በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ምዕራፍ 8

ከጨካኝ ገዢ አመለጡ

ከጨካኝ ገዢ አመለጡ

ማቴዎስ 2:13-23

  • የኢየሱስ ቤተሰብ ወደ ግብፅ ሸሸ

  • ዮሴፍ ቤተሰቡን ወደ ናዝሬት ወሰደ

ዮሴፍ ማርያምን ከእንቅልፏ ቀስቅሶ አንድ አስቸኳይ መልእክት ነገራት። የይሖዋ መልአክ በሕልም ተገልጦ እንዲህ ብሎታል፦ “ሄሮድስ ሕፃኑን አፈላልጎ ሊገድለው ስላሰበ ተነስ፣ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ ግብፅ ሽሽ፤ እኔ እስካሳውቅህም ድረስ እዚያው ቆይ።”—ማቴዎስ 2:13

ወዲያውኑ ዮሴፍና ማርያም ልጃቸውን ይዘው በሌሊት በመሸሽ አመለጡ። የሸሹት ጥሩ ጊዜ ላይ ነው፤ ምክንያቱም በዚህ ወቅት ሄሮድስ ኮከብ ቆጣሪዎቹ እንዳታለሉት አውቋል። ኮከብ ቆጣሪዎቹ ኢየሱስን ሲያገኙት ተመልሰው መጥተው እንዲነግሩት ሄሮድስ አዟቸው ነበር። እነሱ ግን ይህን ሳያደርጉ ወደ አገራቸው ተመለሱ። በዚህም ሄሮድስ በጣም ተናደደ። ኢየሱስን ለመግደል ሲል በቤተልሔምና በዙሪያዋ ያሉ ሁለት ዓመትና ከዚያ በታች የሆኑ ወንዶች ልጆች በሙሉ እንዲገደሉ አዘዘ። ይህን ዕድሜ ያሰላው ከምሥራቅ የመጡት ኮከብ ቆጣሪዎች ቀደም ሲል በሰጡት መረጃ ላይ በመመርኮዝ ነው።

የእነዚያ ሁሉ ሕፃናት እልቂት በጣም የሚሰቀጥጥ ነገር ነው! ምን ያህል ሕፃናት እንደተገደሉ ማወቅ አንችልም፤ ሆኖም ልጆቻቸውን ያጡት እናቶች መራራ ለቅሶና ዋይታ፣ የአምላክ ነቢይ የሆነው ኤርምያስ የተናገረው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኝ አንድ ትንቢት እንዲፈጸም አድርጓል።—ኤርምያስ 31:15

በዚህ መሃል፣ ዮሴፍና ቤተሰቡ ወደ ግብፅ ሸሽተው በዚያ መኖር ጀምረዋል። አንድ ሌሊት የይሖዋ መልአክ እንደገና ለዮሴፍ በሕልም ተገለጠለት። መልአኩ “ተነስ፣ የሕፃኑን ሕይወት ለማጥፋት የሚፈልጉት ሰዎች ስለሞቱ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ እስራኤል ምድር ተመለስ” አለው። (ማቴዎስ 2:20) ዮሴፍ ይህን ሲሰማ እሱና ቤተሰቡ ወደ ትውልድ አገራቸው መመለስ እንደሚችሉ ተገነዘበ። ይህም የአምላክ ልጅ ከግብፅ እንደሚጠራ የሚናገረው ሌላ የመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢት እንዲፈጸም አድርጓል።—ሆሴዕ 11:1

ዮሴፍ፣ በይሁዳ ውስጥ ይኸውም ወደ ግብፅ ከመሸሻቸው በፊት ይኖሩባት በነበረችው በቤተልሔም አቅራቢያ ለመኖር የፈለገ ይመስላል። ሆኖም የሄሮድስ ልጅ የሆነው ክፉው አርኬላዎስ የይሁዳ ንጉሥ እንደሆነ ተረዳ። በተጨማሪም ወደዚያ መሄዱ አደገኛ እንደሆነ አምላክ በሌላ ሕልም አማካኝነት አስጠነቀቀው። ስለዚህ ዮሴፍና ቤተሰቡ ወደ ሰሜን ተጉዘው በገሊላ ክልል ውስጥ በምትገኘው በናዝሬት ከተማ መኖር ጀመሩ፤ ኢየሱስ የአይሁድ ሃይማኖታዊ እንቅስቃሴ ማዕከል ከሆነችው ከኢየሩሳሌም ርቆ በዚህ ማኅበረሰብ ውስጥ አደገ። ይህ ደግሞ “የናዝሬት ሰው ይባላል” የሚለው ትንቢት እንዲፈጸም አድርጓል።—ማቴዎስ 2:23