በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ማቴዎስ ተጠራ

ማቴዎስ ተጠራ

ምዕራፍ 27

ማቴዎስ ተጠራ

ኢየሱስ ሽባውን ከፈወሰ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ከቅፍርናሆም ወጥቶ ወደ ገሊላ ባሕር ሄደ። አሁንም ብዙ ሰዎች ወደ እሱ መጡና ያስተምራቸው ጀመር። ከዚያም ተነስቶ ሲሄድ ሌዊ ተብሎም የሚጠራውን ማቴዎስን በቀረጥ መሰብሰቢያው ቦታ ተቀምጦ አየው። ኢየሱስ “ተከተለኝ” የሚል ጥሪ አቀረበለት።

ጴጥሮስ፣ እንድርያስ፣ ያዕቆብና ዮሐንስ በተጠሩበት ጊዜ ስለ ኢየሱስ ትምህርቶች አስቀድመው ያውቁ እንደነበረ ሁሉ ማቴዎስም ስለ ኢየሱስ ትምህርት አስቀድሞ ሳይሰማ አይቀርም። በተጨማሪም ማቴዎስ ልክ እንደነሱ ወዲያውኑ ለጥሪው አዎንታዊ ምላሽ ሰጥቷል። የቀረጥ ሰብሳቢነት ኃላፊነቱን ሁሉ በመተው ተነሥቶ ኢየሱስን ተከተለው።

በኋላም ማቴዎስ በቤቱ ትልቅ ግብዣ አደረገ። ምናልባትም ይህን ያደረገው በቀረበለት ጥሪ የተሰማውን ደስታ ለመግለጽ ይሆናል። ከኢየሱስና ከደቀ መዛሙርቱ ሌላ የማቴዎስ የቀድሞ የሥራ ባልደረቦችም በግብዣው ላይ ተገኝተው ነበር። እነዚህ ሰዎች አይሁዶች ይጠሏቸው ለነበሩት የሮማ ባለ ሥልጣናት ቀረጥ ይሰበስቡ ስለነበረ በሕዝቡ ዘንድ የተናቁ ነበሩ። ከዚህም በላይ ብዙውን ጊዜ ሕዝቡን ከተለመደው የቀረጥ ዋጋ በላይ በማስከፈል ያጭበረብሩ ነበር።

ፈሪሳውያን ኢየሱስ በግብዣው ላይ ከእነዚህ ሰዎች ጋር ተቀምጦ ሲመለከቱ ደቀ መዛሙርቱን “መምህራችሁ ከቀራጮችና ከኃጢአተኞች ጋር አብሮ ስለ ምን ይበላል?” ብለው ጠየቋቸው። ኢየሱስ ሲጠይቋቸው ሰማና እንዲህ ሲል ለፈሪሳውያን መለሰላቸው:- “ሕመምተኞች እንጂ ባለ ጤናዎች ባለ መድኃኒት አያስፈልጋቸውም፤ ነገር ግን ሄዳችሁ:- ምሕረትን እወዳለሁ መሥዋዕትንም አይደለም ያለው ምን እንደሆነ ተማሩ፤ ኃጢአተኞችን ወደ ንስሐ እንጂ ጻድቃንን ልጠራ አልመጣሁም።”

ማቴዎስ እነዚህን ቀረጥ ሰብሳቢዎች ወደ ቤቱ የጋበዛቸው ኢየሱስን አዳምጠው መንፈሳዊ ፈውስ ማግኘት እንዲችሉ ብሎ ሳይሆን አይቀርም። ስለዚህ ኢየሱስ ከአምላክ ጋር ጤናማ ዝምድና እንዲኖራቸው ለመርዳት ሲል አብሯቸው ተቀመጠ። ኢየሱስ ራሳቸውን ያመጻድቁ እንደነበሩት ፈሪሳውያን እነዚህን ሰዎች አልናቀም። ከዚህ ይልቅ በርኅራኄ መንፈስ ተገፋፍቶ መንፈሣዊ ሐኪም ሆኖ አገልግሏቸዋል።

ስለዚህ ኢየሱስ ለኃጢአተኞች ምሕረት ማሳየቱ ኃጢአታቸውን ችላ ብሎ ማለፉ ሳይሆን አካላዊ ሕመም ላለባቸው ሰዎች ያሳየውን ዓይነት ከአንጀት የመራራት ስሜት መግለጹ ነበር። ለምሳሌ ያህል በሥጋ ደዌ ተይዞ የነበረውን ሰው “እወዳለሁ፣ ንጻ” በማለት በአዘኔታ እጁን ዘርግቶ በመዳሰስ ያሳየውን ርኅራኄ ማስታወስ ትችላለህ። እኛም ልክ እንደዚሁ ችግር ያለባቸውን ሰዎች በተለይ በመንፈሳዊ መንገድ በመርዳት ምሕረት እናሳይ። ማቴዎስ 8:​3፤ 9:​9-13፤ ማርቆስ 2:​13-17፤ ሉቃስ 5:​27-32

▪ ኢየሱስ ማቴዎስን ያየው የት ነበር?

▪ የማቴዎስ ሥራ ምን ነበር? ሌሎች አይሁዶች እነዚህን ሰዎች የሚንቋቸውስ ለምንድን ነው?

▪ በኢየሱስ ላይ የቀረበው ክስ ምን ነበር? እሱስ ምላሽ የሰጠው እንዴት ነው?

▪ ኢየሱስ ኃጢአተኞችን የቀረባቸው ለምንድን ነው?