቢሎን በወጡ ጊዜ አብረዋቸው የተጓዙት እስራኤላውያን ያልሆኑ ናታኒምና የሰሎሞን ባሪያዎች ልጆች የእነርሱ ጥላ ነበሩ። (ዕዝራ 2:1, 43–58) በዚህ ዘመን እጅግ ብዙ ሰዎች ከታላቂቱ ባቢሎን “ውጡ” የሚለውን ትእዛዝ ፈጽመዋል። እነዚህ ሰዎች በአሁኑ ጊዜ በኢሳይያስ 49:10 ላይ “የሚራራላቸውም ይመራቸዋልና፣ በውኃም ምንጮች በኩል ይነዳቸዋልና አይራቡም፣ አይጠሙም፣ ትኩሳት ወይም ፀሐይ አይጎዳቸውም” ተብለው የተተነበዩትን አርኪ መንፈሳዊ በረከቶች በማግኘት እየተደሰቱ ነው። በራእይ 7:9, 16, 17 ላይም እነዚህ በረከቶች ‘የሌሎች በጎች’ ክፍል ለሆኑት “እጅግ ብዙ ሰዎች” እንደሚሠሩ በትክክል ተገልጿል።

“ሕዝቤ ሆይ፣ . . . ከእርስዋ ዘንድ ውጡ”

15. የአምላክ ሕዝብ ለመሆን የሚፈልጉ ሁሉ ከታላቂቱ ባቢሎን እንዲወጡ መጽሐፍ ቅዱስ የሚያስጠነቅቀው ለምንድን ነው?

15 አምላክ የሚያስፈጽመው የቅጣት ፍርድ ለታላቂቱ ባቢሎን ምን ማለት እንደሚሆን ሐዋርያው ዮሐንስ በመንፈስ በተገለጠለት ራእይ ውስጥ አይቷል። ይህ ጉዳይ በጣም እርግጠኛ ነገር በመሆኑ አንድ መልአክ “ሕዝቤ ሆይ፣ በኃጢአትዋ እንዳትተባበሩ ከመቅሰፍትዋም እንዳትቀበሉ ከእርስዋ ዘንድ ውጡ፤ ኃጢአትዋ እስከ ሰማይ ድረስ ደርሶአልና፣ እግዚአብሔርም ዓመፃዋን አሰበ” በማለት አምላክን ወክሎ ከሰማይ ማስጠንቀቂያ አሰምቷል። — ራእይ 18:4, 5

16. ይህንን ትእዛዝ በእርግጥ ፈጽመነው እንደሆነ የሚያመለክተው ምንድን ነው?

16 የመንፈሳዊ እስራኤል አባላት ይህንን ትእዛዝ በመከተል እርምጃ ወስደዋል። ሌሎች ሰዎችም አርአያቸውን እንዲከተሉ እያሳሰቡ ነው። አንድ ሰው እውነተኛውን አምልኮ ከሐሰተኛው ጋር ቀላቅሎ ከያዘ አምላክን ማስደሰት እንደማይችል ያውቃሉ። አንድ ሰው ከይሖዋ ምሥክሮች ጋር ቢቀራረብም ከታላቂቱ ባቢሎን ጋር ያለውን ግንኙነት እስካላቋረጠ ድረስ እንዴት የእርስዋ ክፍል አይደለሁም ለማለት ይችላል? ወደ ቤተ ክርስቲያን ባይሄድም እንኳን በተቀጠረበት መሥሪያ ቤት ወይም ከዘመዶቹ ጋር ሆኖ በሃይማኖታዊ በዓሎቿ የሚካፈል ከሆነ አሁንም ርኩስ የሆነውን ነገር እየነካ ነው። (ኢሳይያስ 52:11) ነፍስ አትሞትም የሚል ወይም ክፉ መናፍስትን የመፍራት አጉል እምነት በሚያንፀባርቁ የቤተሰብ ልማዶች የሚካፈል ከሆነ አሁንም በኃጢአቷ ገና እየተካፈለ ነው። መሐል ላይ መቆም አንችልም። ይሖዋ እውነተኛ አምላክ ነው ብለን የምናምን ከሆነ እርሱን ብቻ ማገልገል አለብን። — 1 ነገሥት 18:21

17. (ሀ) በራእይ 14:6, 7 ላይ እንደተገለጸው በየትም ቦታ የሚገኙ ሰዎች ምን እንዲያደርጉ ተጋብዘዋል? (ለ) ተቀባይነት ባለው መንገድ ይሖዋን ለማምለክ ምን ሌላ ትእዛዝ መፈጸም ይገባቸዋል?

17 ብቻውን እውነተኛ አምላክ የሆነውን ይሖዋን ከእኛ ጋር ተቀላቅላችሁ አምልኩት የሚለው ማራኪ ጥሪ አሁንም በሁሉም ብሔራት፣ ጐሣዎችና ልሳናት ለሚገኙ ሰዎች እየቀረበ ነው! (ራእይ 14:6, 7) ይህንን ለማድረግ “ከባቢሎን ውስጥ ሽሹ፣ እያንዳንዳችሁ ነፍሳችሁን አድኑ” የሚለውን ትእዛዝ የተቀበሉትን የጥንት የአምላክ አገልጋዮች አርአያ መከተል ይኖርብሃል። — ኤርምያስ 51:6

[የአንቀጾቹ ጥያቄዎች]