በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ስለ ጾም ተጠየቀ

ስለ ጾም ተጠየቀ

ምዕራፍ 28

ስለ ጾም ተጠየቀ

ኢየሱስ በ30 እንደ ዘመናችን አቆጣጠር በተከበረው የማለፍ በዓል ላይ ከተገኘ አንድ ዓመት ሊሞላ ምንም ያህል አልቀረም። መጥምቁ ዮሐንስ ከታሰረ ብዙ ወራት ሆኖታል። ምንም እንኳ ዮሐንስ ደቀ መዛሙርቱ የክርስቶስ ተከታዮች እንዲሆኑ የፈለገ ቢሆንም ይህን እርምጃ የወሰዱት ሁሉም አልነበሩም።

በእስር ላይ የሚገኘው የዮሐንስ ደቀ መዛሙርት ከሆኑት ከእነዚህ ሰዎች መካከል የተወሰኑት ወደ ኢየሱስ መጡና “እኛና ፈሪሳውያን፣ ብዙ ጊዜ የምንጦመው፣ ደቀ መዛሙርትህ ግን የማይጦሙት ስለ ምንድር ነው?” ብለው ጠየቁት። ፈሪሳውያን የሃይማኖታቸው ሥርዓት አድርገው በሳምንት ሁለት ጊዜ ይጾሙ ነበር። የዮሐንስ ደቀ መዛሙርትም ይህንኑ ልማድ ሳይከተሉ አይቀሩም። ይጾሙ የነበረው በዮሐንስ መታሰር በማዘን ሊሆንም ይችላል። እናም የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት በዚህ የሐዘን መግለጫ ለምን እንደማይካፈሉ ለማወቅ ፈልገው ይሆናል።

ኢየሱስ እንዲህ ሲል መለሰላቸው:- “ሚዜዎች ሙሽራው ከእነርሱ ጋር ሳለ ሊያዝኑ ይችላሉን? ነገር ግን ሙሽራው ከእነርሱ የሚወሰድበት ወራት ይመጣል፣ በዚያ ጊዜም ይጦማሉ።”

የዮሐንስ ደቀ መዛሙርት ዮሐንስ ራሱ ሙሽራው ኢየሱስ መሆኑን እንደተናገረ አስታውሰው መሆን አለበት። ስለዚህ ዮሐንስም ሆነ የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ኢየሱስ እያለ መጾም አስፈላጊ ሆኖ አልታያቸውም። ከጊዜ በኋላ ኢየሱስ ሲሞት ደቀ መዛሙርቱ ያዝናሉ፤ እንዲሁም ይጾማሉ። ሆኖም ከሞት ተነስቶ ወደ ሰማይ ካረገ በኋላ ግን በሐዘን የሚጾሙበት ምክንያት አይኖርም።

ኢየሱስ በመቀጠል እነዚህን ምሳሌዎች አቀረበ:- “በአረጀ ልብስ አዲስ እራፊ የሚያኖር የለም፤ መጣፊያው ልብሱን ይቦጭቀዋልና፣ መቀደዱም የባሰ ይሆናል። በአረጀ አቁማዳ አዲስ የወይን ጠጅ የሚያኖር የለም፤ ቢደረግ ግን፣ አቁማዳው ይፈነዳል፣ የወይን ጠጁም ይፈሳል አቁማዳውም ይጠፋል፤ ነገር ግን አዲሱን የወይን ጠጅ በአዲስ አቁማዳ ያኖረዋል።” እነዚህ ምሳሌዎች ከጾም ጋር ምን ግንኙነት አላቸው?

ኢየሱስ ማንም ሰው ተከታዮቹ እንደ ጾም ሥርዓት ያሉትን የአይሁድ እምነት ያረጁ ልማዶች ይከተላሉ ብሎ መጠበቅ እንደሌለበት የመጥምቁ ዮሐንስ ደቀ መዛሙርት መገንዘብ እንዲችሉ እየረዳቸው ነበር። ኢየሱስ ወደ ምድር የመጣው ለመጣል የደረሱ ያረጁ የአምልኮ ሥርዓቶችን ለመጠገንና ዕድሜያቸውን ለማራዘም አይደለም። ክርስትና የተቋቋመው በጊዜው ከነበረውና በሰዎች ወግ ከተሞላው የአይሁድ እምነት ጋር እንዲጣጣም አይደለም። በፍጹም፣ ክርስትና ባረጀ ልብስ ላይ እንደሚጣፍ አዲስ ጨርቅ ወይም ባረጀ አቁማዳ ውስጥ እንደሚቀመጥ አዲስ የወይን ጠጅ አይሆንም። ማቴዎስ 9:​14-17፤ ማርቆስ 2:​18-22፤ ሉቃስ 5:​33-39፤ ዮሐንስ 3:​27-29

▪ ይጾሙ የነበሩት እነማን ናቸው? ዓላማቸውስ ምን ነበር?

▪ የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ኢየሱስ አብሯቸው እያለ የማይጾሙት ለምንድን ነው? ከዚያም በኋላ ለጾም ምክንያት የሚሆነው ነገር ወዲያው የሚወገደው እንዴት ነው?

▪ ኢየሱስ ምን ምሳሌዎችን ተናገረ? ትርጉማቸውስ ምንድን ነው?