በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 31

በሰንበት እሸት መቅጠፍ

በሰንበት እሸት መቅጠፍ

ማቴዎስ 12:1-8 ማርቆስ 2:23-28 ሉቃስ 6:1-5

  • ደቀ መዛሙርቱ በሰንበት እሸት ቀጠፉ

  • ኢየሱስ “የሰንበት ጌታ” ነው

ኢየሱስና ደቀ መዛሙርቱ በስተ ሰሜን ወደ ገሊላ እየተጓዙ ነው። ጊዜው የጸደይ ወቅት ስለሆነ በማሳዎቹ ላይ ያለው አዝመራ አሽቷል። ደቀ መዛሙርቱ ስለራባቸው እሸቱን ቀጥፈው በሉ። ዕለቱ ሰንበት ነው፤ ፈሪሳውያኑም ይህን ሲያደርጉ ተመለከቷቸው።

ከጥቂት ጊዜ በፊት፣ በኢየሩሳሌም የሚገኙ አንዳንድ አይሁዳውያን ኢየሱስ የሰንበትን ሕግ እንደጣሰ በመግለጽ ሊገድሉት ፈልገው እንደነበር አስታውስ። አሁን ደግሞ ፈሪሳውያን፣ ደቀ መዛሙርቱን ባደረጉት ነገር ከሰሷቸው። “ተመልከት! ደቀ መዛሙርትህ በሰንበት ቀን በሕግ የተከለከለ ነገር እያደረጉ ነው” አሉት።—ማቴዎስ 12:2

ፈሪሳውያን እሸት መቅጠፍና በእጅ አሽቶ መብላት ከማጨድና ከመውቃት ተለይቶ እንደማይታይ ይናገራሉ። (ዘፀአት 34:21) ሰንበት የተሰጠበት ዓላማ ዕለቱ አስደሳችና በመንፈሳዊ የሚገነባ እንዲሆን ታስቦ ቢሆንም ፈሪሳውያን ሥራ ሲባል ምን ነገሮችን እንደሚጨምር የሚሰጡት የማያፈናፍን ፍቺ ስለ ሰንበት የተሰጠው ሕግ ሸክም እንዲሆን አድርጓል። ስለዚህ ኢየሱስ አመለካከታቸው የተሳሳተ መሆኑን ለማሳየት ይሖዋ አምላክ የሰንበትን ሕግ ያወጣው በዚህ መንገድ እንዲሠራበት አስቦ እንዳልሆነ የሚጠቁሙ ቅዱስ ጽሑፋዊ ምሳሌዎች ጠቀሰ።

ኢየሱስ የጠቀሰው አንዱ ምሳሌ ስለ ዳዊትና አብረውት ስለነበሩት ሰዎች ነው። እነዚህ ሰዎች በተራቡ ጊዜ ወደ ማደሪያው ድንኳን ሄደው በአምላክ ፊት የቀረበውን ኅብስት ወይም ዳቦ በልተዋል። ይህ ዳቦ በይሖዋ ፊት ከቀረበ በኋላ በሌላ ትኩስ ዳቦ ሲተካ በደንቡ መሠረት ለካህናቱ ይቀመጣል። ሆኖም በወቅቱ ከነበረው ሁኔታ አንጻር ዳዊትና ከእሱ ጋር የነበሩት ሰዎች ይህን ዳቦ መብላታቸው እንደ ጥፋት አልተቆጠረም።—ዘሌዋውያን 24:5-9፤ 1 ሳሙኤል 21:1-6

ኢየሱስ እንዲህ ሲል ሌላም ምሳሌ አቀረበ፦ “ካህናት የሰንበትን ሕግ እንደሚተላለፉና ይህም እንደ በደል እንደማይቆጠርባቸው በሕጉ ላይ አላነበባችሁም?” ይህን ሲል በሰንበት ቀንም እንኳ ካህናቱ መሥዋዕት የሚሆኑ እንስሳትን እንደሚያርዱና በቤተ መቅደሱ ውስጥ ሌሎች ሥራዎችን እንደሚያከናውኑ መግለጹ ነው። ኢየሱስ “እኔ ግን እላችኋለሁ፣ ከቤተ መቅደሱ የሚበልጥ እዚህ አለ” አላቸው። (ማቴዎስ 12:5, 6፤ ዘኁልቁ 28:9) ኢየሱስ በአምላክ የተሾመ ሊቀ ካህናት እንደመሆኑ መጠን በሰንበት ዕለት ኃላፊነቱን መወጣት ይችላል፤ እንዲህ ማድረጉ የሰንበትን ሕግ ጥሷል አያስብለውም።

ኢየሱስ ቀጥሎም ከቅዱሳን መጻሕፍት ሌላ ማስረጃ አቀረበ፦ “‘እኔ የምፈልገው ምሕረትን እንጂ መሥዋዕትን አይደለም’ የሚለውን ቃል ትርጉም ተረድታችሁ ቢሆን ኖሮ ምንም በደል ባልሠሩት ላይ ባልፈረዳችሁ ነበር።” ከዚያም “የሰው ልጅ የሰንበት ጌታ ነውና” በማለት ንግግሩን ደመደመ። እንዲህ ሲል በመንግሥቱ ለሺህ ዓመት የሚገዛበትን ሰላማዊ ወቅት ማመልከቱ ነው።—ማቴዎስ 12:7, 8፤ ሆሴዕ 6:6

የሰው ዘር፣ ዓመፅና ጦርነት በተስፋፋበት የሰይጣን አስጨናቂ አገዛዝ እንደ ባሪያ ሲማቅቅ ኖሯል። በሌላ በኩል ግን ክርስቶስ ሲገዛ በሚኖረው ታላቁ ሰንበት እንዴት ያለ እረፍት እናገኛለን! እንዲህ ያለ እረፍት በጣም የሚያስፈልገን ከመሆኑም ሌላ በጉጉት የምንጠብቀው ነገር ነው።