በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ለሕይወትና ለደም አክብሮት ማሳየት

ለሕይወትና ለደም አክብሮት ማሳየት

ትምህርት 12

ለሕይወትና ለደም አክብሮት ማሳየት

ለሕይወት እንዴት ያለ አመለካከት ሊኖረን ይገባል? (1) ለውርጃስ? (1)

ክርስቲያኖች በሕይወት ላይ አደጋ እንዳይደርስ አጥብቀው የሚያስቡ መሆናቸውን የሚያሳዩት እንዴት ነው? (2)

እንስሳትን መግደል ስህተት ነውን? (3)

ለሕይወት አክብሮት እንደሌለን የሚያሳዩ አንዳንድ ድርጊቶች ምንድን ናቸው? (4)

አምላክ ስለ ደም የሰጠው ሕግ ምንድን ነው? (5)

ይህስ ደም በደም ሥር መውሰድን ይጨምራልን? (6)

1. የሕይወት ሁሉ ምንጭ ይሖዋ ነው። ሕያዋን ፍጥረታት በሙሉ ሕይወታቸውን ያገኙት ከአምላክ ነው። (መዝሙር 36:9) ሕይወት በአምላክ ዓይን ቅዱስ ነው። በእናት ማኅፀን ውስጥ ያለ ገና ያልተወለደ ሕፃን ሕይወት እንኳን በይሖዋ ዘንድ በጣም ውድ ነው። እንዲህ ያለውን ገና በማደግ ላይ ያለ ጽንስ ሆን ብሎ መግደል በአምላክ ዘንድ ኃጢአት ነው።​—ዘጸአት 21:22, 23፤ መዝሙር 127:3

2. እውነተኛ ክርስቲያኖች በሕይወት ላይ አደጋ የሚያደርሱ ሁኔታዎች እንዳይኖሩ አጥብቀው ይጠነቀቃሉ። መኪኖቻቸውና ቤቶቻቸው አደጋ ሊያስከትሉ የሚችሉ ሁኔታዎች እንዳይኖሯቸው ጥንቃቄ ያደርጋሉ። (ዘዳግም 22:8) የአምላክ አገልጋዮች ደስታ ለማግኘት ብለው የራሳቸውን ሕይወት ለአደጋ አያጋልጡም። በዚህም ምክንያት በሌሎች ላይ ጉዳት በሚያደርሱ የድብድብ ስፖርቶች አይካፈሉም። ጠበኝነትን ከሚያበረታቱ መዝናኛዎች ይርቃሉ።​—መዝሙር 11:5፤ ዮሐንስ 13:35

3. የእንስሳት ሕይወትም ቢሆን በፈጣሪ ዓይን ቅዱስ ነው። አንድ ክርስቲያን ለምግብና ለልብስ እንዲያገለግሉት ወይም ራሱን ከበሽታና ከአደጋ ለማዳን እንስሳትን መግደል ይችላል። (ዘፍጥረት 3:21፤ 9:3፤ ዘጸአት 21:28) ይሁን እንጂ ለስፖርት ወይም ለጨዋታ ብሎ እንስሳትን ማሠቃየት ወይም መግደል ስህተት ነው።​—ምሳሌ 12:10

4. ማጨስ፣ ጫት መቃምና ለደስታ ሲሉ ዕፆችን መውሰድ ለክርስቲያኖች የማይገባ ልማድ ነው። እነዚህ ልማዶች (1) ባሮቻቸው ስለሚያደርጉን፣ (2) አካላችንን ስለሚጎዱና (3) ርኩስ ስለሆኑ ስህተት ናቸው። (ሮሜ 6:19፤ 12:1፤ 2 ቆሮንቶስ 7:1) እነዚህን ልማዶች ማቆም በጣም ከባድ ሊሆን ይችላል። ቢሆንም ይሖዋን ለማስደሰት ስንል የግድ ማቆም ይኖርብናል።

5. ደምም በአምላክ ዓይን ቅዱስ ነው። አምላክ ነፍስ ወይም ሕይወት በደም ውስጥ እንደሆነ ይናገራል። ስለዚህ ደም መብላት ስህተት ነው። በተጨማሪም በሥርዓት ታርዶ ደሙ ያልፈሰሰ ከብት ሥጋ መብላት ስህተት ነው። አንድ እንስሳ ታንቆ ወይም በወጥመድ ተይዞ ቢሞት መበላት የለበትም። በጥይት ከተመታ ወይም በጦር ከተወጋ ወዲያው ደሙ እንዲፈስ ካልተደረገ ሥጋው መበላት የለበትም።​—ዘፍጥረት 9:3, 4፤ ዘሌዋውያን 17:13, 14፤ ሥራ 15:28, 29

6. ደም በደም ሥር መውሰድ ስህተት ነውን? ይሖዋ ከደም እንድንርቅ እንደሚፈልግ አስታውስ። ይህ ማለት የማንንም ሰው ደም፣ ከሰውነታችን ወጥቶ የተቀመጠ የራሳችን ደም እንኳ ሳይቀር በምንም ዓይነት መንገድ ወደ ሰውነታችን እንዲገባ መፍቀድ የለብንም ማለት ነው። (ሥራ 21:25) በዚህ ምክንያት እውነተኛ ክርስቲያኖች ደም አይወስዱም። ከደም ነጻ የሆኑ መድኃኒቶችን በደም ሥር መውሰድን ጨምሮ ሌሎች ዓይነት ሕክምናዎችን ይቀበላሉ። መኖር የሚፈልጉ ቢሆኑም የአምላክን ሕግ በመጣስ ሕይወታቸውን ለማቆየት አይሞክሩም።​—ማቴዎስ 16:25

[በገጽ 25 ላይ የሚገኙ ሥዕሎች]

አምላክን ለማስደሰት ከፈለግን ደም በደም ሥራችን አንወስድም፣ ከርኩስ ልማዶች እንርቃለን፣ ሕይወታችንን ተገቢ ባልሆነ መንገድ አደጋ ላይ አንጥልም