በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 51

በልደት ግብዣ ላይ የተፈጸመ ግድያ

በልደት ግብዣ ላይ የተፈጸመ ግድያ

ማቴዎስ 14:1-12 ማርቆስ 6:14-29 ሉቃስ 9:7-9

  • ሄሮድስ የመጥምቁ ዮሐንስን አንገት አስቆረጠ

የኢየሱስ ሐዋርያት በገሊላ አገልግሎታቸውን እያከናወኑ ነው፤ ኢየሱስን ለሕዝቡ ያስተዋወቀው ሰው ግን እንዲህ ያለ ነፃነት ተነፍጓል። መጥምቁ ዮሐንስ ከታሰረ ሁለት ዓመት ገደማ ሆኖታል።

ሄሮድስ አንቲጳስ፣ የወንድሙን የፊልጶስን ሚስት ሄሮድያዳን የራሱ ሚስት አድርጎ በመውሰዱ ዮሐንስ በሕዝብ ፊት አውግዞት ነበር። ሄሮድስ፣ ሄሮድያዳን ለማግባት ሲል የመጀመሪያ ሚስቱን ፈትቷል። ሄሮድስ የሙሴን ሕግ እከተላለሁ ቢልም የፈጸመው ጋብቻ በሕጉ መሠረት ምንዝር ከመሆኑም ሌላ ሕጋዊ አይደለም። ዮሐንስ የሄሮድስን ድርጊት በማውገዙ ሄሮድስ ወህኒ አወረደው፤ ምናልባትም ይህን ያደረገው በሄሮድያዳ ውትወታ ሊሆን ይችላል።

ሄሮድስ፣ ዮሐንስን ምን እንደሚያደርገው ግራ ገብቶታል፤ ምክንያቱም ዮሐንስን ‘ሕዝቡ እንደ ነቢይ ይመለከተዋል።’ (ማቴዎስ 14:5) ሄሮድያዳ ግን ይህ ጉዳይ አላስጨነቃትም። ‘በዮሐንስ ላይ ቂም የያዘች’ ሲሆን እንዲያውም እሱን የምታስገድልበትን መንገድ እየፈለገች ነው። (ማርቆስ 6:19) በመጨረሻም ስትፈልገው የነበረው አጋጣሚ ተፈጠረ።

በ32 ዓ.ም. ከሚከበረው የፋሲካ በዓል ጥቂት ቀደም ብሎ ሄሮድስ የልደት ቀኑን ለማክበር አንድ ትልቅ ድግስ አዘጋጀ። የሄሮድስ ከፍተኛ ባለሥልጣናትና የጦር አዛዦች በሙሉ እንዲሁም በገሊላ ያሉ ታላላቅ ሰዎች በግብዣው ላይ ተገኙ። በድግሱ መሃል፣ ሄሮድያዳ ከቀድሞ ባሏ ከፊልጶስ የወለደቻት ሰሎሜ የተባለች ልጇ በእንግዶቹ ፊት እንድትጨፍር ተላከች። ሰዎቹም በውዝዋዜዋ በጣም ተደሰቱ።

ሄሮድስ በሰሎሜ እጅግ ስለተደሰተ “የፈለግሽውን ሁሉ ጠይቂኝ፣ እሰጥሻለሁ” አላት። እንዲያውም “እስከ መንግሥቴ እኩሌታ እንኳ ቢሆን የምትጠይቂኝን ሁሉ እሰጥሻለሁ” ሲል ማለላት። ሰሎሜም መልስ ከመስጠቷ በፊት ወደ እናቷ ሄዳ “ምን ብጠይቀው ይሻላል?” አለቻት።—ማርቆስ 6:22-24

ይህ ሄሮድያዳ ስትጠብቀው የነበረው አጋጣሚ ነው! ምንም ሳታመነታ “የአጥማቂው ዮሐንስን ራስ ጠይቂው” አለቻት። ሰሎሜ ወዲያውኑ ወደ ሄሮድስ ተመልሳ “የመጥምቁ ዮሐንስን ራስ አሁኑኑ በሳህን እንድትሰጠኝ እፈልጋለሁ” ስትል ጠየቀችው።—ማርቆስ 6:24, 25

ሄሮድስ ይህን ማድረግ እጅግ አስጨነቀው፤ ሆኖም እንግዶቹ ለሰሎሜ ሲምልላት ሰምተዋል። ያቀረበችው ጥያቄ አንድ ንጹሕ ሰው ሕይወቱን እንዲያጣ የሚያደርግ ቢሆንም እንኳ የጠየቀችውን አለመስጠት ደግሞ አሳፈረው። በመሆኑም ሄሮድስ ይህን ዘግናኝ ተልእኮ እንዲፈጽም አንድ ጠባቂ ወደ እስር ቤቱ ላከ። ብዙም ሳይቆይ ጠባቂው የዮሐንስን ራስ በሳህን ይዞ መጣ። ከዚያም ለሰሎሜ ሰጣት፤ እሷም ወደ እናቷ ወሰደችው።

የዮሐንስ ደቀ መዛሙርት ይህን በሰሙ ጊዜ መጥተው አስከሬኑን በመውሰድ ቀበሩት። ከዚያም የተፈጸመውን ነገር ለኢየሱስ ነገሩት።

ከጊዜ በኋላ ሄሮድስ፣ ኢየሱስ ሰዎችን እየፈወሰና አጋንንትን እያስወጣ መሆኑን ሲሰማ ፍርሃት አደረበት። እነዚህን ነገሮች እያደረገ ያለው ኢየሱስ የተባለው ሰው፣ ‘ከሞት የተነሳው’ መጥምቁ ዮሐንስ ሊሆን እንደሚችል አሰበ። (ሉቃስ 9:7) በመሆኑም ሄሮድስ አንቲጳስ፣ ኢየሱስን ለማየት በጣም ይጓጓ ጀመር። ዓላማው የኢየሱስን ስብከት ለመስማት እንዳልሆነ ግልጽ ነው። ሄሮድስ ኢየሱስን ማየት የፈለገው ጥርጣሬው ትክክል መሆን አለመሆኑን ለማረጋገጥ ነው።