በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ሐዋርያቱን መምረጥ

ሐዋርያቱን መምረጥ

ምዕራፍ 34

ሐዋርያቱን መምረጥ

አጥማቂው ዮሐንስ ኢየሱስን የእግዚአብሔር በግ ብሎ ለሕዝብ ካስተዋወቀውና ኢየሱስም ሕዝባዊ አገልግሎቱን ከጀመረ አንድ ዓመት ተኩል ገደማ ሆኖታል። በዚያ ወቅት እንድርያስ፣ ስምዖን ጴጥሮስ፣ ዮሐንስና ምናልባትም ያዕቆብ (የዮሐንስ ወንድም)፣ እንዲሁም ፊልጶስና ናትናኤል (በርተሎሜዎስ ተብሎም ይጠራል) የመጀመሪያዎቹ የኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱ ሆነው ነበር። ከጊዜ በኋላ ሌሎች ብዙ ሰዎች ከእነርሱ ጋር በመቀላቀል የክርስቶስ ተከታዮች ሆኑ።

አሁን ኢየሱስ ሐዋርያቱን ለመምረጥ ተዘጋጅቷል። እነዚህ ሰዎች ልዩ ሥልጠና የሚሰጣቸው የቅርብ ወዳጆቹ ይሆናሉ። ሆኖም ኢየሱስ እነርሱን ከመምረጡ በፊት ወደ አንድ ተራራ ላይ ወጣና ሌሊቱን ሙሉ ሲጸልይ አደረ። ይህን ያደረገው ጥበብና የአምላክን በረከት ለማግኘት ሳይሆን አይቀርም። ከዚያም ሲነጋ ደቀ መዛሙርቱን ጠራና ከመካከላቸው አሥራ ሁለቱን መረጠ። ይሁን እንጂ የኢየሱስ ተማሪዎች መሆናቸው ስለማይቀር አሁንም ቢሆን ደቀ መዛሙርት ተብለው ይጠራሉ።

ኢየሱስ ከመረጣቸው መካከል ስድስቱ ስማቸው ከላይ የተገለጸው የመጀመሪያዎቹ ደቀ መዛሙርት ናቸው። ኢየሱስ ከቀረጥ መሰብሰቢያ ቦታው የጠራው ማቴዎስም ተመርጧል። የተቀሩት አምስቱ ደግሞ ይሁዳ (ታዴዎስ ተብሎም ይጠራል)፣ የአስቆሮቱ ይሁዳ፣ ቀነናዊው ስምዖን፣ ቶማስና የእልፍዮስ ልጅ ያዕቆብ ናቸው። ይኼኛው ያዕቆብ ትንሹ ያዕቆብ ተብሎም ይጠራል። ይህ የሆነው ምናልባትም ከሌላኛው ሐዋርያ ያዕቆብ በሰውነት አቋሙ ወይም በዕድሜ የሚያንስ ሆኖ ሊሆን ይችላል።

በዚህ ወቅት እነዚህ 12 ሰዎች ከኢየሱስ ጋር ረዘም ላለ ጊዜ አብረው የቆዩ በመሆኑ በደንብ ያውቃቸዋል። እንዲያውም አንዳንዶቹ የራሱ ዘመዶች ናቸው። ያዕቆብና ዮሐንስ የኢየሱስ የአክስት ልጆች እንደሆኑ ከሁኔታው በግልጽ መረዳት ይቻላል። በተጨማሪም እልፍዮስ የኢየሱስ የእንጀራ አባት የሆነው የዮሴፍ ወንድም ሳይሆን አይቀርም። ስለዚህ የእልፍዮስ ልጅ የሆነው ሐዋርያው ያዕቆብም የኢየሱስ የአጎት ልጅ መሆን አለበት።

እርግጥ ኢየሱስ የሐዋርያቱን ስም የማስታወስ ችግር አልነበረበትም። ይሁን እንጂ አንተ ስማቸውን ታስታውሰዋለህን? ሁለት ስምዖኖች፣ ሁለት ያዕቆቦች፣ ሁለት ይሁዳዎች እንዳሉና ስምዖን እንድርያስ የሚባል ወንድም እንዳለው፣ ያዕቆብ ደግሞ ዮሐንስ የሚባል ወንድም እንዳለው አስታውስ። ይህ ስምንት ሐዋርያትን ለማስታወስ የሚያስችል ቁልፍ ነው። የተቀሩት አራቱ ቀረጥ ሰብሳቢ የነበረው (ማቴዎስ)፣ በኋላ ተጠራጥሮ የነበረው (ቶማስ)፣ ከዛፍ ሥር ተቀምጦ ሳለ የተጠራው (ናትናኤል) እና ጓደኛው ፊልጶስ ናቸው።

አሥራ አንዱ ሐዋርያት ኢየሱስ የኖረባት የገሊላ ተወላጆች ናቸው። ናትናኤል የቃና ሰው ነው። ፊልጶስ፣ ጴጥሮስና እንድርያስ የትውልድ ከተማቸው ቤተ ሳይዳ ስትሆን ከጊዜ በኋላ ግን ጴጥሮስና እንድርያስ በቅፍርናሆም መኖር ጀምረው ነበር። ማቴዎስም ይኖር የነበረው በቅፍርናሆም ሳይሆን አይቀርም። ያዕቆብና ዮሐንስ ዓሣ በማጥመድ ሥራ ተሠማርተው የነበረ በመሆኑ እነርሱም ይኖሩ የነበረው በቅፍርናሆም ውስጥ አለዚያም በአቅራቢያዋ ሳይሆን አይቀርም። የይሁዳ ተወላጅ የሆነው ሐዋርያ ከጊዜ በኋላ ኢየሱስን አሳልፎ የሰጠው የአስቆሮቱ ይሁዳ ብቻ የነበረ ይመስላል። ማርቆስ 3:​13-19፤ ሉቃስ 6:​12-16

▪ የኢየሱስ ዘመዶች ሊሆኑ ይችላሉ የሚባሉት ሐዋርያት እነማን ናቸው?

▪ የኢየሱስ ሐዋርያት እነማን ናቸው? ስማቸውንስ እንዴት ማስታወስ ትችላለህ?

▪ የሐዋርያቱ የትውልድ ቦታ የት ነው?